የላስ ቬጋስ ጥቃት፡ የፓዶክ የሴት ጓደኛ ስለጥቃቱ 'አታውቅም' ነበር

ፓዶክና ማሪሎ
የምስሉ መግለጫ, የቀድሞዋ የቁማር መጫወቻ ቤት ተቀጣሪ ማሪሎ በኔቫዳ ከፓዶክ ጋር ትኖር እንደነበር ፖሊስ ገልጿል

ባለፈው እሁድ 58 ሰዎችን የገደለው የላስቬጋሱ ታጣቂ የሴት ጓደኛ የሆነችው ማሪሎ ዳንሌይ ፓዶክን 'ትሁት፣ ተንከባካቢና ጭምት' ብለ ስትገልፀው ስለ ጥቃት እቅቁ ግን ምንም እንደማታውቅ ተናግራለች።

ማሪሎ ዳንሌይ ይህን የተናገረችው ፖሊስ የፓዶክ ሕይወት ''ምስጢራዊ'' እንደነበር ከመግለጹ ከሰዓታት በፊት ነው።

ፖሊስ ምናልባትም ከጥቃቱ በኋላ ራሱን ከማጥፋት ይልቅ የማምለጥ እቅድ እንደነበረው ቢገልጽም ዝርዝር መረጃ ግን ይፋ አላደረገም።

እስካሁንም በሙዚቃው ዝግጅት ታዳሚዎች ላይ ተኩስ በመክፈት በአሜሪካ የቅርብ ጊዜ ታሪክ የከፋ የተባለውን ግድያ ለምን እንደፈጸመ የታወቀ ነገር የለም።

ጥቃቱን ሲፈጸም ግብረ አበሮች ነበሩት? የሚለው ጥያቄም እስካሁን ምላሽ ባያገኝም ከአሸባሪ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት እንደነበረው የሚያሳይ ምንም መረጃ አልተገኘም።

የሴት ጓደኛውም ለእረፍት ከሄደችበት ፊሊፒንስ በፈቃደኝነት ተመልሳ ትናንት የአሜሪካ የምርመራ ቢሮ (ኤፍ ቢ አይ ) ሲያናግራት ፓዶክ በፈጸመው ''ቃላት የማይገልጹት ጭካኔያዊ ድርጊት'' እንደተደናገጠች ገልጻለች።

ፓዶክ ''ለእኔ እንደማስጠንቀቂያ ሊወሰድ የሚችል ምንም ነግሮኝም ሆነ እርምጃ ወስዶ አያውቅም'' ብላለች በጠበቃዋ በኩል ባቀረበቸው መግለጫ።

በንግግሯ ''አፈቅረው ነበር፤ የወደፊት ህይታችንንም እመኛት ነበር'' ስትል ተደምጣለች።