የታንዛንያው ፕሬዝዳንት ለ1700 ኢትዮጵያውያን እስረኞች ምሕረት አደረጉ

ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ እና ፕሬዝዳንት ማጉፉሊ

የፎቶው ባለመብት, Citizen Tanzania

ታንዛንያ 1 ሺህ 700 ኢትዮጵያውያን ሕገ ወጥ ስደተኞችን ወደ አገራቸው እንደምትመልስ ገለፀች።

የታንዛንያው ፕሬዝዳንት ጆን ፖምቤ ማጉፉሊ ይህንን የተናገሩት የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በታንዛንያ የአንድ ቀን ይፋዊ የሥራ ጉብኝት ባደረጉበት ወቅት ነው።

ኢትዮጵያውያኑ የታንዛንያን ድንበር በሕገ ወጥ መልኩ አቋርጠው ገብተው የተያዙ እና በአገሪቱ በሚገኙ የተለያዩ እስር ቤቶች ውስጥ የሚገኙ ናቸው ተብሏል።

ታንዛንያ በሕገ ወጥ ደላሎች ወደ ደቡብ አፍሪካ ለሚደረግ ሕገ ወጥ ስደት እንደመተላለፊያ መስመር በመሆን ታገለግላለች።

የታንዛንያው ፕሬዝዳነት ጆን ማጉፉሊ ለኢትዮጵያውያን እስረኞች ምሕረት ማድረጋቸውን የገለፁት በትናንትናው ዕለት ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት ወደ አገሪቱ አምርተው ከተወያዩ በኋላ ነው።

ሁለቱ አገራት በአፄ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት የታንዛኒያው መሪ ጁልየስ ኔሬሬ ከነበሩበት ጊዜ አንስቶ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የነበራቸው ናቸው።

የታንዛንያ ፕሬዝዳነት ማጉፉሊ፤ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅን ባስተናገዱበት በትናንትናው ዕለት፤ "በሁለቱ አገራት መካከል ካለው ወዳጅነት የተነሳ [ኢትዮጵያውያን እስረኞች] በነጻ ወደ አገራቸው እንዲሄዱ መፍቀዳችንን ነግሬያቸዋለሁ" ብለዋል።

ፕሬዝዳንቱ በንግግራቸው ወቅት ከኢትዮጵያኑ እስረኞች መካከል በታንዛንያ እስር ቤቶች ውስጥ ለሰባት ዓመት ያህል የቆዩ እንደሚገኙበት ተናግረዋል።

ማጉፉሊ አክለውም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግዙፍ አየር መንገድ መሆኑን በመጥቀስ፤ 260 ሰው የመጫን አቅም ያለው ድሪም ላይነር አውሮፕላን በሁለት በረራ ከአንድ ኤር ባስ ጋር ተጨምሮ እስረኞቹን በአንድ ጊዜ ወደ አገራቸው መመለስ እንደሚቻል ገልፀዋል።

"ዛሬ እንኳን የታሰረ እስረኛ ቢኖር ሁሉንም ለመውሰድ እስከመጣችሁ ድረስ እንዲለቀቅ እፈቅዳለሁ፤ ይህ ደግሞ በሁለቱ አገራት መካከል ያለው መልካም ግንኙነት ማሳያ ነው" ብለዋል።

ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በበኩላቸው፤ በሕገ ወጥ መንገድ ወደ ታንዛንያ የገቡ ኢትዮጵያውያን በመላው ታንዛንያ በሚገኙ እስር ቤቶች እንደሚገኙ አስታውሰው፤ የታንዛንያ መንግሥት ወደ አገራቸው እንዲሄዱ በመፍቀዱ የኢትዮጵያ መንግሥት እነዚህን ዜጎች ለመመለስ የሚቻለውን ሁሉ አንደሚያደርግ ገልፀዋል።

አክለውም የታንዛንያ መንግሥት እነዚህ ዜጎች በነጻ እንዲለቀቁ በመፍቀዱ አመስግነዋል።

በታህሳስ ወር በዳሬ ሰላም የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ በታንዛኒያ 4 ግዛቶች ውስጥ በሚገኙ ማረሚያ ቤቶች ባደረገው ጉብኝት ቁጥራቸው 1100 የሆኑ ኢትዮጵያውያን ታስረው ማግኘቱን ገልጾ ነበር።

ታሳሪዎቹ አብዛኞቻቸው ባለፉት 4 ወራት ውስጥ የታንዛኒያን ድንበር በሕገ ወጥ መልኩ አቋርጠው በመግባታቸው በፖሊስ ተይዘው ከ6 ወር እስከ 2 ዓመት የሚደርስ የእስራት ፍርድ የተፈረደባቸው መሆናቸውንም አክሎ ገልጾ ነበር።

እነዚህ ሕገ ወጥ ስደተኞች በአብዛኛው የመጡት ከሀድያ እና ከምባታ ዞኖች መሆናቸው ሲገለጽ፤ በሁለተኛ ደረጃ ከወላይታ እና ሃላባ ዞኖች የመጡ እንደሚገኙበት ኤምባሲው በድረ ገፁ ላይ አስታውቆ ነበር።

በወቅቱ ሁሉም ታሳሪ ስደተኞች ወንዶች መሆናቸው ተመልክቶ፤ እድሜያቸው ከ14 እስከ 46 ዓመት ባለው ውስጥ መሆኑ ይፋ ተደርጎ ነበር።

ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ በታንዛንያ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ከ3100 በላይ ዜጎችን ከእስር አስፈትቶ ወደ አገር ቤት መመለሱን ገልጿል።

ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በታንዛንያ በነበራቸው ይፋዊ የሥራ ጉብኝት በሁለቱ አገራት መካከል ስላለ ንግድ፣ ቱሪዝም፣ እና ኢንቨስትመንት መወያየታቸውን በአገሪቱ የሚታተሙ ጋዜጦች ዘግበዋል።