ቀጥታ, በመካከለኛው ምሥራቅ የሚፈጸመው ጥቃት ሲቀጥል፣ የነዳጅ ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ ጨመረ

ከሳምንት በፊት የተቀሰቀሰው የፋርስ ባሕረ ሰላጤው ጦርነት በቀጠለበት በአሁኑ ወቅት በዓለም ገበያ የነዳጅ ዋጋ አሻቅቧል። አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የሚፈጽሙት ጥቃት የቀጠለ ሲሆን፣ ኢራን ደግሞ በአጸፋው በዙሪያዋ ያሉ የአሜሪካ አጋር አገራትን በሚሳዔል እና በድሮን እያጠቃች ነው። ይህ ጦርነት የነዳጅ ምርት እና ዝውውርን በማስተጓጎሉ ዋጋው በከፍተኛ ሁኔታ እንዲጨምር ምክንያት ሆኗል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ትራምፕ ወደ ኢራን እግረኛ ሠራዊት የማሰማርት ሐሳብ እንደሌላቸው ተናገሩ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ከእስራኤል ጋር በመቀናጀት በኢራን ላይ መጠነ ሰፊ የአየር እና የሚሳዔል ጥቃት እያካሄዱ ያሉት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እግረኛ ሠራዊት ወደ ኢራን የማሰማራት ዕቅድ እንደሌላቸው ጠቆሙ።

    ፕራምፕ ለኒው ዮርክ ፖስት እንደተናገሩት እስካሁን ባለው ሁኔታ የአሜሪካ ወታደሮችን ወደ ኢራን እንዲዘምቱ ከሚያደርስ ውሳኔ ላይ እንዳልደረሱ ተናግረዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኢራን ያላትን የዩራኒየም ክምችት ደኅንነት ለመጠበቅ እግረኛ ወታደሮችን ለማሰማራት እያሰቡ እንደሆነ ለቀረበላቸው ጥያቄ “በዚያ ላይ ምንም ዓይነት ውሳኔ ላይ አልደረስንም። ወደዚያ ውሳኔ ከሚያደርሰን ሁኔታ አልተቃረብንም” ሲሉ ወታደር የመላክ ሃሳብ እንደሌለ ገልጸዋል።

    የኢራን ቀጣይ መሪን በመወሰን ላይ ሚና እንዲኖራቸው እንደሚፈልጉ ባለፉት ቀናት ሲናገሩ የነበሩት ትራምፕ የኢራን የሊቃውንት ቡድን የቀድሞውን ሟቹን ጠቅላይ መሪ ልጅ ቦታውን እንዲይዝ በመምረጣቸው “ደስተኛ እንዳልሆኑ” ተናግረዋል።

  2. የቀጠሉት ጥቃቶች፣ የነዳጅ ዋጋ ንረት እና አዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ

    ፍንዳታ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በኢራን ላይ የተከፈተው ጥቃት ተባብሶ አስረኛ ቀኑ ላይ በደረሰባት በዛሬው ዕለት ሰኞ በመካከለኛው ምሥራቅ ባሉ አገራት ውስጥ ፍንዳታዎች በስፋት ተሰምተዋል፤ ጉዳትም አድርሰዋል።

    • በአሜሪካ እና በእስራኤል ጥቃት ስር በምትገኘው በኢራን ዋና ከተማ ቴህራን እና በእስራኤል ጥቃት የሚፈጸምባት የሊባኖስ ዋና ከተማ ቤይሩት ውስጥ ከባድ ፈንዳታ ተሰምቷል።
    • ኢራን በእስራኤል ላይ እየወሰደችው ባለው የአጸፋ እርምጃ ቴል አቪቭ ውስጥ አንድ ሰው መገደሉን የአገሪቱ መንግሥት አስታውቋል።
    • ቱርክ ደግሞ በበኩሏ ወደ አየር ክልሏ የገባን የኢራን ሚሳዔል ማውደሟን ስታስታውቅ፣ የዩናይትድ አረብ ኤምሬትስ መከላከያ ሚኒስቴር በአስሮች የሚቆጠሩ ድሮኖችን መለየቱን ገልጿል።
    • ጥቃቶች በተለያዩ አገራት ውስጥ መቀጠላቸው እየተነገረ ባለበት በአሁኑ ወቅት የነዳጅ ዋጋ ማሻቀቡን ቀጥሏል። ሩሲያ በዩክሬን ላይ ወረራ ከከፈተች ወዲህ የነዳጅ ዋጋ በበርሜል ከ100 ዶላር በላይ ደርሷል።
    • አገራት ይህንን ለመቆጣጠር የመጠባበቂያ ነዳጃቸውን ለመጠቀም እንዲሁም የዋጋ ጭማሪን ለመቆጣጠር እርምጃ እየወሰዱ ነው።
    • የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ጦርነቱ የሚራዘም ከሆነ ቤተሰቦች እና የንግድ ተቋማት በከፍተኛ ሁኔታ ጫና እንደሚደርስባቸው ተናግረዋል።
    • ዶናልድ ትራምፕ ግን ከፍተኛውን የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ ለዓለም ሰላም ሲባል የሚከፈል “በጣም ትንሽዬ ዋጋ ነው” ብለዋል።
    • የኢራን ጠቅላይ መሪን በመተካት የሟቹ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ልጅ ሞጅታባ ኻሜኒ መመረጣቸውን ተከትሎ እስራኤል እና አሜሪካ ተተኪውን መሪ ዒላማ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል። ይህም ጦርነቱ በቅርቡ አይቋጭም የሚል ስጋትን ፈጥሯል።
  3. አዲሱን ጠቅላይ መሪ የሚደግፍ ሰልፍ በቴህራን ተደረገ

