የነዳጅ አቅራቢ ድርጅት ለአዲስ ማደያዎች ነዳጅ ላለማቅረብ መወሰኑን አስታወቀ

ነዳጅ ማደያ

የፎቶው ባለመብት, Birbir city communication

የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ድርጅት፤ መንግሥት ወደ ሀገር ውስጥ የሚያስገባውን ነዳጅ "ለመቀነስ እየተሰራ" በመሆኑ ለአዲስ ማደያዎች ነዳጅ ላለማቅረብ መወሰኑን አስታወቀ።

በሀገሪቱ ያለውን የነዳጅ ፍላጎት መሰረት በማድረግ ከውጭ ሀገር ነዳጅ የማስገባት እና ለአከፋፋይ ኩባንያዎች የማቅረብ ኃላፊነት ያለበት ነዳጅ አቅራቢ ድርጅት፤ ይህንን ውሳኔውን ያስታወቀው ሰኞ ሕዳር 30/2017 ዓ.ም. ለነዳጅ እና ኢነርጂ ባለስልጣን በጻፈው ደብዳቤ ነው።

በኢትዮጵያ ብቸኛ ነዳጅ አቅራቢ የሆነው ድርጅቱ፤ በሀገሪቱ ውስጥ ላሉ ማደያዎች ነዳጅ የሚያቀርበው፤ ማደያዎቹ ከነዳጅ እና ኢነርጂ ባለስልጣን የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ሲያገኙ ነው።

ባለስልጣኑ፤ ማረጋገጫ ያገኙ አዲስ ማደያዎች ነዳጅ ማግኘት እንዲጀምሩ ወደ አቅራቢ ድርጅቱ የሚልክ ሲሆን ከአንድ ወር ገደማ በፊትም "ጥቂት የማይባሉ" ማደያዎች በተመሳሳይ መልኩ ወደ አቅራቢ ድርጅቱ ተልከው እንደነበር የኢትዮጵያ ነዳጅ አዳዮች ማህበር የስራ አመራር ቦርድ አባል አቶ ኤፍሬም ተስፋዬ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

ነዳጅ አቅራቢ ድርጅት ለባለስልጣኑ በጻፈው ደብዳቤ ላይም፤ "በተለያየ ጊዜ ለተለያዩ ማደያዎች የብቃት ማረጋገጫ ሰርቲፊኬት በመስጠት ነዳጅ እንዲያገኙ ለድርጅታችን መላካችሁ ይታወሳል" ሲል ተመሳሳይ ሀሳብ አንስቷል።

አዲሶቹ ነዳጅ ማደያዎች ምንም እንኳ የማረጋገጫ ሰርተፊኬት ቢያገኙም የአቅራቢ ድርጅቱ ነዳጅ እንዳላቀረበላቸው የሚገልጹ ቅሬታዎችን መስማታቸውን የማህበሩ የስራ አመራር ቦርድ አባል አቶ ኤፍሬም ተናግረዋል።

የነዳጅ አቅራቢ ድርጅት ለአዲስ ማደያዎች ነዳጅ ላለማቅረብ የወሰነው "የድርጅቱ የሥራ አመራር ቦርድ ባደረገው" ስብሰባ ጉዳዩ ከመንግሥት ፖሊሲ ጋር የሚቃረን ሆኖ ስላገኘው እንደሆነ በደብዳቤው ላይ ጠቅሷል።

ደብዳቤው፤ የድርጅቱ የስራ አመራር ቦርድ "መንግስት ወደ ሀገር የሚገባውን የነዳጅ መጠን ለመቀነስ እየሰራ ባለበት ሁኔታ ለእነዚህ ማደያዎች ነዳጅ ማቅረብ ከመንግሥት ፖሊሲ አንጻር ተገቢ አለመሆኑን አቅጣጫ አስቀምጧል" በማለት ውሳኔው አስረድቷል።

