ታሊባን፡ የአፍጋኒስታን የባንክ ሥርዓት ሊንኮታኮት ከቋፍ ደርሷል ተባለ

የፎቶው ባለመብት, WAKIL KOHSAR/AFP
የአፍጋኒስታን የባንክ ሥርዓት ወደ መፍረስ ተቃርቧል ሲሉ አንድ የሃገሪቱ ባንክ ኃላፊ ለቢቢሲ ተናገሩ።
የአፍጋኒስታን እስልምና ባንክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሰይድ ሙሳ ካሌም አል-ፈላሂ እንዳሉት ደንበኞች በተደናገጡበት በዚህ ወቅት የሃገሪቱ የፋይናንስ ኢንዱስትሪ "የህልውና ቀውስ" ውስጥ ይገኛል።
በካቡል ባለው ትርምስ ምክንያት ጊዜያዊ መቀመጫቸው ካደረጉበት ከዱባይ "በአሁኑ ጊዜ ከፍተኛ ገንዘብ እየወጣ ነው" ብለዋል።
አክለውም "ገንዘብ ማውጣት ብቻ እየተከናወነ ነው። አብዛኛዎቹ ባንኮች እየሠሩ አይደሉም። ሙሉ አገልግሎትም አይሰጡም" ሲሉ ገልጸዋል።
በነሐሴ ወር ታሊባን ሃገሪቱን ከመቆጣጠሩ በፊትም የአፍጋኒስታን ኢኮኖሚ ያልተረጋጋ ነበር።
ኢኮኖሚው በከፍተኛ ሁኔታ በውጭ ዕርዳታ ላይ የተመሠረተ ነው። ከጠቅላላው የሀገር ውስጥ ምርት 40 በመቶ የሚሆነው ከዓለም አቀፍ ዕርዳታ የተገኘ መሆኑን የዓለም ባንክ ገልጿል።
ታሊባን ሃገሪቱን ከተቆጣጠረ በኋላ ምዕራባውያኑ አፍጋኒስታን ከዓለም ባንክ እና ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ጋር ሊያገኙ ይችሉ የነበሩትን ንብረቶች እና ገንዘብን አግደዋል።
እንደ አል-ፈላሂ ከሆነ እገዳው ታሊባን ሌሎች የገንዘብ ምንጮችን እንዲያፈላልግ ያበረታታል ብለዋል።
"ቻይና እና ሩሲያ ጨምሮ ሌሎች ሃገሮችንም በጉጉት እየተጠባበቁ ነው።"
"... በቅርቡም ይሁን ዘግይቶ በውይይት የሚሳካላቸው ይመስላል" ብለዋል።
ቻይና አፍጋኒስታንን እንደገና ለመገንባት እና ከታሊባን ጋር ለመሥራት ስላላት ፍላጎት ቀድሞውኑ አሳውቃለች።
በቻይና መንግስት ቁጥጥር ስር ያለው ግሎባል ታይምስ ጋዜጣ በቅርቡ "አፍጋኒስታንን በመገንባት ረገድ ትልቅ የትብብር አቅም አለ" ያለ ሲሆን ቻይና በእርግጠኝነት "መሪ" መሆኗን ተናግሯል።
ታሊባን የአፍጋኒስታንን የኢኮኖሚ ችግሮች ለማስተካከል ጫና እያደረበት ነው።
የዋጋ ግሽበት እየናረ ሲሆን የአገሪቱ መገበያያ ገንዘብ አፍጋኒ የመግዛት አቅሙ እየቀነሰ ነው። ብዙዎች ሥራ ያጡ ሲሆን የገንዘብ እጥረት በመኖሩ ሰዎች ተስፋ ቆርጠዋል።
በአፍጋኒስታን በየቀኑ በቂ ምግብ ያላቸው ቤተሰቦች አምስት በመቶዎቹ ብቻ ናቸው ሲል የተባበሩት መንግስታት የዓለም የምግብ ፕሮግራም አስጠንቅቋል።
ጥናት ከተደረገባቸው ሰዎች መካከል ግማሾቹ ባለፉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ ቢያንስ አንድ ጊዜ ምግብ እንዳለቀባቸው ተናግረዋል።
ለአፍጋኒስታን ህልውና ሲባል ዓለም አቀፍ ገንዘብ እና የውጭ ዕርዳታ ማግኘት ቁልፍ ነው።
ነገር ግን እንደ አሜሪካ ያሉ ሃገራት ከታሊባን ጋር ለመሥራት ፈቃደኞች ቢሆኑም የአገዛዙን የሴቶች ሰብዓዊ አያያዝ ጨምሮ በሌሎች ቅድመ ሁኔታዎች ላይ የተመሠረተ ነው።
አል-ፈላሂ እንዳሉት ታሊባን ሴቶች "ለጊዜው" መሥራት እንደማይፈቀድላቸው ቢገልጽም በባንኩ የሚሠሩ ሴቶች ወደ ሥራ ገበታቸው እየተመለሱ ነው።
"በሴቶች መካከል ... ፍርሃት ነበር። ወደ ቢሮ አይመጡም ነበር። አሁን ግን ቀስ በቀስ ወደ ሥራ ገበታቸው መምጣት ጀመረዋል" ብለዋል።
የአል-ፈላሂ አስተያየት ከፓኪስታኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ኢምራን ካን በቅርቡ ከሰጡት መግለጫም ጋር ይቀራረባል።
ለቢቢሲ ቃለ ምልልስ በሰጡበት ወቅት ካን እንዳሉት ታሊባኖች ከዚህ ቀደም በስልጣን ላይ ከነበሩበት ወቅት ጋር ሲነጻጸር ለዓለም የበለጠ ዘመናዊ እና የተሻሻለ ገጽታ ለማሳየት እየሞከሩ ነው በማለት- የታሊባን 2.0 ዓይነት ሲሉ ገልጸዋል።
"በአሁኑ ወቅት የበለጠ ተለዋዋጭ እና በጣም ተባባሪ ናቸው።"
ካን "ለጊዜው ምንም ጥብቅ ህጎችንን እና ደንቦችን አላስተላለፉም" ብለዋል።
የሴቶች እና የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ታሊባን በሚናገረው እና በመሬት ላይ ባለው እውነታ መካከል ትልቅ ልዩነት እንዳለ ጠቁመዋል። ብዙ ሴቶች እና ልጃገረዶች ወደ ትምህርት ቤት ወይም ሥራ እንዳይሄዱ ተከልክለዋል ሲሉም ያስረዳሉ።