    በቴህራን የተደረገ የድጋፍ ሰልፍ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, በቴህራን የተደረገ የድጋፍ ሰልፍ

    የኢራን ጠቅላይ መሪ ቦታን በአሜሪካ እና በእስራኤል ጥቃት የተገደሉት አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ልጅ መረከባቸውን ተከትሎ በዋና ከተማዋ ቴህራን የድጋፍ ሰልፍ ተደረገ።

    አደባባይ የወጡት የመንግሥት ደጋፊዎች የሟቹን ጠቅላይ መሪ እና የልጃቸውን ፎቶግራፎችን ከኢራን ባንዲራ ጋር አድርገው ይዘው ታይተዋል።

    የፈረንሳይ ዜና ወኪል ኤኤፍፒ እንደዘገበው በሺዎች የሚቆጠሩ ኢራናውያን በዋና ከተማዋ ማዕከላዊ ክፍል ወደሚገኘው አደባባይ በመውጣት ለአዲሱ ጠቅላይ መሪ ታማኝነታቸውን ገልጸዋል።

    የአዲሱን መሪ ምርጫ በመደገፍ አደባባይ ከወጡት ኢራናውያን በተጨማሪ ሌሎች ደግሞ አዲሱ ጠቅላይ መሪ “ከአባታቸው የከፉ ናቸው” በሚል ለቢቢሲ የፋርስ ቋንቋ አገልግሎት ተናግረዋል።

    ኢራን ዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኃን ወደ አገሯ ገብተው እንዳይዘግቡ ጥብቅ የቪዛ ቁጥጥር ስለምታደርግ በአገሪቱ ውስጥ ያለውን ሁኔታ ለማወቅ የሚያስችሉ መረጃዎችን ማግኘት አዳጋች ነው።

  4. ከአራት ዓመት ወዲህ ከፍተኛው የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ ተመዘገበ

    በነዳጅ ማውጫ፣ መጣሪያ እና ማስተላለፊያዎች ላይ በሚፈጸም ጥቃት ምክንያት አቅርቦቱ ተስተጓጉሏል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በነዳጅ ማውጫ፣ መጣሪያ እና ማስተላለፊያዎች ላይ በሚፈጸም ጥቃት ምክንያት አቅርቦቱ ተስተጓጉሏል

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የከፈቱት ጦርነት አንድ ሳምንት ካለፈው በኋላ የነዳጅ ዋጋ በከፍተኛ ደረጃ ጭማሪ ሲያሳይ በዚህም ምክንያት የሌሎች ሸቀጦች ዋጋ እየጨመረ ነው።

    አሁን የተከሰተው የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ ከአራት ዓመታት ወዲህ ከፍተኛው መሆኑ ተነግሯል። አገራትም በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው ውጥረት እስኪረግብ ድረስ ለመጠባበቂያ ያያዙትን የነዳጅ ክምችት ለመጠቀም እያሰቡ ነው።

    ከፍተኛው የዓለም ነዳጅ ዘይት በሚወጣበት እና በሚተላለፍበት የፋርስ ባሕረ ሰላጤ አካባቢ የተቀሰቀሰው ጦርነት የነዳጅ ማውጫዎች፣ ማጣሪያዎች እና ማስተላለፊያ መስመሮች ላይ መስተጓጎል ፈጥሯል።

    ኢራን የተከፈተባትን ጥቃት ተከትሎ በሳዑዲ፣ በኤምሬትስ እና በኳታር ባሉ የነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ ማዕከላት ላይ ጥቃት በመፈጸሟ እንዲሁም፣ በርካታ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች በሚተላለፉበት የሆርሙዝ ሰርጥ በተከሰተው የደኅንነት ስጋት መርከቦች መንቀሳቀስ አልቻሉም።

    ከፍተኛው የነዳጅ ምርት መንቀሳቀስ ባለመቻሉ በዓለም ገበያ የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ አሳይቶ ባለፈው ሳምንት ከ70 ዶላር በታች የነበረው አንድ በርሜል ነዳጅ ከ100 ዶላር በላይ ተሻግሯል።

