ቀጥታ, ፕሬዝዳንት ትራምፕ የኢራን ጦርነት “ሁሉም ግብ” እስከሚሳካ ይቀጥላል አሉ፤ ሄዝቦላህ ወደ እስራኤል ሮኬት መተኮስ ጀመረ

የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ኢራን ላይ የተጀመረው “የውጊያ ዘመቻ በሙሉ ኃይል እና ሁሉም ግቦቻችን እስከሚሳኩ ድረስ ይቀጥላል” ሲሉ ተናግረዋል። ኢራን፤ እስራኤል ላይ የምታደርሰውን ጥቃት ቀጠለች ሲሆን በቴህራን የሚደገፈው ሄዝቦላህም ቴል አቪቭ ላይ ሮኬት በማስወንጨፍ ጦርነቱን ተቀላቅሏል። እስራኤልም በምላሹ በሊባኖስ የሚገኙ የቡድኑ ይዞታዎች ላይ ጥቃት ፈጽማለች።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በእስራኤል ጥቃት ቀኑን የጀመሩት የቤይሩት ነዋሪዎች ከተማውን ለቅቀው መውጣት ጀምረዋል

    ሊባኖስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የሊባኖስ ዋና ከተማ ቤይሩት ነዋሪዎች ሌሊት ዘጠኝ ሰዓት (በኢትዮጵያ ሰዓት አቆጣጠር ከሌሊቱ 10 ሰዓት) አካባቢ ላይ በመላው ከተማ በተሰማው የእስራኤል ተከታታይ ጥቃቶች በፈጠሩት የፍንዳታ ድምጽ ከተኙበት ነቅተዋል።

    እነዚህ ድምጾች የተሰሙት በኢራን የሚደገፈው ሄዝቦላህ የሮኬት ጥቃት የተፈጸመባት እስራኤል፤ የቡድኑ ይዞታዎችን ዒላማ ያደረገ ጥቃት መፈጸም በመጀመሯ ነው።

    ሄዝቦላህ ባወጣው መግለጫ ጥቃቱን የፈጸመው፤ በኢራኑ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ላይ የተፈጸመው ግድያ የአጸፋ ምላሽ ለመስጠት እንደሆነ አስታውቋል። እርምጃውንም “ሕጋዊ ራስን የመከላከል እርምጃ” ሲል ገልጾታል።

    የደቡባዊ ቤይሩት ነዋሪዎች በተሽከርካሪዎቻቸው ከመኖሪያቸው መሸሽ ጀምረዋል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የደቡባዊ ቤይሩት ነዋሪዎች በተሽከርካሪዎቻቸው ከመኖሪያቸው መሸሽ ጀምረዋል

    ሄዝቦላህ፤ “ትክክለኛ ዒላማቸውን የሚመቱ ሮኬቶችን እና በብዛት ተጉዘው ጥቃት የሚያደርሱ ድሮኖችን” በሰሜናዊ እስራኤል በሚገኝ የሚሳዔል መከላከያ ስፍራ ላይ ማስወንጨፉን ገልጿል። ለሄዝቦላህ ጥቃት ምላሽ መስጠት መጀመሩን ያረጋገጠው የእስራኤል ጦርም፤ ጥቃቱ “ሄዝቦላህ በዘመቻው ለመሳተፍ ያሳለፈው ውሳኔ ላይ” የሚፈጸም እንደሆነ አስታውቋል።

    ሄዝቦላህ፤ “ለእስራኤል መንግሥት ስጋት እንዲጋርጥ እና በሰሜን እስራኤል በሚገኙ ንጹኃን ላይ ጉዳት እንዲያደርስ” እንደማይፈቅድ ጠቅሷል። የእስራኤል ጦር ሊባኖስ ውስጥ ባሉ ከ50 በላይ መንደሮች ውስጥ የሚገኙ ነዋሪዎች አካባቢያቸውን ለቀው እንዲወጡ ትዕዛዝ ሰጥቷል።

