የዓለም መነጋገሪያ ከሆነው ዲፕሲክ ጀርባ ያለው ሊያንግ ዌንፌግ ማን ነው?

ዲፕሲክ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የሰው ሠራሽ አስተውሎት መተግበሪያ የሆነው ዲፕሲክ በመላው ዓለም መነጋገሪያ ሆኗል።

አሜሪካ ውስጥ ከቻትጂፒቲ ቀድሞ መተግበሪያው ተመራጭ የሆነ የሰው ሠራሽ አስተውሎት መተግበሪያ ለመሆን በቅቷል።

የዚህ መተግበሪያ መሥራች እና ቢሊየነሩ ሊያንግ ዌንፌንግ ደግሞ በአንዴ ስሙ ናኝቷል።

ዲፕሲክ ባለፈው ሳምንት ነው ወደ ሥራ የገባው።

ከተቀናቃኞቹ አንጻር በርካሽ ዋጋ ለገበያ የበቃ የሰው ሠራሽ አስተውሎት መተግበሪያ ሆኗል።

የተፎካካሪዎቹን ዋጋ እያሳጣ በርካታ ጥያቄዎችን ለመጫር በቅቷል።

ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የአዲሱ መተግበሪያ ክስተት ለአሜሪካ የቴክኖሎጂ ተቋማት "የማንቂያ ደወል" ነው ሲሉ የደቀነውን ፉክክር ገልጸውታል።

"ጎበዙ ዌንፌንግ"

ዲፕሲክ የተመሠረተው በአውሮፓውያኑ 2023 ነው።

መሥራቹ ሊያንግ ዌንፌንግ በቀጣዩ ዓመት የመጀመሪያውን ትልቁን የሰው ሠራሽ አስተውሎት የቋንቋ አምሳል አቀረበ።

ስለ መሥራቹ የ40 ዓመቱ ሊያንግ ብዙም የሚታወቅ ነገር የለም።

የተወለደው በደቡብ ቻይና ጓንግዶንግ ግዛት ነው።

ዚሄጂያንግ ከተሰኘው ዩኒቨርሲቲ በኤሌክትሮኒክስ ኢንፎርሜሽን ምህንድስና እንዲሁም በኮምፒዩተር ሳይንስ ተመርቋል።

ቴክኖሎጂ ላይ በሚያተኩረው 36ኬአር ላይ በወጣ ጽሑፍ የሚያውቁት ሰዎች "እንደ አለቃ ሳይሆን እንደ በዕውቀት እንደመጠቀ ጎብዝ" እንደሚያዩት ገልጸዋል።

አልፎ አልፎ ብቻ በአደባባይ የሚታየው እና አንዳንዴ ብቻ ቃለመጠይቆችን የሚሰጠው ሊያንግ፣ አሁን በዓለም አቀፍ ደረጃ ትኩረት አግኝቷል።

ከአገሪቱ ሁለተኛ ሰው ሊ ኪያንግ በተሳተፉበት የሥራ ፈጣሪዎች ስብሰባ ላይ እንዲገኝ የተመረጠ ብቸኛው የሰው ሠራሽ አስተውሎት ኩባንያ መሪ ነበር።

አብዛኛዎቹ የአሜሪካ ሰው ሠራሽ አስተውሎት ኩባንያ መሪዎች መነሻቸው ሲሊከን ቫሊ ነው። ሊያንግ ግን መነሻው በፋይናንስ ዘርፍ ነው።

የኢንቨስትመንት ውሳኔዎችን ለማስተላለፍ ሰው ሠራሽ አስተውሎትን ተጠቅሞ የፋይናንስ መረጃን የሚተነትነው የሃይ-ፍላየር ዋና ሥራ አስፈጻሚ ነበር።

የዲፕሲክ መስራች ሊያንግ ዌንፌንግ (በስተቀኝ)

