የኒውዚላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር አድናቆት እየጎረፈላቸው ነው

የፎቶው ባለመብት, EPA
የኒውዚላንዱ ክራይስትቸርች ግድያን ተከትሎ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ጃሲንዳ አርደን ለሁኔታው ምላሽ የሰጡበት መንገድና ለተጎጅዎች ያሳዩት ፍቅር የብዙዎችን ልብ የነካ ነበር።
በተለይም "አንድ ነን፤ እነሱ እኛ ናቸው" በሚል ያደረጉት ንግግርም እንዲሁ የብዙዎችን ስሜት ነክቷል። ጠቅላይ ሚኒስትሯ ለዚህ ፈታኝ ሁኔታ ምላሽ የሰጡበት መንገድና መላ ሃገሬውን በአንድ ላይ እንዲቆም ያደረጉበት ሁኔታ ዓለም አቀፍ አድናቆትን እያስገኘላቸው ነው።
የቢቢሲ ከፍተኛ የፖለቲካ ተንታኝ የሆነው ሮቢን ለስቲግ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያሳዩት ብቃት ከብዙ ነገሮች አንፃር ቢታይ የላቀ የፖለቲካ ብቃት ውጤት እንደሆነ ይናገራሉ።
"ያሉት ብቻም ሳይሆን ያሉበት መንገድም ጭምር ነው ቁም ነገሩ። አገሪቱ ምን እንደሚያስፈልጋት በመረዳትና ምሳሌ በሚሆን መልኩ ነው ምላሽ የሰጡት" ይላል።

የፎቶው ባለመብት, CHRISTCHURCH KENT KONSEYİ
እንዲህ ያለ አገራዊ አደጋ ሲያጋጥም እንዲህ ባለና በተሳካ መንገድ ለገጠመው ችግር ምላሽ በመስጠት አገርን አንድ ላይ እንዲቆም ማስቻል እንደ ኒውዚላንዷ ጠቅላይ ሚኒስትር አርደርን ያሉ ጥቂቶች ብቻ የሚችሉት ነው።
የዋሽንግተን ፖስቱ ኢሻን ታሮር "አርደርን የአገራቸው ሐዘንና ስቃይ ገፅታ ሆነዋል" በማለት የፃፈ ሲሆን ሌሎችም በርካታ ታዋቂ ዓለም ዓቀፍ መገናኛ ብዙኃን ጠቅላይ ሚኒስትሯን 'ድንቅ መሪ' በማለት ዘግበዋል።
የቱርኩ ፕሬዘዳንት ጣይብ ኤርዶዋንም ጠቅላይ ሚኒስትሯ ያሳዩት ነገር ለዓለም ምሳሌ የሚሆን ነው ሲሉ ተናግረዋል።












