ዩኬ ለአሜሪካ ድጋፍ ማድረጓን ስትገልፅ ሩሲያ የአሜሪካን ተግባር ኮንናለች

የፎቶው ባለመብት, US EUROPEAN COMMAND
የሩሲያ ትራንስፖርት ሚኒስትር “የትኛውም ሀገር በአንድ ሀገር የተመዘገበ መርከብን በኃይል የመያዝ መብት የለውም” የሚል መግለጫ አውጥቷል።
በቀድሞ ስሙ ቤላ 1 ተብሎ የሚታወቀው የነዳጅ መርከብ በአሜሪካ ቁጥጥር ስር መዋሉን ተክተሎ ነው ሩሲያ መግለጫ ያወጣችው።
አሜሪካ ከቬንዙዌላ ነዳጅ ጋር ግንኙነት ያለው መርከብ ማዕቀብ ጥሷል በማለት አድና በቁጥጥር ሥር ማዋሏን አስታውቃለች።
ማሪኔራ ተብሎ የሚጠራው መርከብ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሩሲያ ባንዲራ ሲንቀሳቀስ የቆየ ሲሆን ሞስኮው መርከቡን ለማጀብ የባሕር ኃይሏን አሰማርታ ነበር።
የሩሲያ መግለጫ እንደሚጠቁመው በሞስኮው ሰዓት አቆጣጠር ከቀኑ 9 ሰዓት የአሜሪካ ኃይሎች መርከቧን በቁጥጥራቸው ስር ካዋሉ በኋላ ከመርከቡ ጋር የነበረው ግንኙነት ተቋርጧል ብሏል።
ሚኒስቴሩ አክሎ እንደገለፀው ማሪኔራ ከአውሮፓውያኑ ታኅሣሥ ወር መጀመሪያ ጀምሮ “በጊዜያዊ ፈቃድ” በሩሲያ ባንዲራ ሲንቀሳቀስ ነበር።
በተያያዘ ዜና ዩናይትድ ኪንግደም አሜሪካ መርከቡን በቁጥጥር ሥር እንድታውል ድጋፍ ማድረጓን አስታውቃለች።
የዩኬ መከላከያ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ መርከቡ በሰሜን አትላንቲክ በቁጥጥር ሥር እንዲውል ድጋፍ ማድረጉን አስታውቆ “መርከቡ ሩሲያ እና ኢራን ማዕቀብ ጥሰው ከመካከለኛው ምስራቅ እስከ ዩክሬን ሽብርን፣ ግጭት እና መከራን የሚያስፋፉበት ነው” ብሏል።
አሜሪካ ከዚህ መርከብ በተጨማሪ ሌላ ቬንዙዌላ ላይ የተጣለ ማዕቀብ የጣሰ ነው ያለችውን መርከብ ካሬቢያን ላይ በቁጥጥር ስር ማዋሏን አስታውቃለች።




















