ትላልቅ የኤሌክትሪክ ማመንጫ ግድቦች ለታዳጊ ሃገራት "አዋጭ አይደሉም"

oroville dam

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የምስሉ መግለጫ, ካሊፎርኒያ በሚገኘው ኦሮቪል ግድብ ላይ በደረሰ ችግር 10 ሺህ ሰዎች ከቀዬአቸው ተፈናቅለዋል

አዲስ ይፋ የተደረገ ጥናት እንዳመለከተው በአውሮፓ እና በአሜሪካ ያሉ በርካታ ትላልቅ የውሃ ኃይል ፕሮጀክቶች አካባቢ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ነበራቸው።

አደገኛ እና ኢኮኖሚያዊ እንዳልሆኑ ስለተገመተም ከእነዚህ ግድቦች ውስጥ ብዙዎቹ በየዓመቱ ሥራ እንዲያቆሙ ይደረጋል።

ይሁን እንጂ በማደግ ላይ ባሉት ሀገራት ውስጥ እነዚህ ፕሮጀክቶች ዘላቂነት እንደሌላቸው አይታወቅም በሚል አጥኚዎች ስጋታቸውን ያስቀምጣሉ።

በአሁኑ ጊዜ በሺዎች የሚቆጠሩ አዳዲስ ግድቦችን በአፍሪካ እና በኤስያ በሚገኙ ወንዞች ላይ ለመገንባት እየታቀደ ነው።

በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚገኘው የታዳሽ ኃይል 71 በመቶ የሚሆነው ከውሃ የሚገኝ ኃይል ሲሆን ለበርካታ ሀገሮች ዕድገትም ትልቅ ሚና ተጫውቷል።

ይሁን እንጂ በአውሮፓና በአሜሪካ ግድቦችን መገንባት በአውሮፓዊያኑ 1960ዎቹ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ቢደርስም፤ ከዚያን ጊዜ ወዲህ ግን በተቃራኒው እየቀነሰ ከመምጣቱም በላይ ከመገንባት ይልቅ ማፍረስ ላይ ትኩረት ተደርጓል ይላሉ አጥኚዎቹ። አሜሪካ ከውሃ ኃይል የምታገኘው የኤሌክትሪክ ኃይል 6 በመቶ አካባቢ ነው።

በአሁኑ ጊዜ በአትላንቲክ ውቅያኖስ ሁለቱም ጫፎች በሳምንት ከአንድ ግድብ በላይ ከሥራ ውጭ እንዲሆን ይደረጋል።

ከአካባቢ እና ከማህበራዊ ኪሣራው ይልቅ መንግሥታት በጭፍን በርካሽ በሚያገኙት የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ላይ ብቻ አተኩረዋል ይላሉ የጥናቱ ጸሐፊዎች።

በአውሮፓዊያኑ ከ1930ዎቹ ጀምሮ ከተገነቡት ግድቦች ውስጥ 90 በመቶ የሚሆኑት ከተጠበቀው በላይ ወጪ የጠየቁ ነበሩ። የወንዞችን ​​ሥነ-ምህዳር ያበላሹ፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ከቀያቸው ያፈናቀሉ እና በጎርፍ የሚጠረግ አፈር እና የተመነጠሩ ደኖች በግድቦቹ ውስጥ በሚፈጥሩት የግሪን ሃውስ ጋዞች ለአየር ሁኔታ ለውጥ አስተዋፅኦ ያደረጉ ነበሩ።

Elwah river dam

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የምስሉ መግለጫ, የዋሽንግተኑ የኤልውሃ ወንዝ ግድብ በአውሮፓዊያኑ 2011 ሥራ እንዲያቆም ተደርጓል

"የማይሳኩ ነገር ግን ጥቅሞቹን የሚያንቆለጳጵሱ መረጃዎች የሚያቀርቡ ሲሆን የተዘነጉ ነገር ግን በቀጣይ ለትውልድ የሚተላለፉ ወጪዎቹም ችላ ይባላሉ" ሲሉ የጥናቱ መሪ የሆኑት የሚቺጋን ስቴት ዩኒቨርሲቲው ፕሮፌሰር ኤሚሊዮ ሞራን ለቢቢሲ ተናግረዋል።

ሪፖርቱ በምሳሌነት ከአምስት ዓመታት በፊት አገልግሎት የጀመሩትን በብራዚል ማዴራ ወንዝ ላይ የተገነቡትን ሁለቱን ግድቦች ያነሳል። ግድቦቹ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት ከሚጠበቀው የኃይል መጠን የተወሰነውን ብቻ ነው እያመረቱ የሚገኙት።

በአሁኑ ወቅት በማደግ ላይ በሚገኙ ሃገሮች ውስጥ የተለያየ መጠን ያላቸው 3,700 ግድቦች በተለያየ የግንባታ ደረጃዎች ላይ ይገኛሉ።

