ታዋቂዎቹ ኤርትራዊያን ስለስደት በሰሩት ሙዚቃ ይቅርታ ጠየቁ

የፎቶው ባለመብት, Semhar
ሁለት ታዋቂ ኤርትራዊያን ድምፃዊያን ስደተኞችን በተመለከተው ዘፈናቸው ምክንያት ይቅርታ ጠየቁ።
እህትማማቾቹ ድምፃዊያን፤ ዳናይት እና ሰምሃር ይቅርታ የጠየቁት ሙዚቃው ከተለቀቀ ከሁለት ዓመታት በኋላ ሲሆን ስደተኞች ለሃገራቸው ፍቅር እንዳላሳዩ በሚያመለክተው ዘፈናቸው ምክንያት ከአድናቂዎቻቸው ተቃውሞ ስለገጠማቸው ነው።
አድናቂዎቻቸው እንደሚሉት ድምፃዊያኑ የወጣቶችን ለውትድርና መመልመልን ጨምሮ በኤርትራ ስላለው አስቸጋሪ ሁኔታ ችላ ብለው በርካታ ኤርትራዊያንና አፍሪካዊያን ወደ አውሮፓ ለመግባት በሚጓዙበት የሜዲትራኒያን ባሕር ላይ የሚሰምጡ ሰዎችን በሙዚቃ ቪዲዮዋቸው ላይ በማሳየት ግድየለሽ ሆነዋል በሚል ነው የሚከሷቸው።
ድምፃዊያኑ መጀመሪያ የገጠማቸውን ተቃውሞ የተቋቋሙት ቢሆንም ሰምሃር ስለ ፍቅር የሚያወራ ያወጣችውን አዲስ ሙዚቃ ተከትሎ የህዝቡ ቁጣ አገርሽቷል።
ምንም እንኳን አዲሱ ዘፈን ስለ ፖለቲካና ስደት ምንም የሚለው ባይኖርም ቀደም ሲል በሰሩት ዘፈን ላይ ተቃውሞው መልሶ እንዲቀሰቀስ አድርጓል።
አዲስ በወጣውና በዩቲዩብ በተለቀቀው ሙዚቃ የአስተያየት መስጫ ላይም ከሁለት ዓመት በፊት ያወጡትን ሙዚቃ የተመለከተ ከአምስት ሺህ በላይ ቅሬታዎች ቀርበውበታል።
በመሆኑም ድምፃዊያዊያኑ በሙዚቃው የአድናቂዎቻቸውን ስሜት በመጉዳታቸው በይፋ ይቅርታ መጠየቃቸውን ለቢቢሲ ገልፀዋል።
አክለውም "ጥረታችንን እንዲጠሉት ሳይሆን፤ ሰዎች ሥራዎቻችንን እንዲወዱልን እንፈልጋለን" በማለት አድናቂዎቻቸውን ለመጉዳት ብለው ሙዚቃውን እንዳልሰሩት ተናግረዋል።
ድምፃዊያኑ የአንጋፋው ኤርትራዊ ድምፃዊ ዮሐንስ እስጢፋኖስ ልጆች ናቸው።













