የላስ ቬጋሱ ታጣቂ ካሜራዎችን በሆቴሉ ውስጥ ገጥሞ ነበር

በሆቴል ከፍል ውስጥ የተገኘ መሳሪያ

የፎቶው ባለመብት, Boston 25 News

የምስሉ መግለጫ, በሆቴል ከፍል ውስጥ የተገኘ መሳሪያ

የ64 ዓመቱ ፓዶክ 59 ሰዎችን በገደለበት እና ከ500 በላይ ሰዎችን ባቆሰለበት ጥቃት የፖሊስን እንቅስቃሴ ለመቃኘት በማሰብ በነበረበት የሆቴል ክፍል ውስጥ እና በአቅራቢያው ካሜራዎችን ገጥሞ እንደነበር ፖሊስ አስታወቀ።

በሆቴሉ መተላለፊያዎች (ኮሪደሮች) የገጠማቸው ሁለት ካሜራዎች እና በበር ላይ የገጠመው ካሜራ ''የፖሊሶችን ወይም ፀጥታ አስከባሪዎችን'' እንቅስቃሴ እንዲቃኝ አስችሎታል ብሏል ፖሊስ።

እሰካሁን ፓዶክ ጥቃቱን ለመፈፀም ምን እንዳነሳሳው ግልፅ የሆነ ነገር ባይኖርም ጥቃቱን ለመፈፀም ከፍተኛ ዝግጅት አድርጎበት ነበር።

የፖሊስ አዛዥ ጆሴፍ ሎምባርዶ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ''ጥቃቱ ከመፈፀሙ በፊት ከፍተኛ ቅድመ ዝግጅት እንዳደረገ እርግጠኞች ነን'' ብለዋል።

ይህ ጥቃት የአሜሪክ የጦር መሳሪያ አያያዝ ህግ ላይ ክርክር ፍጥሯል። ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ''በሕጉ ላይ መነጋገር ካስፈለገን የምንነጋገርበት ጊዜ አሁን አይደለም'' ብለዋል።

ፖሊስ ፓዶክ ጥቃቱን ከፈፀመበት ክፍል ውስጥ 23 መሳሪያዎችን ሲያገኝ በመኖሪያ ቤቱ ውስጥም የተለያዩ መሳሪያዎችን እና ፈንጂዎችን አግኝቷል።

ጥቃቱ ሲፈፀም ከተቀረፁ ምስሎችና ድምፆች በመነሳት መረዳት እንደተቻለው ፓዶክ የተጠቀማቸው መሳሪያዎች በፍጥነት እንዲተኩሱ ለማድረግ የተለያዩ መለዋወጫዎችን በመጠቀም አሻሽሎ ነበር።