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

ይህንን የሥራ አመራር ቦርድ "አቅጣጫ" የተቀበለው የነዳጅ አቅራቢ ድርጅት "በመንግስት የተለየ ውሳኔ ካልተሰጠ በስተቀር ለአዳዲስ ማደያዎች ነዳጅ ለማቅረብ እንደሚቸገር" ለነዳጅ እና ኢነርጂ ባለስልጣን በጻፈው ደብዳቤ አስታውቋል።

ቢቢሲ በጉዳዩ ላይ ለኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ድርጅት እንዲሁም ነዳጅ እና ኢነርጂ ባለስልጣን ተጨማሪ መረጃ ለማድረግ ያደረጋቸው ጥረቶች አልተሳኩም።

የኢትዮጵያ ነዳጅ አዳዮች ማህበር የስራ አመራር ቦርድ አባል አቶ ኤፍሬም፤ የነዳጅ አቅራቢ ድርጅት ለአዲስ ማደያዎች ላለማቅረብ መወሰኑ ላይ እምብዛም ተቃውሞ እንደሌላቸው ለቢቢሲ ተናግረዋል።

ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙየነዳጅ ማደያዎች ቁጥር ከሁለት ዓመት ገደማ በፊት ከነበረበት 1,200 ገደማ በአሁኑ ሰዓት ወደ 1,800 አካባቢ መድረሱን አቶ ኤፍሬም ይናገራሉ። "500 ገደማ ነዳጅ ማደያዎችም" በግንባታ ሂደት ላይ መሆናቸውን አክለዋል።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የነዳጅ ማደያዎች እየተከፈቱ ያሉት "ብዙም ፍላጎት እና አቅርቦት በሌለባቸው ቦታዎች" መሆኑን የሚናገሩት አቶ ኤፍሬም፤ የእነዚህ ማደያዎች መከፈት የፈጠረው "የገበያ ሽሚያ" ህዝብ በብዛት የሚገለግልባቸው አካባቢዎች ላይ በሚገኙ ማደያዎች ላይ ተፅእኖ እየፈጠረ መሆኑን ያነሳሉ።

"አንድ ሺህ፣ ሁለት ሺህ ሰው ባለበት መንደር 'ከተማ' በሚል ስያሜ ነዳጅ ማደያ ሲገነባ እያየን ነው። ምናልባት አንድ መኪና ቢያራግፉ በዓመት ሸጠው ጨርሰው የማይገዙበት ሁኔታ ባለበት ሁኔታ ማደያዎች ተቋቁመው፤ 'በወር ሁለት ሶስት ጊዜ [ነዳጅ] ካልተራገፈልን' ብለው የገበያ ሽሚያ ውስጥ የመግባት ሁኔታ አለ" ብለዋል።

"ብዙም የህዝብ ቁጥር የሌለባቸው አካባቢዎች ላይ ነዳጅ ሲሰራጭ ለሀገር ውስጥ ህገ ወጥ የነዳጅ ዝውውር ተጋላጭ ነው" ሲሉም አዲስ የሚከፈቱ ማደያዎች የሚገኙበት ቦታ የፈጠረውን ስጋት ገልፀዋል።

ይሁን እንጂ ለአዲስ ማደያዎች ነዳጅ ላለማቅረብ ሲወሰን፤ ትክክለኛ የነዳጅ ፋላጎት ባለባቸው አከባቢዎች ላይ የተከፈቱ ማደያዎችንም አብረው "እየተጨፈለቁ" መሆኑን አስረድተዋል።

እነዚህን አካባቢዎች መለየት እንዳለባቸውን የጠቆሙት የማህበሩ ስራ አመራር ቦርድ አባል፤ በዋንኛነት ጉዳዩ በሀገሪቱ ውስጥ "በበቂ ሁኔታ ነዳጅ አለመቅረቡ" መሆኑን አክለዋል።

እስካሁን ድረስ በመንግስታዊው በሆነው የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ድርጅት ብቻ ወደ ሀገር ውስጥ ይገባ የነበረው ነዳጅ ከሚቀጥለው ዓመት ጀምሮ በግል አቅራቢዎችም እንዲገባ ሊፈቀድ እንደሚችል የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዶ/ር ካሳሁን ጎፌ ከሶስት ሳምንት ገደማ በፊት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ተናረው ነበር።