መሰረቁ ሳይታወቅ የቆየው ባለ500 ዓመት ዕድሜ ሥዕል ጣሊያን ውስጥ ተገኘ

የፎቶው ባለመብት, EPA
የ500 ዓመት ዕድሜ ያለው ሥዕል ጣልያን ውስጥ በሚገኝ መኖሪያ ቤት ተገኝቶ ወደ ሙዚየም የተመለሰ ሲሆን የሙዚየሙ ሠራተኞቹ ግን መሰረቁንም አላወቁም ነበር ተብሏል።
በሊዮናርዶ ዳ ቪንቺ ተስሏል ተብሎ የሚታመነው የሳልቫተር ሙንዲ የሥዕል ቅጂ ቅዳሜ ዕለት በኔፕልስ በሚገኝ አንድ መኝታ ቤት ቁም ሣጥን ውስጥ ተገኝቷል።
ይህ ቅጂ ከዳቪንቺ ተማሪዎች በአንዱ እንደተሳለ ይታመናል።
የ36 ዓመቱ የአፓርትመንቱ ባለቤት የተሰረቀ ዕቃ ይዞ በመገኘት በቁጥጥር ስር መዋሉን ፖሊስ አስታውቋል።
የኔፕልስ ዐቃቤ ሕግ ጆቫኒ መሊሎ ለኤኤፍፒ የዜና ወኪል እንደተናገሩት "ሥዕሉ የተገኘው ቅዳሜ ዕለት በብሩህና በትጋት በተደረገ የፖሊስ ተግባር ነው።"
የሥነ ጥበብ ሥራው በከተማው የሚገኘው የሳን ዶሜኒኮ ማጊዬር ቤተክርስቲያን የዶማ ሙዚየም ስብስብ አካል ነው።
ሜሊሎ እንዳሉት በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት "ሥዕሉ የተቀመጠበት ክፍል ለሦስት ወራት ያህል ክፍት ባለመሆኑ ባለሥልጣናቱ መሰረቁን አላወቁም።"
የኪነ ጥበቡ ሥራው መጥፋት ባለመገለጹ መቼ እንደተወሰደ የሚታወቅ ነገር ባይኖርም ሙዚየሙ እስከ ጥር መጀመሪያ በእጁ ይገኝ እንደነበር አስታውቋል።
ፖሊስ የተሰረቀበትን ሁኔታ እያጣራ ቢሆንም በሙዚየሙ ውስጥ የተገባበት ምልክት ግን አልተገኘም።
"በዓለም አቀፍ የጥበብ ንግድ ውስጥ በሚሠራ ድርጅት ድጋፍ ሰጪነት የተፈጸመ ስርቆት መሆኑ አሳማኝ ነው" ብለዋል ሜሊሎ።
የኪነ ጥበብ ሥራውን ማን እንደሳለው ባይታወቅም አንዳንድ ባለሙያዎች የሊዮናርዶ ተማሪ የሆነው ጃኮሞ አሊብራንዲ በ1500 ዎቹ መጀመሪያ እንደሳለው ያምናሉ።
በሥዕሉ ላይ ክርስቶስ አንድ እጁን ወደ ላይ ከፍ አድርጎ ሲታይ በሌላኛው ደግሞ ሉል ይዞ ይወታያል።
ውዝግቡን ለመጨመር ያህል ትክክለኛውና የመጀመሪያው ሥዕል የሊዮናርዶ ዳ ቪንቺ ይሁን አይሁን የሚለው በራሱ አከራካሪ ነው። ሊዮናርዶ በ1519 ሕይወቱ ያለፈ ሲሆን ከ20 ያነሱ ሥዕሎቹ ብቻ ናቸው ያሉት።