    ብሬንት የተባለው ዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ መተመኛ መድረክ ላይ እሐድ ዕለት በተደረገው ግብይት ዋጋው በ30 በመቶ ጨምሮ አስከ 119 ዶላር ደርሷል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ግን የነዳጅ ጭማሪው ለአጭር ጊዜ ብቻ እንደሚቆይ በማኅበራዊ ሚደያ ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    “የነዳጅ ዋጋ ጭማሪው ለአጭር ጊዜ የሚከፈል ዋጋ ነው፤ የኢራን የኒውክሌር ስጋት ሲያበቃ ዓለም ደኅንነቷ የተጠበቀ እና ሰላም ስለምትሆን ዋጋው በፍጥነት ይቀንሳል” ሲሉ ጭማሪውን አቃለውታል።

    ከአንድ ሳምንት በፊት አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት ከከፈቱ በኋላ የነዳጅ ዋጋ በ50 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል።

    ኢራን በተከፈተባት ጥቃት ምክንያት እየወሰደችው ባለው የአጸፋ እርምጃ በሆርሙዝ ሰርጥ የሚደረገው የነዳጅ ዝውውር ተገትቷል፤ ይህም ማለት 20 በመቶ የዓለም ነዳጅ አቅርቦት እንዲቋረጥ ሆኗል።

  5. ፑቲን "የአባትዎትን ሥራ እንደሚያስቀጥሉ እተማመናሁ" ሲሉ ለአዲሱ የኢራን መሪ መልዕክት አስተላለፉ

    የሩሲያ ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን

    የፎቶው ባለመብት, Sputnik

    የሩሲያ ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ትናንት ሌሊት ለተመረጡት አዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ የእንኳን ደስ አለዎት መልዕክት አስተላለፉ። ፑቲን፤ ሩሲያ ለኢራን ያላትን "የማይናወጥ አጋርነትም" በድጋሚ አረጋግጠዋል።

    ፑቲን የክሬምሊን ድረ ገጽ ላይ በወጣ መልዕክታቸው፤ “እባክዎት፤ የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ጠቅላይ መሪ ሆነው በመሾምዎ ከልብ የመነጨ የእንኳን ደስ አልዎት መልዕክቴን ይቀበሉኝ” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ፤ ሩሲያ “ለቴህራን ያላትን ድጋፍ እንዲሁም ከኢራናውያን ወዳጆቻችን ጋር ያለንን አጋርነት አረጋግጣለሁ” ብለዋል። “ታማኝ አጋር ሆኖ ለመቀጠልም” ቃል ገብተዋል።

    “ኢራን በትጥቅ የታገዘ አመጻ እየተጋፈጠች ባለችበት በዚህ ጊዜ፤ [በተረከቡት] ከፍተኛ ሥልጣን የሚወስዱት እርምጃ ያለ ምንም ጥርጥር ትልቅ ድፍረት እና ቁርጠኝነት ይጠይቃል” ሲሉ ለአዲሱ ጠቅላይ መሪ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    ፑቲን መልዕክታቸው፤ “የአባትዎን ስራ እና ከፍተኛ መከራ የተደቀነበትን የኢራን ሕዝብ አንድነት በክብር እንደሚያስቀጥሉ እተማመናለሁ” ብለዋል።

  6. የኢራን ሚሳዔሎች አሜሪካ እንደማይደርሱ የቴህራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ተናገሩ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ፤ የአገሪቱ ሚሳዔሎች አሜሪካ እንደማይደርሱ በመግለጽ የፕሬዝዳንት ትራምፕን ንግግር አጣጣሉ።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ፤ ኢራን ላይ ጦርነት የተከፈተበት አንዱ ምክንያት አገሪቱ በቅርቡ አሜሪካ የመድረስ አቅም ያላቸው ሚሳዔሎችን ልትታጠቅ በመሆኑ እንደሆነ ተናግረው ነበር። ትናንት ከአሜሪካው ‘ኤንቢሲ ኒውስ’ ቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ቃለ መጠይቅ ያደረጉት የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የትራምፕን ክስ “ሐሰተኛ መረጃ” ሲሉ አጣጥለዋል።

    አራግቺ፤ “ሚሳዔሎችን የማምረት አቅም አለን፤ ነገር ግን [የሚሳኤሎቹ] ርቀት ከ2,000 ኪሎ ሜትር እንዳይበልጥ ሆነ ብለን ራሳችንን ገድበናል” ብለዋል። “ምክንያቱም በቀሪው ዓለም ባለ የትኛውም አካል እንደ ስጋት መታየት አንፈልግም” ሲሉ ለቴሌቪዥን ጣቢያው ገልጸዋል።

    “ሚሳዔሎቻችን አሁን [የሚወነጨፉበትን] ርቀት ለመጨመር ያስጀመርነው ምንም ዕቅድ የለም” ሲሉም አጽንኦት ሰጥተዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በቃለ መጠይቃቸው ተኩስ አቁም ላይ የመድረስ ሀሳብንም ውድቅ አድርገዋል። አሜሪካ እና እስራኤል “ሰዎችን እየገደሉ ነው፣ ሴት ተማሪዎችን እየገደሉ ነው፣ ሆስፒታል እያጠቁ ነው” ያሉት አራግቺ፤ “ለሕዝባችን ስንል መዋጋት መቀጠል” አለብን ሲሉ ተደምጠዋል።

