ሜጀር ጄኔራል ገብረመድኅን ፈቃዱ (ወዲ ነጮ) በድንገት ሕይወታቸው አለፈ

የፎቶው ባለመብት, ENDF TV
በትግራይ የተቀሰቀሰውን ጦርነት ተከትሎ በእስር ላይ የነበሩት ሜጀር ጄነራል ገብረመድኅን ፈቃዱ ባልታወቀ ምክንያት ሕይወታቸው አለፈ።
በአገር መከላከያ ሚኒስቴር የኮምዩኒኬሽን ኤሌክትሮኒክስ ሳይበር ዋና መምርያ ኃላፊ የነበሩት ሜጀር ጄኔራል ገብረመድኅን (በትግል ስማቸው ወዲ ነጮ) ዛሬ ሰኞ ሚያዝያ 24/2014 ዓ. ም. ባልታወቀ ምክንያት ሕይወታቸው ማለፉን የቤተሰባቸው አባላት፣ ጠበቃቸው እና የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች ለቢቢሲ አረጋገጠዋል።
የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን ስለ ግለሰቡ ህልፈት፣ በቃሊቲ ከፍተኛ ጥበቃ ማረሚያ ማዕከል የቀጠሮ እስረኛው ሰኞ ጠዋት 3፡30 ገደማ "ባለቤታቸው እና ልጃቸው አስጠርተዋቸው እያወሩ እያለ በድንገት መውድቃቸውን" ገልጿል።
ይህንንም ተከትሎ ወድያውኑ ከቤተሰቦቻቸው ጋር ወደ ሕክምና ቦታ ቢወሰዱም ሕይታቸው ያለፈ መሆኑን የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን ገልጿል፡፡
የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን ጨምሮም የሜጀር ጄኔራል ገብረመድኅን ህልፈት ምክንያት ምን እንደሆነ ለማወቅ አስክሬናቸው ለተጨማሪ ምርመራ ወደ ሕክምና ተቋም መላኩን አመልክቷል።
ቀደም ሲል የአግአዚ ክፍለ ጦር ኣዛዥ የነበሩት ሜጀር ጄኔራል ገብረመድኅን፣ በአገር መከላከያ ሚኒስቴር የኮምዩኒኬሽንን ኤሌክትሮኒክስ ሳይበር ዋና መምርያ ኃላፊ በነበሩበት ጊዜ ከሰሜን ዕዝ ጋር የነበረው ወታደራዊ የሬዲዮ ግንኙነት እንዲቋረጥ አድርገዋል በሚል በአገር ክህደት ወንጀል ተከሰው እስር ቤት ሆነው ጉዳያቸውን እየተከታተሉ ቆይተዋል።
ቢቢሲ የሜጀር ጄኔራል ገብረመድኅንን ባለቤትን በስልክ ለማነጋገር የሞከረ ሲሆን፣ ማናገር ስላልቻሉ የባለቤታቸው እህት ወ/ሮ አፀደ የጄነራሉ ሞት እውነት መሆኑን አረጋግጠዋል።
ጄነራሉ ታስረው በቆዩበት በቃሊቲ እስር ቤት ሕይወታቸው ማለፉን አረጋገጠው፣ ሆኖም በምን ምክንያት ለሞት እንደበቁ እንደማያውቁ ተናግረዋል።
"አዎ፤ ዛሬ ጠዋት ነው ሕይወቱ ያለፈው። በዚያው በቃሊቲ እስር ቤት ውስጥ ነው የሞተው" ሲሉ የባለቤታቸው እህት ለቢቢሲ ገልጸዋል።
ከዚህ በፊት ጄነራሉ ታመው እንደማያቁ እና ጤነኛ እንደነበሩም ተናግረዋል።
ቢቢሲ ያነጋገራቸው የጄኔራሉ ጠበቃ ዛሬ የፍርድ ቤት ቀጠሮ እንደነበራቸውና በበዓሉ ምክንያት ወደ ነገ የተላለፈውን የፍርድ ቤት ቀጠሮ ሲጠባበቁ እንደነበረና ደንበኛቸውን ባለፈው ሐሙስና አርብ ሲያገኘዋቸው ሙሉ ጤነኛ እንደነበሩ አብራርተዋል።
የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ገረመው አያሌው በበኩላቸው፣ "ልክ ነው [ጄነራሉ] ሕይወታቸው አልፏል። ቤተሰብ ጥየቃ ላይ ነበሩ። ከባለቤታቸውና ከልጃቸው ጋር እያወሩ ሳለ ነው ድንገት የወደቁት። ቤተሰቦችም ጭምር አንድ ላይ ሆነው ወደ ሕክምና በሚወሰዱበት ጊዜ ሕይወታቸው አልፏል" በማለት ለቢቢሲ አስረድተዋል።
ለጄነራሉ ህልፈት ምክንያቱ ምን እንደሆነ የተጠየቁት አቶ ገረመው "የሕክምና መረጃ እየጠበቅን ነው" በማለት ምክንያቱ ምን እንደሆነ እንደማያውቁ ተናግረዋል።
ከ1975 ዓ. ም. ጀምሮ የደርግ ሥርዓትን ለመደምሰስ በነበረው ትግል የትግራይ ሕዝብ ወደሚያካሂደው ሕዝባዊ ትግል የተቀላቀሉት ሜጄር ጄነራል ገብረመድኅን ወይም ወዲ ነጮ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት የ21ኛው ክፍለ ጦር አዛዥ በመሆን በገማህሎ ግንባር ዘመቻ ፀሐይ ግብአት፣ ሰምበል፣ ባድመ ከመሩ ወታደራዊ መኮንኖች አንዱ እንደነበሩ ይነገራል።
ሜጀር ጄኔራል ገብረመድኅን፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ወደ ሥልጣን ከመምጣታችው በፊት የአግአዚ ክፍለ ጦር ኣዛዥ የነበሩ ሲሆን፣ ከዚያም እስከታሰሩበት ጊዜ ድረስ ደግሞ በአገር መከላከያ ሚኒስቴር የኮምዩኒኬሽንና ኤሌክትሮኒክስ ሳይበር ዋና መምርያ ኃላፊ ነበሩ።
ጄኔራሉ ከዚህ ባሻገር የአግአዚ ሰራዊት ኮማንዶ በመሆን በጸረ አልሸባብ ትግል ሶማሊያ ተሳትፎ አድርገዋል። ከሶማሊያ ከተመለሱ በኃላ ደግሞ 6ኛ መካናይዝድ ክፍለ ጦር የኅብረት ወታደራዊ ኮሌጅ ኃላፊ ነበሩ።
ከፍተኛ የውጊያ ክህሎት እንደነበራቸው ይነገርላቸው የነበሩት ጄኔራሉ ከኮማንድ ስታፍ ኮሌጅ በሊደርቪፕና ወታደራዊ ሳይንስ የመጀመርያ ዲግሪ አግኝተዋል።
ባለትዳርና የሦስት ልጆች አባት ነበሩ።
ባለፈው ዓመት ትግራይ ውስጥ የተቀሰቀሰውን ጦርነት ተከትሎ በከፍተኛ የአገር ክህደት ወንጀል ከተከሰሱት የፖለቲካና ወታደራዊ ባለሥልጣናት መካከል ሜጀር ጄኔራል ገብረመድኅን አንዱ ናቸው።