    ይህንንም ተከትሎ አገሪቱ ዜጎች መኖሪያቸውን ለቅቀው እየወጡ ነው። ቤይሩት እና ሲዶን ከተሞች ውስጥ የሚገኙ ነዋሪዎች ለቅቀው በሚወጡበት ወቅት ከፍተኛ የትራፊክ መጨናነቅ መከሰቱን የሚያሳዩ ምሥሎች ወጥተዋል።

    ከአንድ ዓመት በላይ ቆየው እና እስራኤል በሄዝቦላህ ላይ ከፍተኛ ጥቃት የፈጸመችበት ውጊያን ለማስቆም በአውሮፓውያኑ 2024 በአሜሪካ አሸማጋይነት በተደረሰ ስምምነት እስራኤል እና ሊባኖስ፤የተኩስ አቁም ለማድረግ ተስማምተው ነበር። ኋላ ላይ ግን ተኩስ አቁሙ ለመጣሱ አንዳቸው ሌላኛቸውን ተጠያቂ አድርገዋል።

    እስራኤል ስምምነቱ ከተፈጸመም በኋላ፤ ከሄዝቦላህ ጋር ግንኙነት አላቸው ባለቻቸው የሊባኖስ ግዛቶች ላይ በየቀኑ በሚባል ደረጃ ጥቃት ስትፈጸም ቆይታለች።

    የእስራኤል አካባቢውን ለቅቆ የመውጣት ትዕዛዝ የተላለፈው ሌሊት ላይ ነው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል አካባቢውን ለቅቆ የመውጣት ትዕዛዝ የተላለፈው ሌሊት ላይ ነው
    ሳይዶን ከተማ ውስጥ ነዋሪዎች ለቅቀው ሲወጡ የትራፊክ መጨናነቅ ተከስቷል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ሳይዶን ከተማ ውስጥ ነዋሪዎች ለቅቀው ሲወጡ የትራፊክ መጨናነቅ ተከስቷል
  2. ሰበር, እስራኤል ከ50 በላይ በሚሆኑ መንደሮች የሚኖሩ ሊባኖሳውያን ለቅቀው እንዲወጡ አዘዘች

    የእስራኤልን ማስጠንቀቂያ የሰሙ ሊባኖሳውያን መኖሪያ አካባቢያቸውን በመልቀቅ እየወጡ ነው

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤልን ማስጠንቀቂያ የሰሙ ሊባኖሳውያን መኖሪያ አካባቢያቸውን በመልቀቅ እየወጡ ነው

    እስራኤል ጥቃት እንደምትፈጽም በመግለጽ ከ50 በላይ በሆኑ አነስተኛ ከተሞች እና መንደሮች የሚኖሩ ሊባኖሳውያን አካባቢያቸውን ለቅቀው እንዲወጡ አዘዘች።

    የእስራኤል ጦር ከለያቸው ከእነዚህ አከባቢዎች ነዋሪዎች ቢያንስ አንድ ኪሎ ሜትር እንዲርቁ አስጠንቅቋል።

    የእስራኤል ጦር ያስተላለፈው ማስጠንቀቂያ “ለራሳችሁ ደህንነት ሲባል ቤታችሁን በአስቸኳይ ለቅቃችሁ፣ ቢያንስ ከመንደራችሁ 1000 ሜትሮች ወደ ግልጽ ስፍራ እንድትሄዱ ይሁን" ይላል።

    “ማንኛውም የሄዝቦላህ አባላት፣ ተቋማት ወይንም ወታደራዊ ቁሳቁሶች ቅርብ የሆነ ሰው ሕይወቱን ለአደጋ ያጋልጣል” በማለት መንደሮቹን በዝርዝር አስፍሯል።

