አሜሪካዊው የምክር ቤት አባል ሽጉጥ ተደግኖባቸው መኪናቸው ተዘረፈ

የአሜሪካ የምክር ቤት አባል ሄንሪ ኩሌር

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የአሜሪካ የምክር ቤት አባል ሄንሪ ኩሌር ሽጉጥ ተደግኖባቸው መኪናቸው እንደተዘረፈ የአገር ውስጥ ሚዲያዎች ዘግበዋል።

የምክር ቤቱ አባል መኪናቸው የተሰረቀው ሰኞ ማምሻውን መስከረም 21/2016 ዓ.ም በዋሸንግተን መሆኑ ተነግሯል።

የቴክሳስ ግዛት የዴሞክራት ፓርቲ ተወካዪ ከአሜሪካ የካፒቶል ህንጻ በ1.6 ኪሎሜትር ርቀት ላይ መኪናቸውን አቁመው የነበረ ሲሆን ሦስት የታጠቁ ግለሰቦችም ሽጉጥ ደግነው መኪናቸውን እንደወሰዱ ተነግሯል።

የምክር ቤቱ አባል ጉዳት ያልደረሰባቸው ሲሆን ተሽከርካሪያቸውም በኋላ ተገኝቷል።

የካፒቶል ፖሊስ እንዳስታወቀው መርማሪዎች ተጠርጣሪዎቹን ለማግኘት ክትትል እያደረጉ እንደሆነ ነው።

ዘረፋው የተከሰተው በከተማዋ ደቡብ ምስራቅ የባህር ኃይል ቅጥር ግቢ ውስጥ ከአመሻሹ ሦስት ሰዓት ተኩል ላይ ነበር።

ከመኪናቸው በተጨማሪ ስልክ እና አይፓዳቸውም እንደተወሰደ የሄንሪ ኩለር ዋና ጸሐፊ ጃኮቭ ሆችበርግ ተናግረዋል። ስልክ እና አይፓዳቸው ስለመመለሱ ግልጽ የሆነ ነገር የለም።

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በዋሽንግተን የሚፈጸሙ የመኪና ዝርፊያዎች እየጨመሩ ሲሆን ከሁለት ዓመታት በፊት የአካባቢው ፖሊስ ችግሩን ለመፍታት ግብረ ኃይል አቋቁሟል።

የፖሊስ የቅርብ ጊዜ መረጃ እንደሚያመለክተው በዚህ ዓመት በከተማው ውስጥ 750 መኪኖች የተዘረፉ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ 75 በመቶ የሚሆኑት በጦር መሳሪያዎች ታግዘው ነው።

ሄንሪ ኩለር በአሜሪካ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቴክሳስን ግዛት በመወከል ለ10ኛ ዓመት እያገለገሉ ይገኛሉ።