ቱርክ ለሁለት ዓመት የዘለቀውን አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አነሳች

የቱርክ ፕሬዚዳንት ጣይብ ኤርዶዋን

የፎቶው ባለመብት, Reuters

የቱርክ መንግሥት የኤርዶዋን አገዛዝ ላይ ከተሞከረው መፈንቅለ-መንግሥት መክሸፍ ጋር ተያይዞ አውጆት የነበረውን የአስቸኳይ ጊዜ ማዕቀብ ከሁለት ዓመት በኋላ ማንሳቱን አስታውቋል።

የቱርክ መንግሥት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ወቅት 10 ሺዎችን ወደ ከርቸሌ መወርመወሩ የሚታወስ ነው፤ 100 ሺዎችን ደግሞ ከመፈንቅለ-መንግሥቱ ጋር በተገናኘ ከሥራ ገበታቸው እንዲፈናቀሉ ሆነዋል።

መባቻው ላይ ለሶስት ወራት ብቻ ታውጆ የነበረው ይህ አዋጅ ሰባት ጊዜ ያህል እንዲራዘም ተደርጓል።

ፕሬዝደንት ረሲፕ ጣይብ ኤርዶዋን ለሁለተኛ ጊዜ ምርጫ ካሸነፉ ሳምንታት በኋላ ነው የአዋጁ ተግባራዊነት እንዲቋረጥ ያዘዙት።

በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት የኤርዶዋን ዋነኛ ተቀናቃኝ የሆኑ ዕጩዎች ከተመረጡ አዋጁን እንደሚሽሩት ቃል ገብተው ነበር።

107 ሺህ ገደማ የመንግሥት ሠራተኞች በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ወቅት ከሥራቸው የታገዱ ሲሆን ከ50 ሺህ በላይ የሚሆኑቱ ደግሞ ለእሥር ተዳርገዋል።

ለእሥር የተዳረጉትም ሆኑ ለሥራ የተሰናበቱት ነዋሪነታቸውን አሜሪካ ካደረጉት ልጥጡ ፌቱላህ ጉሌን ጋር ግንኙት አላቸው፤ እርሳቸውንም ይደግፋሉ ተብለው ነው።

ቱጃሩ ጉሌን የኤርዶዋን የቀድሞ አጋር ሲሆኑ መፈንቅለ-መንግሥቱን አቀነባብረዋል ሲል የቱርክ መንግሥት ይከሳቸዋል።

250 ሰዎች ሕይወታቸውን ባጡበት የቱርክ መፈንቅለ-መንግሥት ሙከራ ወቅት አንድ የጦር አውሮፕላን የሃገሪቱን ፓርላማ ማጋየቱ ይታወሳል።