በፈረንሳይ ኩሽና ውስጥ ተሰቅሎ የተገኘ ስዕል በ24 ሚሊዮን ዩሮ ተሸጠ

የፎቶው ባለመብት, AFP/Getty Images
በዕውቅ ጣሊያናዊ ሰዓሊ ተስሎ የነበረው እና ለረዥም ዓመታት ጠፍቶ የቆየው ስዕል በአንዲት አዛውንት ፈረንሳያዊ ሴት ኩሽና ውስጥ ከተገኘ በኋላ ሪኮርድ በሆነ በ24 ሚሊዮን ዩሮ ዋጋ በጨረታ ተሸጠ።
ይህ የስዕል ሥራ ከአንድ ወር በፊት ነበር በሰሜናዊ ፈረንሳይ የተገኘው።
6 ሚሊዮን ዋጋ ያወጣል ተብሎ ቢገመጥም፤ ከተገመተው አራት እጥፍ በሆነ ዋጋ በጨረታ ተሽጧል።
አጫራጩ ድርጅት በሥም የልተጠቀሰው የስዕሉ ገዢ ከሰሜናዊ ፈረንሳይ እንደሆነ ጠቁሟል።
ስዕሉ ለበርካታ ዓመታት በኩሽና ውስጥ ከማብሰያ ምድጃ በላይ ግድግዳ ላይ ተንጠልጥሎ ቆይቷል። አንድ የስዕል ባለሙያ እና አጫራች ስዕሉን ከተመለከተ በኋላ ባለቤቶቹ የስዕሉን ዋጋ ለማስተመን ባለሙያዎችን እንዲያማክሩ ሲወተውት ነበር ተብሏል።
ባለቤቶቹ ግን ስዕሉ እድሜ ጠገብ ሃይማኖታዊ ምልዕክት ያለው ስዕል ከመሆን ባለፈ ብዙ ዋጋ ያለው የጥበብ ሥራ መስሎ አልታያቸውም።
በስዕሉ ላይ የተደረጉ ጥልቅ ምርምሮች ስዕሉ የጣሊያናዊው ሰዓሊ ሶኒ ዲ ፔፖ መሆኑን አረጋገጥዋል።
በጣሊያን ፍሎረንስ የተወለደው ሶኒ ዲ ፔፖ በ13ኛው ክፈለ ዘመን መጨረሻ ላይ እና በ14ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ የስዕል ሥራዎችን ሰርቷል።
ይህ የጥበብ ሥራ በመጠን አነስተኛ ሲሆን 20 ሲ.ሜትር በ26 ሴንቲ ሜትር ያክላል። ስዕሉ የአንድ የስዕል ሥራ አካል ሲሆን የተቀሩት ስዕሎች ሎንደን እና ኒው ዮርክ በሚገኙ የሰዕል ማሳያ ማዕከል ውስጥ ይገኛሉ።