የፎቶው ባለመብት, CCTV

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

ሃይ-ፍላየር እአአ በ2019 ቻይና ውስጥ ከ13 ሚሊዮን ዶላር በላይ ማሰበሳብ የቻለ ድርጅት ነው።

ሊያንግ ሃይ-ፍላየር እያለ የአክሲዮን ዋጋዎችን ሊነኩ የሚችሉ አካሄዶችን ለመለየት ሰው ሠራሽ አስተውሎት እና አልጎሪዝምን (ስልተ ቀመር) በመጠቀም ሃብት አካብቷል።

በሰው ሠራሽ አስተውሎት ዲዛይን የተደረጉ ኤች800 የኮምፕውተር ቺፖች (ግብዓቶችን) እንዲሁም በዎል ስትሪት ተወዳጅ የሆነውን ኒቪዲያን በመጠቀም በአክሲዮኖች ግብይት ላይ የተካነ ሆነ።

በአውሮፓውያኑ 2023 ደግሞ ዲፕሲክን አቋቋመ። በዚህም የሰው አዕምሮን የሚስተካከል ሰው ሠራሽ አስተውሎትን ለማዳበር ያለውን ፍላጎት አሳወቀ።

በዲፕሲክ ጥናት ውስጥ በግሉ የተሳተፈው ሊያንግ ከተለያዩ ኢንቨስተሮች የተሰበሰበ ገንዘብ (ሄጅ ፈንድ) ያገኘውን ገቢ በሰው ሠራሽ አስተውሎት ዘርፍ ምርጥ ተሰጥኦ ላላቸው ከፍተኛ ደመወዝ ለመክፈል እንደተጠቀመበትም ይነገራል።

ኩባንያው ከአሜሪካ ተቋማት ባለሙያዎችን ከመቅጠር ይልቅ እንደ ፔኪንግ፣ ስንጉዋ እና ቤይሃንግ ዩኒቨርሲቲዎች ካሉ ከቻይና ምርት የትምህርት ተቋማት የተወጣጡ ዶክትሬት ያላቸውን ምሑራንን አሰባስቧል።

የቲክ ቶክ ባለቤት እንደሆነው ባይትዳንስ ሁሉ ዲፕሲክም በቻይና ውስጥ ላሉ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ባለሙያዎች ከፍተኛ ደመወዝ ነው የሚከፍላቸው። የተቋሙ ቢሮዎች በሃንግዡ እና ቤይጂንግ ይገኛሉ።

ባለፈው ዓመት ከሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ ሊያንግ ኩባንያው "ከባሕር ማዶ የተመለሱ ባለሙያዎችን አላካተተም። ሁሉም የአገር ውስጥ ባለሙያዎች ናቸው. . .እኛ የራሳችንን ከፍተኛ አቅም ማዳበር አለብን" ብሏል።

የቻይናው ሰው ሠራሽ አስተውሎት ዘርፍ "ለዘላለም የሌሎች ተከታይ ሆኖ ሊቀጥል አይችልም" ሲልም ሊያንግ ተናግሯል።

የዲፕሲክ ሞዴል በሲልከን ቫሊ አግራሞት የፈጠረበትን ምክንያት የተጠየቀው ሊያንግ "እነሱን ያስገረማቸው የቻይና ኩባንያ መድረኩን በመከተል ሳይሆን እንደ ፈጣሪ ሲቀላቀል በማየታቸው ነው። አብዛኞቹ የቻይና ኩባንያዎች የተለመዱት ሌሎችን በመከተል ነው" ብሏል።

ዲፕሲክ እና ቻትጂፒቲ

የፎቶው ባለመብት, Reuters

የዲፕሲክ ተወዳዳሪነት

ዲፕሲክ-አር1 የተሰኘው ሞዴሉ የተሠራው በነባር ቴክኖሎጂ እና ማንም ሰው በነጻ ሊጠቀምበት እና ሊጋራው በሚችለው በነጻ በሚገኝ መተግበሪያ (ሶፍትዌር፣ ኦፕን ሶርስ) መሥራት እንደቻለ ተናግሯል።

