ቡርኪናፋሶ፡ ቤተክርስቲያን ውስጥ በተፈጸመ ጥቃት ቢያንስ 14 ሰዎች ሞቱ

ትናንት በቡርኪናፋሶ ያልታወቁ ታጣቂዎች በቤተክርስቲያን ውስጥ በከፈቱት ድንገተኛ ተኩስ በትንሹ 14 ሰዎች መገደላቸው ተገለፀ።
ጥቃቱ የተፈጸመው በምስራቃዊ ቡርኪና ፋሶ ሃንቶኩራ በተባለው አካባቢ ሲሆን የአካባቢው ነዋሪዎች የዕለተ ዕሁድ የቤተክርስቲያን አገልግሎት ለመካፈል በቤተክርስቲያኗ ተገኝተው ነበር።
የጥቃት ፈጻሚዎቹ ማንነት እና ለምን ጥቃቱን እንደፈጸሙት እስካሁን የታወቀ ነገር የለም።
ባለፉት ዓመታት በቡርኪናፋሶ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በታጣቂዎች የተገደሉ ሲሆን አብዛኛዎቹ ሰዎች በአክራሪ ኢስላማዊ ቡድኖች እንዲሁም ዘርና ሃይማኖትን መሰረት ባደረጉ ጥቃቶች ህይወታቸው አልፏል።
የአካባቢው የመንግሥት ሀላፊዎች ሰጡት በተባለ መረጃ መሰረት ደግሞ በእሁዱ ጥቃት ከሟቾች በተጨማሪ በርካቶች መቁሰላቸው ታውቋል።
አንድ የሀገሪቱ የደህንነት ምንጭን ጠቅሶ ኤኤፍፒ እንደዘገበው የጦር መሳሪያ የታጠቁት ሰዎች ወደ ቤተክርስቲያኗ በመግባት የተኩስ እሩምታ የከፈቱ ሲሆን የቤተክርስቲያኗ አገልጋይ ፓስተር እንዲሁም ህጻናትን ጨምሮ ብዙዎችን ገድለዋል።
ባሳለፍነው ጥቅምት በቡርኪናፋሶ መስጂድ ውስጥ በተፈጸመ ጥቃት 15 ሰዎች ሲደገሉ ሁለት ደግሞ መቁሰላቸው የሚታወስ ነው።













