አሜሪካ ከሶሪያ አማጺያን ጋር "ቀጥተኛ ግንኙነት" ማድረጓን አስታወቀች

የፎቶው ባለመብት, Reuters
አሜሪካ ከሶሪያ አማጺያን ጋር "ቀጥተኛ ግንኙነት" ማድረጓን አስታወቀች።
የባሻር አል-አሳድን መንግሥት ያስወገደው ኤችቲኤስ ሶሪያን ቶቀጣጥሯል። የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ኃላፊ አንቶኒ ብሊንከን እንዳሉት አሜሪካ ከዚህ ቡድን ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት አድጋለች።
ከቡድኑ ጋር አሜሪካ ቀጥተኛ ግንኙነት ማድገጓ በይፋ ሲገለጽ ይህ የመጀመሪያው ነው።
አሜሪካ ቡድኑን አሸባሪ ብላ ፈርጃለች።
ብሊንከን ዮርዳኖስ ውስጥ ከበርካታ የአረብ አገራት ተወካዮች፣ ከአውሮፓና ቱርክ መሪዎች ጋር ንግግር አድርገዋል።
በሶሪያ ሰላማዊ የሽግግር ሂደትን እንደሚደግፉ መሪዎቹ ተናግረዋል።
የዮርዳኖስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የቀጠናው አገራት ሶሪያ "ወደ ቀውስ ስትመለስ ማየት አይሹም" ብለዋል።
ሁሉን አቀፍ መንግሥት በሶሪያ እንዲመሠረት ጠይቀዋል።
የሚመሠተው መንግሥት "ለሽብርተኛ ቡድኖች" ቦታ እንዳይሰጥ አሳስበዋል።
ከሶሪያ ውጭና ከአገሪቱ ውስጥም የሚሰማው ሁሉንም ሶሪያውያን ያቀፈ መንግሥት መመሥረት መቻል ነው።
በዩርዳኖስ በተካሄደው ውይይት የኢራቅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፉአድ ሑሴን እንዳሉት የቀጠናው መሪዎች ሌላ ሊቢያ ማየት አይሹም።
የቱርክ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሐካን ፊዳን በበኩላቸው ሶሪያ ለውጥ እንደሚያስፈልጋት ገልጸዋል።
"አሸባሪነት በሽግግር ሂደቱ ጣልቃ እንዲገባ አትፍቀዱ። ከቀደመው ስህተት ተምረን መተባበር አለብን" ብለዋል።
በሌላ በኩል እስራኤል በሶሪያ ላይ የአየር ጥቃት እየፈጸመች ነው። የቀጠናው አገራት ድርጊቱን ቢኮንንም እስራኤል ጥቃቱን ገፍታበታለች።
እስራኤል ከዚህ ቀደም "ስጋት ለመቀነስ ስትራቴጀያዊ ጥቃት" እንደምትፈጽም መግለጿ ይታወሳል።
ኤችቲኤስ ሁሉን አቀፍ መንግሥት መመሥረት ቢሻም የመጣበት ጂሃዲስት አቋም ጣልቃ ሊገባ ይችላል የሚሉ ስጋቶች ተስተጋብተዋል።
አሜሪካ እንዳለችው ከቡድኑ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ስታደርግ ከጠፋ ዓመታት የተቆጠው ጋዜጠኛ ኦስተን ቲስ ጉዳይ ተነስቷል።

የፎቶው ባለመብት, Reuters
"ከኤችቲኤስና ሌሎች ቡድኖች ጋር ግንኙነት ጀምረናል" ብለዋል ብሊንከን።
በዮርዳኖሱ ውይይት ላይ ከሶሪያ ተወካይ አልገተኘም።
ከስምንት አረብ አገራት የተገኙ ተወካዮች፣ ሶሪያ አንድ ሆና ማየት እንደሚፈልጉና ሃይማኖታዊና ቡድናዊ ክፍፍልን ማየት እንደማይሹ ተናግረዋል።
የአሳድ ደጋፊ የሆኑት ሩሲያ እና ኢራን በውይይቱ አልተገኙም።
ሶሪያ ውስጥ ሲዋጉ የነበሩ የውጭ ኃይሎች አሁንም በአገሪቱ ቀጣይ እጣ ፈንታ ሚና ሊኖራቸው ይችላል።
ሶሪያውያን ባለፈው ሳምንት ያጣጣሙት ነጻነት ቀጣይነት እንዲኖረው አማጺ ቡድኑ ከአገሪቱ ውስጥና ውጭም አንድነት ያስፈልገዋል።
ለ24 ዓመታት ሥልጣን ላይ የነበሩት አሳድ ከተወገዱ በኋላ ወደ ሩሲያ ሸሽተዋል።
አሳድ የዴሞክራሲ ጥያቄ ያነሱ ተቃዋሚዎችን በማፈናቸው ሰበብ ተነስቶ ለ13 ዓመታት በቆየው የእስር በእርስ ጦርነት በግማሽ ሚሊዮን በላይ ሰዎች ሲገደሉ ሌሎች ሚሊዮኖች ተፈናቅለል።
የውጭ አገራትም በዚህ ጦርነት ውስጥ ተሳትፎ አድርገዋል።
የአማጺያኑ መሪ አቡ መሐመድ አል-ጆውላኒ መሐመድ አል-ባሸርን ጊዜያዊ ጠቅላይ ሚኒስትር አድርጎ ሾሟል።
ኤችቲኤስ የአሳድ መንግሥትን ከሚቃወሙ ቡድኖች ጠንካራው ሲሆን የተባበሩት መንግሥታት፣ አሜሪካ፣ ቱርክና ሌሎችም አገራት ሽብርተኛ ብለውታል።