እንደአጥኚዎቹ ከሆነ አብዛኛዎቹ ትላልቅ ፕሮጀክቶች በሚገነቡባቸው ወንዞች ላይ መልሶ የማይስተካከል ጉዳት ያደርሳሉ።

በኮንጎ ወንዝ ላይ በሚገነባው የግራንድ ኢንጋ ፕሮጀክት ከአፍሪካ ጠቅላላ የኤሌክትሪክ ኃይል ከአንድ ሦስተኛ በላይ የሚሆን ኃይል ያመርታል ተብሎ ይጠበቃል።

አዲሱ ጥናት እንደሚያመለክተው ከሆነ የ80 ቢሊዮን ዶላሩ ፕሮጀክት ዋና ግብ ለኢንዱስትሪዎች ኃይል ለማቅረብ ነው።

"ከዚህ ፕሮጀክት ከሚገኘው ኃይል ከ90 በመቶ በላይ የሚሆነው ለደቡብ አፍሪካ የሚሸጥ ሲሆን ይህም ለማዕድን ፍለጋ ይውላል። ስለዚህም የኮንጎ ህዝብ ብዙ ኃይል አያገኙም" ይላሉ ፕሮፌሰር ሞራን።

"በብራዚል ጥናት ባደረኩባቸው ቦታዎች ያሉ ሰዎች የኤሌክትሪክ ኃይል ለእነሱ ሳይደርስ ከ4ሺህ ኪሎ ሜትር በላይ በእነሱ በኩል ቢያልፍም ለአካባቢው ነዋሪዎች ግን ምንም ዓይነት ኃይል አልተሰጣቸውም።"

hoover dam

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የምስሉ መግለጫ, በአሜሪካ የሚገኘው የሁቨር ግድብ ባለፉት ዓመታት የውሃ መጠኑ እየቀነሰ ነው

"በገጠር ኤሌክትሪክን በማስፋፋት ውስጥ ያለው መልካም ግብ ይህንን ቴክኖሎጂ በሚደግፉ ትላልቅ ፍላጎቶች ተዳክሟል። መንግሥታትም ትክክለኛው አቅጣጫ እንደሆነ በማረጋገጥ በዚህ ሃሳብ ተስማምተዋል።"

ሪፖርቱ እንደሚያመለክተው ከሆነ በእነዚህ ታላላቅ ወንዞች ላይ የሚገነቡት ትላልቅ ኃይል ማመንጫዎች የምግብ ምንጮችን ያጠፋሉ።

በሜኮንግ አካባቢ የሚኖሩ 60 ሚሊዮን ሰዎች ከሁለት ቢሊዮን ዶላር በላይ የሚገመት የኑሮ መሠረታቸው የሆነውን የአሣ ምርት ሊያጡ ይችላሉ። በተጨማሪም የብዝሃ ሕይወት መገኛ የሆኑት እነዚህ ቦታዎች ውስጥ የሚገኙ በሺህዎች የሚቆጠሩ ዝርያዎችን ግድቦቹ ያጠፋሉ ብለው አጥኚዎቹ ያምናሉ።

ከውሃ የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ 67 በመቶውን የኤሌክትሪክ ኃይሏን በምታገኘው በብራዚል በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የውሃ መጠን በመቀነሱ ምላሽ እንዲሆን የተደረገው ተጨማሪ ግድቦችን መገንባት ነው።

ጃየር ቦልሶናሮ በመመረጣቸው ለጊዜው ተቋርጦ የነበረው አዲስ የሃይድሮ ኃይል ፕሮጄክት የመገንባት ሥራ ሊቀለበስ ይችላል። አዳዲስ 60 ግድቦች ለመሥራት ዕቅድ ተዘጋጅቷል።

አጥኚዎቹ እንደገለፁት አገራት ታዳሽ ኃይልን እንዲያስፋፉ ካለባቸው ትልቅ ተጽዕኖ አንጻር ከውሃ የሚገኘውን ጨምሮ የተለያዩ የኃይል አማራጮችን መከተል ዘላቂነት ያለው አቀራረብ ነው ይላሉ።

"ትላልቅ የሃይድሮ ኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫዎች አዋጭነት የላቸውም የሚል ነው የእኛ መደምደሚያ" ይላሉ ፕሮፌሰር ሞራን።

"በ21ኛው ክፍለ ዘመን የሃይድሮኤሌክትሪክ ኃይልን ጨምሮ የተለያዩ የታዳሽ ኃይል ማመንጫዎች ማሰባጠር አለብን" ብለዋል ፕሮሰር ሞራን።

"ወደ ከፍተኛ ደረጃ እስክንደርስ ድረስ ለፀሃይ፣ ለንፋስ እና ለባዮማስ እንዲሁም ወጪና ጥቅሙ ግልጽ እስከሆነ ድረስ ከውሃ ለሚገኝ የኃይል ማመንጫ ተጨማሪ ኢንቨስትመንት ያስፈልጋል።"

ጥናቱ በፕሮሲዲንግ ኦፍ ዘ ናሽናል አካዳሚ ኦፍ ሳይንስ ላይ ነው የታተመው።