ጋናውያኑን ያስቆጣው መሠረታዊ ስነ ወሲብ ትምህርት

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በጋና ዕድሜያቸው ከአራት አመት ጀምሮ ላሉ አንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ለመስጠት ታቅዶ የነበረው መሠረታዊ የስነ ወሲብ ትምህርት ከወላጆችና ከክርስቲያን ቡድኖች በገጠመው ተቃውሞ ምክንያት ተቋረጠ።
የጋና የትምህርት ባለሙያዎች እንደሚሉት ይህ የዩኔስኮ ፕሮግራም ተማሪዎች ስለ ወሲብ እና ስነ ተዋልዶ ጉዳዮች አጠቃላይ መረጃ እንዲኖራቸው ያደርጋል።
የጋና ትምህርት አገልግሎት ዳይሬክተር እንዳሉት ይህ መሰረታዊ የስነ ወሲብ ትምህርት ተማሪዎቹ "በጎ የሆነ አመለካከት እንዲያዳብሩ፣ ለራሳቸውና ለሌሎች ክብር እንዲኖራቸው፣ አእምሯቸውን እንዲያዘጋጁ፣ ሌሎች ላይ እንዳይፈርዱና የስነተዋልዶና ወሲብ ጉዳዮች ላይ ኃላፊነት አንዲሰማቸው ያደርጋል" ብለዋል።
ይህንን መርሀ ግብር የተቃወሙ አካላት ሕፃናቱ ስለተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት እየተዋወቁ ነው ሲሉ ይከስሳሉ።
" ይህ ስልት ነው፤ ዕቅድ አላቸው። ግልፅ ሆኖ እንዲታይ ያልተፈለገ ነገር አለ" ይላል የስነወሲብና ቤተሰብ ጉዳዮች በአግባቡ መሰጠት አለባቸው ሲል የሚከራከረው ጥምረት መሪ የሆነው ሞሰስ ፎህ አሞኒንግ፤ እርሱ እንደሚለው የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት "ሀጥያት" ነው።
ወላጆችና ክርስቲያን ቡድኖች ልጆቹ ለአካለ መጠን ሳይደርሱ ለምን ስለ ወሲብ እንዲማሩ ተፈለገ ሲሉ በመጠየቅ እቅዱን "ሰይጣናዊ" ሲሉ ይቃወሙታል።
የጋና መምሕራን ማህበር በበኩሉ በዚህ መርሀግብር ማንም እንዳላማከረው ገልጿል።
ይህ መሰረታዊ የስነ ወሲብ ትምህርት ከባለድርሻ አካላት ጋር ምክክር ከተደረገበት በኋላ መሰጠት ይጀምራል ተብሏል።


















