በቡርኪና ፋሶ መስጅድ ላይ በተሰነዘረ ጥቃት 15 ሰዎች ተገደሉ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በሰሜን ቡርኪና ፋሶ በአንድ መስጅድ ላይ በተሰነዘረ ጥቃት ቢያንስ 15 ሰዎች መገደላቸው ተገልጿል።
ታጣቂዎች ሳልሞሲ ተብላ በምትጠራ መንደር መስጅድ ውስጥ ጸሎት ሲያደርሱ በነበሩ ሰዎች ላይ በከፈቱት ተኩስ ነው 15 ሰዎች የተገደሉት።
በዚህ ጥቃት የተደናገጡ ቁጥራቸው ከፍተኛ የሆኑ የአካባቢው ነዋሪዎች ወደ ጎረቤት ሃገር ማሊ መሸሽ ጀምረዋል።
በቡርኪና ፋሶ መሰል ጥቃቶች ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ ተከስተው የነበረ ሲሆን፤ ጥቃቶቹ የሚፈጸሙት ደግሞ በጽንፈኛ እስላማዊ ቡድኖች እንደሆነ ይነገራል።
ጥቃቱ ከተሰነዘረባት መንደር አቅራቢያ በምትገኘው ጎሮም-ጎሮም ከተማ ነዋሪ የሆኑ አንድ ሰው ለኤኤፍፒ ዜና አገልግሎት እንደተናገሩት፤ ''ከዛሬ ጠዋት ጀምሮ ሰዎች አከባቢውን ለቅቀው እየወጡ ነው"።
እስካሁን ለጥቃቱ ኃላፊነቱን የወሰደ አካል የለም።
ከጎርጎሳውያኑ 2015 ወዲህ በቡርኪና ፋሶ የጽንፈኛ ቡድኖች የሚያደርሱት ጥቃቶች የተበራከቱ ሲሆን፤ በዚህም ምክንያት በሺዎች የሚቆጠሩ ትምህርት ቤቶች ተዘግተዋል።
የተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን እንደሚለው ከሆነ በቡርኪና ፋሶ ባለፉት ሶስት ወራት ብቻ ሩብ ሚሊዮን ሰዎች ከመኖሪያ ቀያቸው ተፈናቅለዋል።












