ጀርመን ውስጥ ሁለት ታዳጊ ሴቶችን በስለት የወጋው ኤርትራዊ ዕድሜ ልክ ተፈረደበት

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ጀርመን ውስጥ በአስራዎቹ የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሁለት ሴቶችን በስለት የወጋው ኤርትራዊ የዕድሜ ልክ እስራት ተፈረደበት።
ጥገኝነት ጠያቂ የሆነው ይህ ኤርትራዊ በስለት ከወጋቸው ሁለት ታዳጊ ሴቶች መካከል የአንዷ ሕይወቷ አልፏል።
ኡቁባ ቢ በሚል ስም ብቻ የተጠቀሰው የ27 ዓመቱ ግለሰብ፣ ሁለቱ ታዳፊ ሴቶች ላይ ጥቃቱን የፈጸመው በዚህ ዓመት ኅዳር ወር ላይ ኢሌራኪራቸበርግ ተብላ በምትጠራ የጀርመን ከተማ ውስጥ ነው።
በጀርመን ከፍተኛ ቁጣን በቀሰቀሰው በዚህ የወንጀል ድረጊት፤ ኤስ የተባለችው የ14 ዓመት ታዳጊ 23 ጊዜ በስለት ተወግታ ሕይወቷ ሲያልፍ፤ የ13 ዓመት ጓደኛዋ ደግሞ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባታል።
ዐቃቤ ሕግ እንደሚለው የዕድሜ ልክ እስራት የተፈረደበት ኤርትራዊ ስለቱን የያዘው በአካባቢው በሚገኝ የኢሚግሬሽን መሥሪያ ቤት ውስጥ ሊጠቀመው አስቦት የነበረ ነው።
ነገር ግን ግለሰቡ የያዘውን ቢላ ታዳጊዎቹ ከተመለከቱበት በኋላ ጥቃት ሰንዝሮባቸዋል አንደኛዋን ለሞት ሲዳርጋት ሌላኛዋ ክፉኛ መጎዳቷ ተነግሯል።
ዐቃቤ ሕግ እንዳለው ግለሰቡ ታዳጊ ሴቶቹ ለፖሊስ ይጠቁሙብኛል በሚል ድንገት ወንጀሉን ፈጽሞባቸዋል።
በተጨማሪም ዐቃቤ እንዳመለከው ግለሰቡ ወደ ኢትዮጵያ ተጉዞ ጋብቻ ለመፈጸም ከጀርመን ባለሥልጣናት የጠየቀው የጉዞ ሰነድ ስላልተሰጠው በኢሚግሬሽን ኃላፊዎች ተበሳጭቶ ነበር።
በደቡብ ጀርመን የሚገኘው ፍርድ ቤት ኤርትራዊው የፈጸመው ወንጀል “እጅግ ከባድ” በመሆኑ ግለሰቡ 15 ዓመታት በእስር ከቆየ በኋላ እንኳን ከእስር የመለቀቅ ዕድሉ በጣም የጠበበ ነው ተብሏል።
ይህ ኤርትራዊ ጀርመን የገባው ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ስደተኞች ጦርነት እና እስርን በመሸሽ አውሮፓን ባጥለቀለቁበት ዓመት እአአ 2015 ላይ ነበር።
ግለሰቡ ከዘጠኝ ወራት በፊት የጀርመንኛ ቋንቋ ተምሮ እና ሥራ ይዞ በተረጋጋ ሁኔታ የጀርመን ማኅብረሰብን ተቀላቅሎ ነበር ይላል ጉዳዩን የተመለከተው ፍርድ ቤት መዝገብ።
ኡቁባ ቢ ፍርድ ቤት በቀረበበት ወቅት በፈጸመው የወንጀል ድርጊት መጸጸቱን ገልጾ የተጎጂ ቤተሰቦች ይቅርታን ጠይቋል።
ግለሰቡ የተላለፈበትን ብይን ይግባኝ መጠየቅ ይችላል ተብሏል። ፍርደኛው የሚያቀርበው ይግባኝ ውድቅ ከተደረገ ግን በእስር ጊዜው ወቅት ወደ ትውልድ አገሩ እንዲመለስ ሊደረግ እንደሚችል ዐቃቤ ሕግ ገልጿል።
በሁለቱ ታዳጊ ሴቶች ላይ የተፈጸመው ወንጀል በጀርመን ከፍተኛ ቁጣን ቀስቅሷል። የልጆቹ ቤተሰቦች ግን በታዳጊዎቹ ላይ የተፈጸመው ወንጀል የፀረ-ስደተኛ አቋም በሚያራምዱ ቡድኖች የፖለቲካ መጠቀሚያ እንዲሆን አንፈልግም ብለዋል።
በጥቃቱ የተገደለችው ጀርመናዊት የዘር ሐረጋቸው ከቱርክ ከሆኑ ቤተሰቦች የተገኘች ነበረች።
በኤርትራ ያለውን የፖለቲካ እና የእምነት ነጻነት ጭቆና እንዲሁም የጊዜ ገደብ የሌለውን አስገዳጅ የብሔራዊ አገልግሎት በመሸሽ በርካቶች ኤርትራውያን አገር ጥለው ይሰደዳሉ።












