በፍጥነት እየመጣ ወደነበረ ባቡር በኤርትራዊው የተገፈተረው ታዳጊ ህይወቱ አለፈ

በፍራንክፈርት ታዳጊውን የገጨው ባቡር

የፎቶው ባለመብት, AFP

የምስሉ መግለጫ, በፍራንክፈርት ታዳጊውን የገጨው ባቡር

የስምንት ዓምት ታዳጊ እና ወላጅ እናቱ በፍጥነት እየመጣ ወደነበረ ባቡር ተገፍትረው ልጁ ህይወቱ ወዲያው ሲልፍ እናቲቱ ደግሞ ጉዳት ደርሶባት ወደ ሆስፒታል ተወሰዳለች።

በጀርመን ፍራንክፈርት ሁለቱን የቤተሰብ አባላት ገፍትሯል ተብሎ የተጠረጠረው ግለሰብ የ40 ዓመት ጎልማሳ ኤርትራዊ መሆኑን ፖሊስ አስታውቋል።

ግለሰቡ እናትን እና ልጅን በፍጥነት እየመጣ ወደነበረ ባቡር ለምን እንደገፈተራቸው ባይታወቅም፤ ድርጊቱን ፈጽሞ በሩጫ ሊያመልጥ ሲል በባቡር ጣቢያው አከባቢ የነበሩ ሰዎች አሯሩጠው እንደያዙት እና ለፖሊስ አሳልፈው እንደሰጡት ሬውተርስ ዘግቧል።

የዓይን እማኞች እንዳሉት ግለሰቡ በግልጽ ሆነ ብሎ እናት እና ልጅን ወደ ባቡር ሃዲዱ ገፍትሯቸዋል። በተጨማሪም ሶስተኛ ሰውን ለመገፍተር ሙከራ አድርጎ እንደነበር የዓይን እማኞች ተናገረዋል።

የፖሊስ ቃል አቀባይ ሲናገሩ፤ "እናት እና ልጅ በፍጥነት እየተቃረበ ወደነበረ ባቡር ተገፍትረዋል። እናቲቱ እራሷን ማዳን ችላለች" ብለዋል።

ፖሊስ ጨምሮም በግድያ ወንጀል ምረመራ መጀመሩን አስታውቋል። መርማሪ ፖሊሶች እንዳሚሉት ግለሰቡን ድርጊቱን ለመፈጸም ምን እንዳነሳሳው እስካሁን ግልጽ ባይሆንም፤ ተጠርጣሪው ከእናት እና ልጅ ጋር ትውውቅ አለው ብዬ አላስብም ብለዋል።

ለህክምና ወደ ሆስፒታል የተወሰደችው እናት የደረሰባት የጉዳት መጠን አልታወቀም።

እረፍት ላይ የነበሩት የሃገር ውስጥ ሚንስትሩ ከዜናው በኋላ ወደ ሥራ የተመለሱ ሲሆን፤ በጉዳዩ ላይ ከከፍተኛ የደህንነት ኃላፊዎች ጋር እወያያለሁ ብለዋል።

የሃገር ውስጥ ሚንስትሩ ሆረስት ሲሆፈር "የዚህ ጭካኔ የተሞላበት ወንጀል ጀርባ ያለው ምን እንደሆነ እስካሁን ግልጽ አይደለም" ብለዋል።