    አራግቺ፤ አሜሪካ ከተሳተፈችበት የባለፈው ዓመቱ የኢራን እና እስራኤል የ12 ቀናት ጦርነት በኋላ የተደረሰው የተኩስ አቁም መጣሱን ተናግረዋል። አክለውም፤ “እና አሁን በድጋሚ የተኩስ አቁም መጠየቅ ይፈለጋል? እንደዚህ አይሰራም” ብለዋል።

    “ጦርነቱ በዘላቂነት ማብቃት እንዳለበት” ያነሱት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፤ “ያንን እስካላገኘን ድረስ ለሕዝባችን እና ለደኅንነታችን ስንል መዋጋት መቀጠል ያለብን ይመስለኛል” ሲሉ ተናግረዋል።

  7. ዛሬ በመካከለኛው ምሥራቅ የተፈጸሙ ጥቃቶች በምሥል

    ዛሬ ከማለዳው ጀምሮ ኢራን በመካከለኛው ምሥራቅ የተለያዩ አካባቢዎች የድሮን ጥቃት ስትፈጽም እስራኤል በኢራን እና ሊባኖስ በሚገኙ ዒላማዎች ላይ ድብደባ አካሂዳለች።

    የእስራኤል ጦር በቤይሩት ዳሂህ አካባቢ የሔዝቦላህ መሠረተ ልማት ነው ባለው ስፍራ ላይ ድብደባ ፈጽሟል።

    ቀደም ሲል የጦሩ ቃል አቀባይ አቪሻይ አድራኢ ቨቬይሩት በሚገኙ የ"አሸባሪ መሠረተ ልማቶች" ላይ "የኃይል እርምጃ እንወስዳለን" በማለት ነዋሪዎች ከአካባቢው ለቅቀው እንዲወጡ አሳስበው ነበር

    በቤይሩት ደቡባዊ ክፍል በሚገኝ ስፍራ ላይ የእስራኤል ጦር የፈጸመውን ጥቃት ተከትሎ የተነሳ የእሳት ቃጠሎ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በቤይሩት ደቡባዊ ክፍል በሚገኝ ስፍራ ላይ የእስራኤል ጦር የፈጸመውን ጥቃት ተከትሎ የተነሳ የእሳት ቃጠሎ
    በቴህራን በእስራኤል እና በአሜሬካ ትቃት የሞቱ ሰዎች የቀብር ሥነ ስርዓት ተፈጽሟል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በቴህራን በእስራኤል እና በአሜሬካ ትቃት የሞቱ ሰዎች የቀብር ሥነ ስርዓት ተፈጽሟል
    ኢራን ለሊቱን ወደ እስራኤል ያስወነጨፈቻቸው ሚሳዔሎች የባሕር ዳርቻ ከተማ በሆነችው ኔታንያ ሰማይ ላይ ሲታዩ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ኢራን ለሊቱን ወደ እስራኤል ያስወነጨፈቻቸው ሚሳዔሎች የባሕር ዳርቻ ከተማ በሆነችው ኔታንያ ሰማይ ላይ ሲታዩ
    ኢራን በባህሬን በሲትራ ደሴት ባፕኮ ነዳጅ ዘይት ማጣሪያ ላይ የፈጸመችውን የድሮን ጥቃት ተከትሎ ከፍተኛ ጭስ ታይቷል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ኢራን በባህሬን በሲትራ ደሴት ባፕኮ ነዳጅ ዘይት ማጣሪያ ላይ የፈጸመችውን የድሮን ጥቃት ተከትሎ ከፍተኛ ጭስ ታይቷል
    እስራኤል በቤይሩት ደቡባዊ ክፍል ከፈጸመችው ጥቃት በኋላ ጭስ ታይቷል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, እስራኤል በቤይሩት ደቡባዊ ክፍል ከፈጸመችው ጥቃት በኋላ ጭስ ታይቷል
  8. አሥረኛ ቀኑን በያዘው የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት እስካሁን ያሉ ዐበይት ዜናዎች

