ኬንያ በትምህርት ቤቶች ውስጥ የፀረ ተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት ዘመቻ ጀመረች

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ኬንያ በትምህርት ቤቶች ውስጥ ተንሰራፍቷል ያለችው የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት አጀንዳ ላይ ዘመቻ ጀመረች።
የኬንያ የትምህርት ሚንስትር ኢዚኬል ማቾጉ በኬንያ ትምህር ቤቶች ውስጥ የተመሳሳይ ጾታ አፍቃሪዎች አጀንዳ ሰርጎ ገብቷል ሲሉ ለአገሪቱ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተናግረዋል።
ሚንስትሩ በትምህር ቤቶች ውስጥ ‘የተመሳሳይ ጾታ አጀንዳን’ ለማስቀረት በኬንያ አንጀሊካን ቤተ-ክርስቲያን የሚመሩ ጉዳዩን የሚከታተሉ ሰዎች ይሾማሉ ብለዋል።
በኬንያ ትምህር ቤቶች ውስጥ የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነትን የተመለከቱ ጉዳዮችን የሚከታተል ኮሚቴ የተቋቋመ ሲሆን ኮሚቴው መማሪያ እና አጋዥ መጽሐፍትን መከለሰን ሊያካትት እንደሚችል ትምህር ሚንስትሩ ገልጸዋል።
ይህ የኬንያ ትምህርት ሚንስቴር እቅድ የተሰማው ቀዳማዊት እመቤት ሬቸል ሩቶ የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት አደጋ ፈጥሯል በማለት በመላው ኬንያ ጸሎት እንዲደረግ ካወጁ ከቀናት በኋላ ነው።
የፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ ባለቤት የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት ‘ቤተሰብ በሚባለው ተቋም ላይ አደጋ ደቅኗል' ብለዋል።
“አባት፣ እናት እና ልጆች ያሉበትን የቤተሰብ ተቋም ማጠናከር እንፈልጋለን። የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት በመጽሐፍ ቅዱስም ሆነ በአፍሪካውያን ዘንድ ተቀባይነት የለውም። የቤተሰብ እሴቶችን እንጠብቅ” ብለዋል ቀዳማዊት እመቤት ሬቸል ሩቶ።
አንዳንድ የተመሳሳይ ጾታ ደጋፊዎች ግን ይህ የመንግሥት እርምጃ በትምህር ቤቶች ውስጥ ስለ ተመሳሳይ ጾታ የተሳሳተ ግንዛቤ አንዲሰርጽ ያደርጋል በማለት ስጋታቸውን ገልጸዋል።
የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት በኬንያ ሕጋዊ አይደለም። የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነትን የሚቃወሙ አመለካከቶች ባለፉት ቀናት ጠንከር ብለው ታይተዋል።
ለዚህም ምክንያቱ የአገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የተመሳሳይ ጾታ አፍቃሪዎች በማሕበር የመደራጀት መብት አላቸው ማለቱን ተከትሎ ነው።












