ሙጋቤ እንደገና እንዲቀበሩ የዚምባብዌ ባህላዊ መሪ ወሰኑ

የፎቶው ባለመብት, PHILL MAGAKOE
ዚምባብዌን ከሦስት አስርት አመት በላይ የመሯት ሮበርት ሙጋቤ አፅም ከተቀበረበት ወጥቶ በብሔራዊ መካነ መቃብር እንዲያርፍ የአገሪቱ ባህላዊ መሪ ውሳኔን አስተላልፈዋል።
ከሁለት አመት በፊት ሕይወታቸው ያለፈው ሙጋቤ በሕይወት እያሉ በተናዘዙት መሰረት የተቀበሩት በትውልድ ቦታቸው ኩታማ ከተማ ነበር፤ ነገር ግን እንደሳቸው ያሉ የአገር መሪም ሆነ ታላላቅ ባለስልጣናት ሲሞቱ የሚቀበሩት በመዲናዋ ሃራሬ በሚገኘው የብሔራዊ ጀግኖች መካነ መቃብር ነው።
ሙጋቤን በስልጣን የተኩት ፕሬዚዳንት ኤመርሰን ምናንጋግዋም ሆነ ሌሎች ባለስልጣናት ሙጋቤ እዚህ ስፍራ እንዲቀበሩ ምኞታቸው ነበር።
የዚምባብዌ መንግሥት ቀብራቸውን ይፈፀምበታል ባለው ስፍራ ለስማቸው መጠሪያ ሐውልት አቆማለሁ፣ በትውልድም ሲታወሱም ይኖራሉ በማለቱ አስከሬናቸው በቤታቸው ተቀምጦ ቆይቶ ነበር።
የሙጋቤ ቤተሰቦች በበኩላቸው በብሔራዊ መካነ መቃብር ከተቀበሩ ከስልጣን ያስወገዷቸው የፖለቲካ ተቀናቃኞቻቸው አፅሙን አንዳንድ "ጥንቆላ" መሰል ስራዎች ሊያከናውኑ ይችላሉ ይላሉ። ይህንንም ያደረባቸውን ስጋት ሙጋቤ በሕይወት እያሉ ተናግረዋል ይላሉ።
በያዝነው ሳምንት ሰኞ ዝቪምባ የሚባለው ግዛት ባህላዊ መሪ እንዳሉት ከሙጋቤ ጎሳ አባላት ስለ መቃብር ስፍራቸው ቅሬታ እንደደረሳቸው ነው።
መሪው ባለቤታቸው ግሬስ ሙጋቤ ባህላዊ እሴቶችን በመጣስ ሙጋቤን ከቤታቸው ጓሮ ቀብራቸዋለች በማለት ጥፋተኛ አድርገዋታል። ግሬስ ሙጋቤ በውሳኔው ላይ ባትኖርም መሪው አምስት ላሞችና አንድ ፍየል እንድትከፍል ቅጣት ጥለውባታል።
"ባህላዊው መሪው ኩታማ ግዛት አይመለከታቸውም። የኩታማ ግዛት የሚመለከተው ባህላዊ መሪ ይህንን ውሳኔም ቢያስተላልፍም እጃችንን አጣጥፈን አንመለከትም። ፍርድ ቤት ይግባኝ ብለን እንጠይቅ ነበር" በማለት የቤተሰቡ ቃለ አቀባይ ሊዮ ሙጋቤ ለሮይተርስ የዜና ወኪል ተናግሯል።