    ሞጅታባ ኻሜኒ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    • ከ2022 ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ በአንድ በርሜል 120 ዶላር ገብቷል፤ ዶናልድ ትራምፕ ለዓለም ሰላም "የሚከፈል በጣም ትንሽ ዋጋ" ሲሉ ጭማሪው ላይ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
    • ዛሬ ከሰዓት በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪን ጨምሮ የጦርነቱ ኢኮኖሚያዊ ተጽዕኖ ላይ ለመወያየት የቡድን ሰባት የፋይናንስ ሚኒስትሮች አስቸኳይ ስብሰባ ያካሄዳሉ። ደቡብ ኮሪያ በ30 ዓመታት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ የነዳጅ ዋጋ ተመን አውጥታለች።
    • የኢራን የሃይማኖት ሊቃውንት ጉባኤ ሞጅታባ ኻሜኒ አባታቸውን አያቶላህ አሊ ኻሜኒን ተክተው የአገሪቱ አዲሱ ጠቅላይ መሪ እንዲሆኑ መርጧል።
    • የኢራን ሰው አልባ አውሮፕላን በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ የሚፈጽሙትን ጥቃት የቀጠሉ ሲሆን በባህሬን በደረሰው ጥቃት ቢያንስ 32 ሰዎች መቁሰላቸውን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል ።
    • የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት ሌሊቱን በኢራን ላይ ተጨማሪ "የጥቃት ማዕበል" ማካሄዱን አስታውቋል። ጥቃቱ የሚሳኤል ስፍራዎችን እና ሌሎች የአገዛዙ "መሠረተ ልማቶችን" ዒላማ ያደረገ እንደነበር ጨምሮ አስታውቋል። ባለፈው ሳምንት ኢራን ላይ "ወደ 3,400 የሚጠጉ ጥቃቶችን" መፈጸሙንም በመግለጫው ላይ ጠቅሷል።
    • የእስራኤል የአደጋ ጊዜ አገልግሎት እንዳስታወቀው፣ ኢራን በእስራኤል ላይ በፈጸመችው ጥቃት አንዲት ሴት በፍንጥርጣሪ ተመትታ መጠነኛ ጉዳት ደርሶባታል።
    • ኢራን ከሳምንት በፊት በሳዑዲ አረቢያ ላይ የፈጸመችውን ጥቃት ተከትሎ ጉዳት የደረሰበት የአሜሪካ ወታደር መሞቱ ተገልጿል። ይህ እስራኤል እና አሜሪካ ከኢራን ጋር ጦርነት ከጀመሩ ወዲህ የሞቱ የአሜሪካ ወታደሮችን ቁጥር ሰባት ያደርሰዋል።
  9. የቡድን ሰባት አገራት የአደጋ ጊዜ መጠባበቂያ ነዳጅን ስለመልቀቅ ሊወያዩ መሆኑ ተገለጸ

    የነዳጅ ማከማቻ ላይ የተፈጸመ ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Anadolu via Getty Images

    የቡድን ሰባት አገራት፤ ከኢራን ጦርነት ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ከፍተኛ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ ለመቋቋም ከመጠባበቂያ የነዳጅ ክምችታቸው ውስጥ የተወሰነውን በጋራ የመልቀቅ ሀሳብ ላይ ለመወያየት አስቸኳይ ጉባኤ ሊያካሂዱ ነው።

    የነዳጅ ክምችቱን የሚያስተባብረው ዓለም አቀፉ የኢነርጂ ኤጀንሲ ነው። 32 የኤጀንሲው አባላት በነዳጅ ዋጋ ጭማሪ ምክንያት የሚፈጠርን ቀውስ ለማስተዳደር በተዘረጋ የጋራ የአደጋ ጊዜ ስርዓት አማካኝነት ስትራቴጂክ የነዳጅ ክምችት ይዘዋል።

    አሜሪካን ጨምሮ ዋነኛዎቹ ሦስቱ የቡድን ሰባት አገራት በጋራ ነዳጅ የመልቀቅን ሀሳብ እንደደገፉ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ሰዎች መናገራቸውን የአሜሪካው ፋይናንሻል ታይምስ ጋዜጣ ዘግቧል።

    ዘገባው እንደሚያመለክተው በአጠቃላይ ያለው የነዳጅ ክምችት 1.2 ቢሊዮን በርሜል ነው። አሜሪካ ባለሥልጣናት፤ ከዚህ ውስጥ ከ300 እስከ 400 ሚሊዮን በርሜል ያህሉ በጋራ ቢለቀቅ ተገቢ ነው የሚል ሀሳብ እንዳላቸው አንድ ምንጭ ተናግሯል ተብሏል።

    የቡድን ሰባት አገራት ይህንን ስብሰባ የሚያካሂዱት ፕሬዝዳንት ትራምፕ በጦርነቱ መጀመር ምክንያት በከፍተኛ ደረጃ የጨመረውን የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ እንዲያስቆሙ ጫና እየተደረጋቸው ባለበት ጊዜ ነው።

    ከአውሮፓውያኑ 2022 በኋላ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ የተስተዋለበት ነዳጅ በበርሜል 110 ዶላር ገብቷል።

    አሜሪካ እና እስራኤል የከፈቱትን ጦርነት ተከትሎ ኢራን ከዓለም የነዳጅ አቅርቦት አንድ አምስተኛ የሚሆነው የሚጓጓዝበት የሆርሙዝ ወሽመጥ ዘግታለች። በተጨማሪም በዚህ ጦርነት የነዳጅ ማከማቻ እና ማምረቻዎች ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል።