    የእስራኤል ጦርን ማስጠንቀቂያ የሰሙ ሊባኖሳውያን ከተጠቀሱት አካባቢዎች ለቅቀው እየወጡ ነው።

  3. የአሜሪካ፣ እስራኤል እና ኢራን ጦርነት የሦስተኛ ቀን ዋና ዋና ክስተቶች

    የእስራኤል የአየር መከላከያ ስርዓት ኢራን አሽኬሎን ውስጥ የተፈጸመችውን ጥቃት አክሽፏል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል የአየር መከላከያ ስርዓት ኢራን አሽኬሎን ውስጥ የተፈጸመችውን ጥቃት አክሽፏል

    አሜሪካ እና እስራኤል ከኢራን ጋር የጀመሩት ጦርነት ሦስተኛ ቀኑን አስቆጥሯል፤ ሁሉም ወገኖች ከፍተኛ የአየር ድብደባ መፈጸም ቀጥለዋል። በጦርነቱ ሦስተኛ ቀን ምን ተከሰተ?

    • ዶናልድ ትራምፕ በኢራን ላይ የተከፈተው “የማጥቃት ዘመቻ” “ሁሉም ግቦቻችን እስኪሳኩ ድረስ” ይቀጥላሉ ሲሉ በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት ገልጸዋል።
    • የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ በኢራን በተፈጸመ ጥቃት ሦስት አሜሪካ ወታደሮች መገደላቸውን እና አምስት ደግሞ የመቁሰል አደጋ እንደደረሰባቸው ካረጋገጠ በኋላ "ተጨማሪ" አሜሪካውያን ላይ ጉዳት ሊደርስ እንደሚችል ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናግረዋል።
    • ሰኞ ማለዳ ላይ ሄዝቦላህ ወደ እስራኤል ሮኬቶችን መተኮሱን ተከትሎ፤ ቴል አቪቭ የቡድኑ ዒላማዎች ናቸው ባለቻቸው በሊባኖስ የሚገኙ አካባቢዎች ላይ ላይ ጥቃት መሰንዘር ጀመራለች።
    • አሜሪካ እና እስራኤል፤ በኢራን በሚገኝ የሴቶች ትምህርት ቤት ላይ በፈጸሙት ጥቃት ቢያንስ 153 ሰዎች መገደላቸውን የአገሪቱ መንግሥት ገልጿል። የኢራን ፕሬዝዳንት ማስዑድ ፔዜሽኪያን ድርጊቱን "አረመኔያዊ " ሲሉ ጠርተውታል።
    • እስራኤል ከኢራን የተተኮሱ ሚሳዔሎች ቢያንስ ዘጠኝ ሰዎችን መግደላቸውን አሳውቃለች። ይህ ጦርነቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በእስራኤል ላይ የደረሰው ከፍተኛ የሟቾች ቁጥር ነው።
    • የተባበሩት አረብ ኤምሬትቶች ቅዳሜ ዕለት ኢራን በፈጸመችው ጥቃት ሦስት ሰዎች መሞታቸውን አስታውቃለች ፤ በባህሬን ፣ በኢራቅ ኤርቢል እና በዮርዳኖስ ከፍተኛ ፍንዳታዎችም መከሰታቸው ተገልጿል።
    • ሰኞ ጠዋት በእስያ የዓለም የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳይቷል።
    • የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር አሜሪካ የዩኬ ወታደራዊ ሰፈሮች በመጠቀም ጥቃቶችን እንድትፈጽም መፍቀዳቸውን አስታውቀዋል። ነገር ግን "አሁን የማጠቃት እርምጃውን አልተቀላቀልንም" ሲሉ ለሕዝባቸው ተናግረዋል።
    • በሳይፕረስ የሚገኘው የዩኬ የጦር ሠፈር በቆጵሮስ በሚገኝ አንድ የጦር ሰፈር ላይ ለተፈጸመ የድሮን ጥቃት ምላሽ መስጠቱን አረጋግጧል።
    ኢራን ዱባይ ውስጥ የምታደርሰውን ጥቃት ቀጥላለች

    የፎቶው ባለመብት, Bloomberg via Getty

    የምስሉ መግለጫ, ኢራን ዱባይ ውስጥ የምታደርሰውን ጥቃት ቀጥላለች