የሮማ ካቶሊክ ሊቀ ጳጳስ ፖፕ ፍራንሲስ የተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት ያሳስበኛል እያሉ ነው

የፎቶው ባለመብት, REUTERS
የሮማ ካቶሊክ ሊቀ ጳጳስ ፖፕ ፍራንሲስ በቤተክርስቲያኒቱ ቀሳውስት መካከል እየተፈጠረ ያለው የተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት እጅጉን እንደሚያሳስባቸው አሳወቁ።
በሃይማኖታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ቃለ-መጠይቅ የሰጡት ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ የተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት ጉዳይ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ነው ሲሉ ተደምጠዋል።
የተመሳሳይ ፆታ ግንኙነትን 'ዘመን አመጣሽ' ሲሉ የገለፁት ፖፕ ፍራንሲስ ቀሳውስት ከድርጊቱ በመቆጠብ ለጌታ ትዕዛዝ ተገዥ እንደሆኑ አሳስበዋል።
የካቶሊክ አብያተ ክርስትያናት ለቫቲካን የሚሆን ቄስ ሲመርጡ አስተውለው እንደሆን ጥሪ አቅርበዋል።
ቄሶችን የሚያሰለጥኑ የኃይማኖት ሰዎች 'በሰብዓዊነት እና ስሜትን በመቆጣጠር' ብቁ እንዲሆኑ ሊያደርጓቸው ይገባል ሲሉም መልዕክት አክለዋል።
በቅስና እና ምንኩስና ዓለም የተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት ቦታ እንደሌላቸው ነው ፖፕ ፍራንሲስ ያሳወቁት።
በፈረንጆቹ 2013 ፖፕ ፍራንሲስ የተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት ድርጊት ሃጥያት ነው የተመሳሳይ ፆታ ግንኙነት ውስጥ መገኘት ግን አይደለም ብለው ትንሽ ወዝገብ የሚያደርግ አስተያየት መስጠታቸው ይታወሳል።
«አንድ ሰው የተመሳሳይ ፆታ ውስጥ ሆኖ ፈጣሪን የሚፈልግ ከሆነና መልካም ምግባር ካለው እኔ ማን ሆኜ ነው የምፈርደው» ብለው ነበር አስተያየት የሰጡት።