  10. የቻይና የመካከለኛው ምሥራቅ መልዕክተኛ የኢራን ጦርነትን ለማሸማገል ሳዑዲ አረቢያ ገቡ

    የቻይና መንግሥት የመካከለኛው ምሥራቅ ጉዳዮች ልዩ መልዕክተኛ ዣይ ጁን

    የፎቶው ባለመብት, Charly Triballeau via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የቻይና መንግሥት የመካከለኛው ምሥራቅ ጉዳዮች ልዩ መልዕክተኛ ዣይ ጁን

    የቻይና መንግሥት የመካከለኛው ምሥራቅ ጉዳዮች ልዩ መልዕክተኛ የሆኑት ዣይ ጁን አሜሪካ እና እስራኤል ከኢራን ጋር እያካሄዱት ያለውን ጦርነት ለማሸማገል ሳዑዲ አረቢያ ገብተዋል።

    ቤይጂንግ "በባህረ ሰላጤው አካባቢ ሰላምና መረጋጋትን ለማስፈን የማያቋርጥ ጥረት" ለማድረግ ከሪያድ ጋር ለመስራት ዝግጁ መሆኗን የቻይና መንግሥት አስታውቋል።

    ቻይናን "የሳዑዲ አረቢያ ጥሩ ወዳጅ እና አጋር" ሲሉ የገለጹት ዣይ፣ ከሳዑዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፋይሰል ቢን ፋርሃን አል ሳዑድ እና ከባህረ ሰላጤው የትብብር ምክር ቤት (ጂሲሲ) ዋና ፀሐፊ ጃሴም አል ቡዳይዊ ጋር ውይይት ያደርጋሉ።

    ዣይ ከልዑል ፋሲል ጋር በተወያዩበት ወቅት "በቀጣናው ስላለው ውጥረት ትልቅ ስጋት" እንዳላቸው የገለፁ ሲሆን የባህረ ሰላጤው አገራት ሉዓላዊነት፣ ደኅንነት እና የግዛት አንድነት መጣስ እንደሌለበት ተናግረዋል።

    "በንጹኃን ዜጎች እና ወታደራዊ ባልሆኑ ዒላማዎች ላይ የሚሰነዘር ማንኛውም ጥቃት ሊወገዝ እንደሚገባም" ገልጸዋል።

    ዣይ ቤይጂንግ ከዚህ በፊት "ወታደራዊ እንቅስቃሴዎች በአስቸኳይ እንዲቆሙ" ስትል ያቀረበችውን ጥሪም በድጋሚ አቅርበዋል።

  11. አሜሪካ በሳዑዲ አረቢያ የሚገኙ የኤምባሲ ሠራተኞቿን አስወጣች

    ሐሙስ ዕለት ሪያድ ውስጥ የተፈጸመ የኢራን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአስቸኳይ ጊዜ ሠራተኞች ያልሆኑ የአሜሪካ መንግሥት ተቀጣሪዎች እና ቤተሰቦቻቸው በደኅንነት ስጋት ምክንያት ሳዑዲ አረቢያን ለቅቀው እንዲወጡ አዘዘ።

    ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አሜሪካውያን ዜጎች ወደ ሳዑዲ ጉዞ የማድረግ ሀሳባቸውን በድጋሚ እንዲያጤኑትም አሳስቧል። ይህ ውሳኔ የተላለፈው “የኢራን ድሮን እና ሚሳዔል የአሜሪካ ፍላጎቶችን ዒላማ” ያደርጋሉ የሚል ስጋት በመኖሩ እንደሆነ ገልጿል።

    “የትጥቅ ግጭት፣ ሽብር፣ ከአገር የመውጣት ክልከላ እና የማኅበራዊ ሚዲያ እንቅስቃሴን በተመለከተ የአገር ውስጥ ሕግ” የመውጣት እርምጃዎችም በስጋት ምንጭነት ተጠቅሰዋል።

    ኢራን በባሕረ ሰላጤው አገራት ጋር የምትፈጽማቸው የድሮን ጥቃቶች በቀጠሉበት በዚህ ጦርነት የተነሳ አሜሪካ የኤምባሲ ሠራተኞቿን ስታስወጣ ይህ የመጀመሪያው አይደለም። ባለፈው ሳምንት በኩዌት ኤምባሲ የነበሩ ሠራተኞቿን በሙሉ በሙሉ አስወጥታለች።

    በተጨማሪም ሳዑዲ የአየር ኃይል ሰፈሯን ዒላማ ያደረገ ባለስቲክ ሚሳዔል ከኢራን እንደተተኮሰባት ገልጻለች። የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስቴር እንደገለጸው “ወደ ልዑል ሱልጣን የአየር ኃይል ሰፈር የተተኮሰውን” ባለስቲክ ሚሳዔል መክሸፉ እና መውደሙን አስታውቋል።

    ከዚህ አስቀድሞም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ወደ ሪያድ ከተማ ሰሜናዊ ክፍል የተተኮሱ ሁለት የድሮን ጥቃቶችን ማክሸፉን አስታውቆ ነበር።