'ዋየርድ' መጽሔት ግን የዲፕሲክ መሥራች የሆነው ሊያንግ ዌንፌንግ ኩባንያው ሃይ-ፍላየር የሰው ሠራሽ አስተውሎት የጀርባ አጥንት የሆኑትን ጂፒዩዎች ወይም የግራፊክስ ፕሮሰሲንግ ዩኒት በመባል የሚታወቁትን ቺፖች እያከማቸ እንደነበር ዘግቧል።

ይህም ከ10 ሺህ እስከ 50 ሺህ ሊደርስ እንደሚችል ሲል 'ኤምአይቲ ቴክኖሎጂ ሪቪው' የተሰኘው የቴክኖሎጂ መጽሄት ግምቱን አስቀምጧል።

እነዚያ ቺፖች መሠረታዊ ጥያቄዎችን ከመመለስ አንስቶ ውስብስብ የሂሳብ ቀመሮችን እስከመፍታት የሚደርሱ ከፍተኛ የሰው ሠራሽ ሞዴሎችን ለመገንባት አስፈላጊ ናቸው።

በአውሮፓውያኑ 2022 አሜሪካ የእነዚህን ከፍተኛ ኃይል ያላቸው የቴክኖሎጂ ቺፖች ለቻይና እንዳይሸጡ አገደች።

ይህ እርምጃ "ከባድ ፈተና" ነው ሲል ሊያንግ ከቻይና መገናኛ ብዙሃን ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ ተናግሮ ነበር።

በምዕራቡ ዓለም ያሉ ዋና ዋና የሰው ሠራሽ አስተውሎት መተግበሪያዎች እስከ 16 ሺህ የሚገመቱ ልዩ የቴክኖሎጂ ቺፖችን ይጠቀማሉ። ዲፕሲክ በበኩሉ አር1 የተሰኘውን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ሞዴሉን ለማዘጋት ልዩ የሚባሉ ሁለት ሺህ እና በሺዎች የሚቆጠሩ ዝቅተኛ ደረጃ ያላቸው የቴክኖሎጂ ቺፖችን በመጠቀም እንዳሰለጠነ አስታውቋል። ይህም ርካሽ አድርጎታል።

እንደ ኩባንያው ገለጻ ዲፕሲክ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ለመገንባት 5.6 ሚሊዮን ዶላር ብቻ ፈጅቷል። የቻትጂፒቲ አምራቹ ኦፕንአይአይ ባለፈው ዓመት ብቻ 5 ቢሊዮን ዶላር አውጥቷል።

ቢሊየነሩ ኤሎን መስክን ጨምሮ አንዳንዶች በዚህ ዙሪያ ጥያቄ አንስተዋል። ኩባንያው ከገደቦቹ አንጻር ምን ያህል ልዩ የቴክኖሎጂ ቺፖችን እንደተጠቀመ ሊገልጽ አይችልም ሲሉም ተከራክረዋል።

የዋሽንግተን እገዳ ለቻይና የሰው ሠራሽ አስተውሎት ኢንዱስትሪ ፈተና እንዲሁም ዕድል እንደፈጠረለት ባለሙያዎች ተናግረዋል።

በሲድኒ የቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ተባባሪ ፕሮፌሰር የሆኑት ማሪና ዣንግ "እንደ ዲፕሲክ ያሉ የቻይና ኩባንያዎችን በውስን ነገር እንዲሠሩ አስገድዷቸዋል" ብለዋል።

"እነዚህ ገደቦች ተግዳሮቶችን የሚፈጥሩ ቢሆንም፤ ከቻይና የቴክኖሎጂ ነጻነትን ከማሳካት ሰፊ የፖሊሲ ግቦች ጋር ለማጣጣም ፈጠራን አነሳስተዋል።" ሲሉ ያስረዳሉ።

የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን እና የፀሐይ ፓናሎችን ከሚያንቀሳቅሱ ባትሪዎች እስከ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ድረስ ቻይና በትልልቅ ቴክኖሎጂዎች ላይ ብዙ ገንዘብ አፍስሳለች።

