ስታርመር ስደተኞችን ለመቆጣጠር በዩኬ ድንበሮች ጦራቸውን ሊጠቀሙ እንደሚችሉ ትራምፕ ጠቆሙ

የፎቶው ባለመብት, EPA
የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በዩኬ ያደረጉትን ሁለተኛ ጉብኝት ሲያጠናቅቁ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ሰር ኪር ስታርመር ጦራቸውን በመጠቀም ሕገወጥ ስደትን ማስቆም እንደሚችሉ ጠቁመዋል።
ትራምፕ በስደተኞች ጉዳዮች ላይ ከሰር ኪር ጋር ባደረጉት ስብሰባ ላይ መወያየታቸውን ተናግረዋል።
ፕሬዚዳንቱ የአሜሪካን ድንበር ለመጠበቅ ስላወጧቸው ፖሊሲዎች የተናገሩ ሲሆን ዩናይትድ ኪንግደምም በትናንሽ ጀልባዎች የእንግሊዝ ቻናልን በሚያቋርጡ ስደተኞች የተነሳ ተመሳሳይ ፈተና ገጥሟታል ብለዋል።
"ሰዎች እየገቡ በመሆኑ እኔ ብሆን እንደማስቆም ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ነግሬው ነበር። ጦሩን ብታሰማሩም ሆነ ሌላ መንገድ ብትጠቀሙ ምንም አይደለም ብያለሁ" ብለዋል ትራምፕ።
ከፎክስ ኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ደግሞ ሰር ኪርን "ክፉኛ" እየጎዳው ነው በማለት በስደተኞች ላይ "ጠንካራ እርምጃ" እንዲወስዱ አሳስበዋል።
ትራምፕ ከዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ጋር በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት እንደተናገሩት ሕገ ወጥ ስደት "አገሮችን ከውስጥ ያጠፋል። እናም አሁን ወደ አገራችን የገቡትን ብዙ ሰዎችን እናስወግዳለን" ብለዋል።
ትራምፕ በድጋሚ ተመርጠው ወደ ዋይት ሐውስ ከተመለሱ በኋላ ሕገ ወጥ ስደተኞችን የማስወጣት እና ሕገ ወጥ የድንበር ዝውውሮችን የመቆጣጠር ሥራውን አሳድገውታል።
ለሁለት ቀናት በቆየው የዩናይትድ ኪንግደም ጉብኝታቸው በዊንሶር ቤተመንግሥት በንጉሥ ቻርልስ እና በንጉሣዊው ቤተሰብ ተስተናግድዋል።
ሐሙስ ዕለት ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ፖለቲካዊ ውይይት ከማድረጋቸው በፊት ረቡዕ ዕለት በመንግሥት ግብዣ ላይ ተገኝተዋል።
ፕሬዚዳንቱ እና ቀዳማዊት እመቤት ሜላኒያ ትራምፕ ከጋዜጣዊ መግለጫው በኋላ ብዙም ሳይቆይ ከስታንስተድ አውሮፕላን ማረፊያ በኤር ፎርስ ዋን ዩናይትድ ኪንግደምን ለቅቀው ወጥተዋል።
ከዩናይትድ ኪንግደም እና ከአሜሪካ ጋዜጠኞች ጋር ባደረጉት ሰፊ የጥያቄና መልስ ቆይታ መሪዎቹ ስለፍልስጤም መንግሥት መመስረት፣ የመናገር ነፃነት፣ የዩክሬን ጦርነት፣ ኃይል እና ሌሎችም ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ጥያቄ ቀርቦላቸዋል።
መሪዎቹ በዩናይትድ ኪንግደም እና በዩናይትድ ስቴትስ መካከል ያለውን "ልዩ ግንኙነት" በመጥቀስ አዲስ የቴክኖሎጂ ስምምነትን ይፋ አድርገዋል።
ስምምነቱ በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (ኤአይ) ዘርፍ "የበላይ እንዲሆኑ" እንደሚረዳቸው ትራምፕ ተናግረዋል።
በቼከርስ የተፈረመው የቴክኖሎጂ ስምምነት የአሜሪካ ኩባንያዎች በእንግሊዝ ኢንቨስት በማድረግ በኤአይ፣ ኳንተም እና ሌሎች አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች ላይ ያላቸውን ትብብር ያሳድጋል።
ጉብኝቱ ብሪታንያ በንግድ ወይም በውጭ ፖሊሲ ላይ ያላትን ተጽዕኖ ያሳድጋል ወይ የሚል ጥያቄ ከቢቢሲ ለዋይት ሐውስ ዋና ኃላፊ ሱዚ ዊልስ ቀርቦ "ምንም" ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።
የዩናይትድ ስቴትስ የንግድ ሚኒስትር ሃዋርድ ሉትኒክ ለቢቢሲ እንደተናገሩት ብሪታንያ እንደ ዲጂታል አገልግሎት ግብር ወይም የበይነ መረብ ደህንነት ሕግ ያሉ እና ኢንቨስትመንቶችን የሚገቱ ሕጎችን ብታነሳ የኤአይ የኢንቨስትመንት ስምምነቱ አስር እጥፍ ሊሆን ይችላል።