  12. ትራምፕ እና የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ስታርመር ከተወቃቀሱ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ ተነጋገሩ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ሰር ኪር ስታርመር እአአ በ2025 ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ሰር ኪር ስታርመር እአአ በ2025 ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ ዩናይትድ ኪግደም ከኢራን ጋር ለሚያደርጉት ጦርነት የሰጠችውን ምላሽ ተከትሎ መራር ትችት ከሰነዘሩ በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር ጋር ተነጋገሩ።

    የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ስለመሪዎቹ ንግግር ባወጣው መረጃ በመካከለኛው ምሥራቅ እና በአገራቱ መካከል ስላለው ወታደራዊ ትብብር ተወያይተዋል ብሏል።

    ቅዳሜ ዕለት ፕሬዝዳንቱ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ ዩኬ የአውሮፕላን ተሸካሚዎችን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ለመላክ እያሰበች እንደሆነ በማንሳት "ካሸነፍን በኋላ ጦርነቱን የሚቀላቀሉ ሰዎች አያስፈልጉንም!" ሲሉ ጽፈዋል።

    ብሪታንያንም "በአንድ ወቅት ታላቅ አጋራችን" ነበረች ሲሉ ጠርተዋታል።

    ኪር ስታርመር ቀደም ሲል ዩኬ በኢራን በሚካሄደው ጦርነት ላይ እንደማትሳተፍ ገልጸው ነገር ግን አሜሪካ በኢራን የሚሳዔል ተቋማት ላይ ለምትፈጽማቸው የመከላከል ጥቃቶች የብሪታኒያ ጦር ሰፈሮችን እንድትጠቀም ተስማምተዋል።

    ትራምፕ በኢራን ላይ ለፈጸሙት የመጀመርያ ዙር ጥቃት የዩኬ ጦር ሰፈርን ለመጠቀም ያቀረቡት ጥያቄ ውድቅ ከሆነ በኋላ በጠቅላይ ሚኒስትር ስታርመር ላይ የተሰማቸውን ብስጭት በተደጋጋሚ ገልጸዋል።

    ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ ላይ ትራምፕ "በዩኬ ደስተኛ አይደለሁም" ካሉ በኋላ ስታርመር "ዊንስተን ቸርችልን አይደሉም" ብለዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢቬት ኩፐር እሁድ ዕለት ከቢቢሲ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ኪር ስታርመር "ለብሪታንያ ጥቅም የመቆም መብት አላቸው" በማለት የዩኬ መንግሥት ከፕሬዚዳንቱ ጋር "በእያንዳንዱ ጉዳይ" እንደማይስማሙ ተናግረዋል።

    “የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ለአሜሪካ ብሔራዊ ጥቅም ምን እንደሚያስብ የመወሰን ኃላፊነት አለበት፤ እናም ይህን ማድረግ ያለበት እርሱ ነው” ብለዋል።

    አክለውም “ነገር ግን እንደ ዩኬ መንግሥት የዩኬ ብሔራዊ ጥቅምን የመወሰን ሥራ የእኛ ነው፤ ይህ ማለት ከሌሎች አገሮች ጋር መስማማት ወይም የውጭ ፖሊሲያችንን ለሌሎች አገሮች ጥቅም ማዋል ማለት አይደለም" ሲሉ ተናግረዋል።

  13. የኢራን አብዮታዊ ዘብ አዲስ ለተሾሙት ጠቅላይ መሪ "ሙሉ በሙሉ ለመታዘዝ ዝግጁ" ነኝ አለ

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ አባላት ወታደራዊ ትዕይንት ላይ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ ከአዲሱ ጠቅላይ መሪ የሚመጡ ትዕዛዞችን ያለምንም ማመንታት ለመቀበል እና ለመፈጸም ዝግጁ መሆኑን አስታወቀ።

    የኢራን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ኢሪብ እና የታስኒም የዜና ወኪል አዲስ ስለተሾሙት ሞጅታባ ከአብዮታዊ ዘብ የተሰጠውን መግለጫ አጋርተዋል።

    አብዮታዊ ዘቡ በመግለጫው ሞጅታባ ኻሜኒ “ሁሉን አቀፍ የሕግ ባለሙያ፣ ወጣት አሳቢ እና በፖለቲካዊ እና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ በጣም እውቀት ያላቸው” ሲል ገልጿቸዋል።

    የአብዮታዊ ዘብ አባላቱ ከበላይ መሪው የሚሰጡ ትዕዛዞችን ያለምንም ማመንታት እንደሚቀበሉ “ሙሉ በሙሉ ለመታዘዝ እና ራስን መስዋዕት ለማድረግ ዝግጁ" ናቸው በማለት ለኻሜኒ ያለውን "አክብሮት፣ ታማኝነት እና ታዛዥነት" ገልጿል።