ቻይናን የቴክኖሎጂ ልዕለ ኃያል ማድረግ የፕሬዚዳንት ዢ ጂንፒንግ የረዥም ጊዜ ምኞት ሆኖ ቆይቷል። የዋሽንግተን እገዳንም ቤጂንግ በዚህ መልኩ የተቀበለችው ፈተና ሆኗል።

ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከሰው ሠራሽ አስተውሎት ኩባንያ መሪዎች ጋር

የፎቶው ባለመብት, EPA

የተደበላለቀ አስተያየት

ዲፕሲክ ወደ ሥራ ከገባ በኋላ የበርካታ ቴክኖሎጂ ኩባንያዎች አክሲዮን ተሽመድምዷል።

ለምሳሌ የኒቪዲያ አክሲዮኖች ድርሻ ሰኞ ዕለት በተጠናቀቀው የአሜሪካ ገበያ በ17 በመቶ ቀንሷል።

ይህም የ600 ቢሊዮን ዶላር ዋጋ መቀነስ ያሳየ ሲሆን በአሜሪካ የስቶክ ገበያ ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ መሆኑን ብሉምበርግ አስታውቋል።

ታዋቂው አሜሪካ የሶፍትዌር መሓንዲስ ማርክ አንድሬሴን "ዲፕሲክ-አር1ን ልክ የጠፈር ውድድር የተጀመረበትን አጋጣሚ ጋር በማወዳደር "የሰው ሠራሽ አስተውሎት መተግበሪያውን ከስፑትኒክ አጋጣሚ ጋር በማወዳደር ነው ኤክስ ገጻቸው ላይ የጻፉት

የቻይናው የሰው ሰራሽ አስተውሎት መተግበሪያ በብዙዎች ዘንድ ስጋቶችን አስነስቷል።

የዲፕሲክን የፋይናንስ ዘገባ በመጥቀስ "እየሆነ ያለውን ነገር በተመለከተ እውነቱ የተደበቀ ይመስለኛል" ሲሉ አንጋፋው ተንታኝ ጂን ሙንስተር ለቢቢሲ ተናግረዋል። ድጎማ ተደርጎለታል ወይም ደግሞ የተዘገበው ቁጥሩ ትክክል ስለመሆኑ ጥያቄ እንደሚያስነሳ ገልጸዋል።

"የሰው ሰራሽ አስተውሎት መተግበሪያው በሚያስደንቅ ሁኔታ ጥሩ በመሆኑ ይህም ለማመን አዳጋች ያደርገዋል" ብለዋል።

የአውስትራሊያ የሳይንስ ሚኒስትር ኤድ ሁሲች የደህንነት ስጋቶችን ጠቁመዋል።

"በጥራት፣ በተጠቃሚ ምርጫዎች፣ በመረጃ እና በግላዊነት አስተዳደር ላይ በጊዜ ምላሽ የሚሹ ብዙ ጥያቄዎች አሉ። ስለዚያ በጣም መጠንቀቅ ያስፈልጋል። እነዚህ አይነት ጉዳዮች በጥንቃቄ መመዘን አለባቸው" ሲሉ ለኢቢሲ ተናግረዋል።

ባለፈው ሳምንት የኦፕን ኤአዩ ሳም አልትማን እና የኦራክሉ ላሪ ኤሊሰን ከፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ጋር በመሆን ስታርጌትን ይፋ አድርገዋል።

ለኤአይአይ መሠረተ ልማት በጋራ ሽርክና እስከ 500 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ ፋይናንስ የሚደረግበት፤ በቴክሳስ እና በሌሎች አካባቢዎች የመረጃ ማዕከላት የሚኖሩት እና ከ 100 ሺህ በላይ አዳዲስ የሥራ እድሎችን የሚፈጥር ፕሮጀክት ነው።

ዲፕሲክ በድንገት መምጣቱ ስለወደፊቱ የአሜሪካ የሰው ሠራሽ አስተውሎት የበላይነት እና የአሜሪካ ኩባንያዎች እያቀዱ ስላሉት የኢንቨስትመንት መጠን ጥያቄዎችን ሊያስነሳ እንደሚችል አንዳንድ ባለሙያዎች ያምናሉ።