ትራምፕ እና ሰር ኪር በብሪታንያ ስለተነሳው የመናገር ነፃነትን ክስ እና ባለፈው ሳምንት ፒተር ማንደልሰን ከአሜሪካ የዩናይትድ ኪንግደም አምባሳደር ኃላፊነታቸው እንዲነሱ መደረጉን ጨምሮ በተለያዩ አከራካሪ ጉዳዮች ዙሪያ ሃሳባቸውን አካፍለዋል።
ለሎርድ ማንደልሰን ሐዘኔታ እንደተሰማቸው ሲጠየቁ "በእርግጥ እሱን አላውቀውም" ሲሉ ትራምፕ መልሰዋል።
ትራምፕ ሎርድ ማንደልሰን ከሟቹ ጄፍሪ ኤፒስቴይን ጋር ባለው ግንኙነት ምክንያት ከኃላፊነት ወዳባረሩት ሰር ኪር ጥያቄውን አስተላልፈዋል።
በአንድ አጋጣሚ ደግሞ በፍልስጤም ጉዳይ ላይ "ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር አልስማማም" ሲሉ ትራምፕ ተናግረዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሚቀጥለው ሳምንት በኒውዮርክ ከሚካሄደው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባዔ በፊት ለፍልስጤም አገርነት ዕውቅና ለመስጠት አቅደዋል።
ፍልስጤም የተወሰነ ዓለም አቀፍ ዕውቅና ቢኖራትም በዓለም አቀፍ ደረጃ ስምምነት የተደረሰበት ድንበር፣ ዋና ከተማ እና ጦር የላትም።
በአሁኑ ወቅት ከ193 የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አባል አገራት 147ቱ ለፍልስጤም ዕውቅና ሰጥተዋል። ዩናይትድ ኪንግደም ድጋፋቸውን የሰጡ አገራት ዝርዝርን በመቀላቀል ጠንከር ያለ የፖለቲካ ውሳኔ እንደምትሰጥ ይጠበቃል።
ትራምፕ ይህን የመሰለውን እርምጃ በመቃወም የፍልስጤሙ ታጣቂ ቡድን ሐማስ ጋዛ ውስጥ "ታጋቾቹን እንደ ማጥመጃ ያደርጋቸዋል" ሲሉ ከሰዋል።
በዩክሬን ጦርነት ዙሪያ ጥያቄዎች የተነሱ ሲሆን፤ የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ለሰላም ጥረቶች ድጋፍ ባለማድረጋቸው የተሰማቸውን ቅሬታ ትራምፕ ገልጿል።
"በእርግጥም አሳዝኖኛል" ብለዋል።
ትራምፕ አክለውም ፑቲንን ወደ ድርድር ጠረጴዛ እንዲመጡ ለማስገደድ ምዕራባውያን አጋሮች የሩስያ ነዳጅ መግዛታቸውን እንዲያቆሙ ቢያሳስቡም ሞስኮን ላይ ስለሚጣል ማዕቀብ ግን አልገለጹም።
በትራምፕ እና በስታርመር መካከል ሕገ ወጥ ስደትን ለመቅረፍ በሚደረግ ጥረት ላይ ምንም ልዩነት አልነበረም።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ መንግሥታቸው ሕገ ወጥ ስደትን "በትኩረት" ሲመለከተው የነበረ ጉዳይ ነው ብለዋል።
ሰር ኪር አክለውም መንግሥታቸው ፈረንሳይን ጨምሮ ከሌሎች አገሮች ጋር ስደተኞችን ለመመለስ ስምምነቶችን መፈጸሙን እና በሕገወጥ የሰው አዘዋዋሪዎች ላይ እርምጃ ሲወስድ መቆየቱን ተናግረዋል።
ከፈረንሣይ ጋር በተደረገው የአንድ ማስገባት፣ የአንድ ማስውጣት ዕቅድ መሠረት ለመጀመሪያ ጊዜ ስደተኛ መመለሳቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቁመዋል።
የቁጥሩ መጨመር በብሪታንያ ፖለቲካ ውስጥ ጎልተው ከሚወጡ ጉዳዮች አንዱ ሲሆን ጠቅላይ ሚኒስትሩ የመፍትሄ ሃሳብ እንዲያቀርቡ ግፊትም በዝቶባቸዋል።
ትራምፕ ሕገ ወጥ ስደትን ለመቅረፍ ባደረጉት እንቅስቃሴ በደቡብ ድንበር በኩል የሚገቡ ጥገኝነት ጠያቂዎች ላይ ሰፊ እገዳን ተግባራዊ በማድረግ ተከታታይ የስራ አስፈፃሚ ትዕዛዞችን አውጥተዋል። የድንበር ደህንነት ጥረቶችን ለመርዳት ወታደሮችን አሰማርተዋል።
ትራምፕ ሥልጣን ከያዙ በኋላ በአሜሪካ የድንበር ጥበቃ ሠራተኞች የሚያዙ ስደተኞች ቁጥር እየቀነሰ መጥቷል።
ትራምፕ ከፎክስ ኒውስ ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ ወቅት ዩናይትድ ኪንግደም አንዳንድ ታሪፎችን መቀነስ ትችል እንደሆነ ተጠይቀው ሰር ኬርን "ወድጄዋለሁ" አሁን ባለው ስምምነት ግን አሜሪካ "ብዙ ገንዘብ እያገኘች ነው" ሲሉ መልሰዋል።
ዩናይትድ ኪንግደም ለነዳጅ እና ጋዝ ማውጫ "የሰሜን ባህርን እንድትከፍት" ጠይቀዋል።
ትራምፕ አክለውም "እዚህ ከዋጋው ጋር በተያያዘ ትልቅ የኃይል ችግር አለባቸው" ብለዋል።















