በጃፓን ጎርፍ የመቶ ሰዎችን ሕይወት ቀጠፈ

የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች በሥራ ላይ

የፎቶው ባለመብት, AFP

በጃፓን ቢያንስ አንድ መቶ ሰዎች በጎርፍ መወሰዳቸው ተሰምቷል። ይህ የሆነው ባለፉት ቀናት በተከታታይ የጣለውን ከባድ ዝናብ ተከትሎ ነው።

ከሞቱት ሰዎቸ ሌላ ሐምሳ ሰዎች የገቡበት አልታወቀም።

ካለፈው ሐሙስ ጀምሮ ምዕራብ ጃፓን ሌላ ጊዜ ከነበረው የሐምሌ የዝናብ መጠን በሦስት እጥፍ ጥሏል። ይህንንም ተከትሎ ሁለት ሚሊዮን ዜጎች ቀያቸውን ለቀው እንዲወጡ ታዘዋል። ምክንያቱ ደግሞ ወንዞች ግድቦቻቸውን ጥሰው እየፈሰሱ ስለሆነ ነው።

'እንዲህ ዓይነት ዝናብ ዘንቦ አያውቅም' ሲሉ የጃፓን የአየር ትንበያ ባለሞያ ለቢቢሲ ተናግሯል።

አብዛኛዎቹ የሞት አደጋዎች የተመዘገቡት በሂሮሺማ ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትር ሺንዞ አቤ ለመገናኛ ብዙኃን እንደተናገሩት የነፍስ አድን ሠራተኞች ቀንተሌለት እየሠሩ ነው።

በሺኮኩ ደሴት ሞቶያማ በምትባለው ከተማ 583 ሚሊ ሚትር ዝናብ መጠን መመዝገቡ ተሰምቷል።

በቀጣይ ቀናትም ከዚህ የባሰ የዝናብ መጠን ሊኖር እንደሚችል ስጋት አለ።