አሜሪካ ውስጥ ለሞተችው ኡጋንዳዊት ከ10 ሚሊዮን ዶላር በላይ ካሳ ተፈረደ

ኤስተር ናካጂጎ

የፎቶው ባለመብት, EU International Partnerships

የምስሉ መግለጫ, ኤስተር ናካጂጎ

ኡታህ ግዛት ውስጥ የሚገኝ አንድ የአሜሪካ ፍርድ ቤት ከሁለት ዓመት በፊት በድንገተኛ አደጋ ሕይወቷ ላለፈ ኡጋንዳዊት አክቲቪስት ቤተሰቦች ከ10 ሚሊዮን ዶላር በላይ ካሳ እንዲከፈል ወሰነ።

ኡጋንዳዊቷ ኡታህ ግዛት ውስጥ የሚገኝን አንድ ብሔራዊ ፓርክ ከባሏ ጋር እየጎበኙ ሳለ ነበር በድንገተኛ አደጋ ምክንያት ሕይወቷ ሊጠፋ የቻለው።

ቤተሰቦቿ በአደጋው ምክንያት ሕይወቷ ባለፈው ኤስተር ናካጂጎ ሞት ምክንያት ለደረሰባቸው ጉዳት ካሳ እንዲከፈላቸው ጉዳዩን ፍርድ ቤት ወስደው ሲከራከሩ ቆይተው እንደተወሰነላቸው የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

ነገር ግን ፍርድ ቤቱ አሁን ለቤተሰቡ የወሰነው ካሳ ከተጠየቀው 140 ሚሊዮን ዶላር በከፍተኛ ደረጃ ያነሰ ቢሆንም፣ በኡታህ ግዛት ታሪክ የፌደራል መንግሥቱ የከፈለው ከፍተኛው ካሳ መሆኑን የቤተሰቡ ጠበቃ ገልጿል።

በኡጋንዳዊቷ ኤስትር ላይ ለደረሰው የሞት አደጋ ለቤተሰቡ በፍርድ ቤት ከተወሰነው የ10 ሚሊዮን ዶላር በላይ ካሳ ውስጥ ባለቤቷ 9.5 ሚሊዮን ዶላር፣ እናቷ 700,000 ዶላር እና አባቷ ደግሞ 350,000 ዶላር እንደሚደርሳቸው ተነግሯል።

አዲስ ተጋቢ የነበሩት የ25 ዓመቷ ሟች ኤስተር ናካጆጎ እና ባሏ ሉዶቪች በምሥራቃዊ ኡታህ ውስጥ ጉብኝት ላይ ሳሉ ነበር አደጋ ደርሶ ሚስት ሕይወቷ ያለፈው።

የአደጋውም ምክንያት በፓርኩ ውስጥ በአግባቡ ያልተዘጋ የብረት በር በከባድ ነፋስ ምክንያት ተወርውሮ ከባሏ ጋር መኪና ውስጥ የነበረችውን ኤስተር ላይ የከፋ ጉዳት በማድረስ በአሰቃቂ ሁኔታ ለሞት አብቅቷታል።

አሰቃቂው አደጋ በኤስተር ላይ ያስከተለው ሞት እና በኡጋንዳ ውስጥ ለሴቶች እና ለልጃገረዶች መብት ተከራካሪ ከመሆኗ አንጻር የኤስተር ሞት በአሜሪካ ውስጥ ከፍተኛ ትኩረት እንዲያገኝ አድርጎታል።