ለቲክቶክ ዕይታ ሲባል የተሞከረው ትዕይንት ከባደ ጉዳትን አደረሰ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
በቲክቶክ ላይ ዕይታ እና ትኩረትን ለማግኘት ሲሉ በመኪና ላይ አደገኛ ትዕይንት ለማሳየት የሞከረው ወጣት ከባድ የአንጎል ጉዳት ሲደርስበት ጓደኛው ለደረሰው አደጋ ተጠያቂ ሆኖ ተፈረደበት።
በዩናይትድ ኪንግደም የሰሴክስ ፖሊስ እንዳለው ጉዳት የደረሰበት የ23 ዓመቱ ወጣት የመኪና ወዳጆች በተመልካችነት በተሰበሰቡበት ስፍራ ጓደኛው በሚያሽከረክረው መኪና ኮፈን ላይ ሆኖ የቲክቶክ ቪዲዮ ሲቀረጽ ወድቆ ነው ከባድ ጉዳት የደረሰበት።
ወጣቱ በኃይል ከሚሽከረከረው መኪና ላይ ወድቆ ጭንቅላቱን ክፉኛ መሬት ስለመታው በአንጎሉ ላይ ከባድ ጉዳት ደርሶበታል።
በዚህም ምክንያት መኪናውን ያሽከረክር የነበረው ኮነር ፔስ በጓደኛው ላይ ጉዳት እንዲደርስ ምክንያት በመሆኑ በአደገኛ የማሽከርከር ክስ ጥፋተኛ ተብሏል።
ቲክቶክ በክስተቱ ላይ አስተያየት እንዲሰጥ ተጠይቋል።
ጉዳዩን የተመለከቱት ዳኛም ሹፌሩን በአደገኛ ሁኔታ በማሽከርከር እና በጓደኛው ላይ ጉዳት እንዲሰደርስ ሰበብ በመሆን በሁለት ዓመት ገደብ የ16 ወራት እስር ፈርደውበታል።
በተጨማሪም የአውቶብስ ሹፌር የሆነው ፔስ ለሁለት ዓመታት እንዳያሽከረክር ታግዶ ለ300 ሰዓታት ሳይከፈለው የማኅበራዊ አገልግሎት ሥራ እንዲሠራ እና ቁጥጥር እንዲደረግበት ዳኛው ወስነዋል።
በአደጋው ጉዳት የደረሰበት ስሙ ያልተጠቀሰው የ23 ዓመቱ ወጣት ለአንድ ወር ያህል እራሱን ስቶ ቆይቶ "እንዲህ ዓይነቱ የጭንቅላት ጉዳት ተደራራቢ ቀዶ ሕክምናዎች እና የሕክምና ድጋፎች አስፈልገውት ነበር" ብለዋል ፖሊሶች።
በአደጋው ምክንያት ወጣቱ በአካሉ ላይ እና በአእምሮው ላይ ከባድ ተጽእኖ እንደተፈጠረበት እና እሱን ለመንከባከብ እናቱ ከሌላ ግዛት ለመምጣት መገደዳቸውን ፖሊስ ገልጿል።
ይህ ለቲክቶክ ሲባል በአደገኛ ሁኔታ በሚሽከረከር መኪና ላይ ሆኖ ወጣቱ ቪዲዮ ለመቅረጽ የተሞከረው ለአጭር ጊዜ ነበር። አደጋው የደረሰው መኪናው መንቀሳቀስ ከጀመረ በግምት ከ17 ሰከንዶች በኋላ ነው።
አንድ ታዛቢ እንዳለው የአሽከርካሪው ድርጊት "ጭፍን እና ኃላፊነት የጎደለው" መሆኑን በመግለጽ ክስተቱ የአሽከርካሪውን እና የአደጋው ሰለባ የሆነውን ወጣት "ሕይወት በማይጠገን ሁኔታ የለወጠ ነው" ብሏል።
"ፔስ [አሽከርካሪው] ከባድ ጉዳት ለማድረስ ብሎ የፈጸመው ነገር ባይሆንም፤ ከመጀመሪያው እራሱን በዚህ ሁኔታ ውስጥ መክተት አልነበረበትም" ሲል መሞከር ያልነበረበትን ነገር መፈጸሙ ከባድ አደጋን ማስከተሉን ገልጿል።