    አሜሪካ እና እስራኤል የካቲት 21/2018 ዓ.ም. በኢራን ላይ በከፈቱት የጋራ ጥቃት ከተገደሉ ከፍተኛ የኢራን ባለሥልጣናት መካከል የአብዮታዊው ዘብ ዋና ጽህፈት ቤት አዛዦች ይገኙበታል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ ከ190 ሺህ በላይ ወታደሮች እንደሚኖረው የሚገመት ሲሆን፤ የራሱን የምድር፣ የባሕር እና የአየር ኃይል አጠናክሯል። ወሳኝ የሚባሉትን የኢራንን ስልታዊ የጦር መሣሪያዎችንም የሚቆጣጠረው ይኸው ኃይል ነው።

  14. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ጦርነቱ የሚቋጨው ከኔትያናሁ ጋር በሚተላለፍ “የጋራ” ውሳኔ መሆኑን ተናገሩ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔትያናሁ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራን ጦርነት መቼ ይጠናቀቃል የሚለው ከእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔትያናሁ ጋር “በጋራ” የሚወሰን እንደሆነ መናገራቸውን ታይምስ ‘ኦፍ ኢስራኤል’ ዘገበ።

    ስለ ጦርነቱ ከኔትያናሁ ጋር “እየተነጋገሩ” መሆኑን በስልክ በተደረገ ቃለ መጠይቅ ለእስራኤሉ መገናኛ ብዙኃን የገለጹት ትራምፕ፤ “ትክክለኛው ጊዜ ላይ ውሳኔ እንደሚያሳልፉ” ተናግረዋል ተብሏል።

    አሜሪካ ጥቃት መፈጸም የምታቆም ከሆነ ኢራን ጦርነቱን መቀጠል ትችል እንደሆነ ለቀረበላቸው ጥያቄ፤ ይህ የመሆን እድል የመኖሩ ጉዳይ ላይ ከመናገር ተቆጥበዋል። “ይሄ አስፈላጊ ይሆናል ብዬ አላስብም” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

    የቀድሞው አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ልጅ የሆኑት ሞጅታባ ኻሜኒ የኢራን ጠቅላይ መሪነትን ሥልጣን ስለ መረከባቸው ለቀረበላቸው ጥያቄም ግልጽ ምላሽ ሳይሰጡ አልፈዋል። “የሚፈጠረውን እናያለን” ብለዋል።

    ከዚህ ቀደም ትራምፕ “ለእኔ የኻሜኒ ልጅ ተቀባይነት የለውም” ሲሉ ሞጅታባ ላይ ያላቸውን ተቃውሞ አሰምተው ነበር።

  15. የአያቶላህ ኻሜኒ ልጅ ሞጅታባ አዲሱ የኢራን ጠቅላይ መሪ ሆነው ተመረጡ

    ሞጅታባ ኻሜኒ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    88 አባላት ያሉት የኢራን የሃይማኖት ሊቃውንት ጉባኤ፤ የአያቶላህ አሊ ኻሜኒ ሁለተኛ ልጅ የሆኑት ሞጅታባ ኻሜኒ የአባታቸውን ቦታ በመተካት አዲሱ የአገሪቱ ጠቅላይ መሪ እንዲሆኑ መረጠ።

    ሞጅታባ ኻሜኒ፤ አሜሪካ እና እስራኤል ከሳምንት በፊት ኢራን ላይ በከፈቱት የመጀመሪያ ዙር ጥቃት የተገደሉትን አባታቸውን ቦታ በመተካት የአገሪቱ መንፈሳዊ መሪነትን እና ከፍተኛውን የሥልጣን ቦታ ይቆጣጠራሉ።

    አዲሱ ጠቅላይ መሪ የአባታቸውን አክራሪ ፖሊሲዎች እንደሚያስቀጥሉ ብዙዎች ይጠብቃሉ።

    የኢራን መንግሥት ቴሌቪዥን ጣቢያ የአዲሱን ጠቅላይ መሪ መመረጥ ባበሰረበት ዘገባ፤ “ከባድ የጦርነት ጊዜ ሁኔታ እና በዚህ ታዋቂ ተቋም ላይ የጠላቶች ቀጥተኛ ዛቻ ቢኖርም” ውሳኔው መተላለፉን ገልጿል።

    የቴሌቪዥን ዜና አቅራቢው፤ የሊቃውንት ጉባኤው “የመረጣ እና የእስላማዊ ስርዓቱን መሪ የማስተዋወቅ ሂደቱን ለደቂቃ እንኳ አላቋረጠም” ብሏል። አክሎም፤ “አላሁ አክበር፣ አላሁ አክባር መሪው ኻሜኒ ናቸው” ሲል ተደምጧል።

    ሹመቱን እንደሚቃወሙ የሚጠበቁት አሜሪካ እና እስራኤል እስካሁን ድረስ ውሳኔውን በተመለከተ አስተያየት አልሰጡም።

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለኢራን አዲስ መሪ የመምረጥ ሂደት ውስጥ ሚና መጫወት እንደሚፈልጉ ተናግረው ነበር።

    ከቀድሞው የአገሪቱ አመራር ጋር ግንኙነት ያለው ሰው ቢመረጥ ሊቀበሉ እንደሚችሉ የጠቆሙት ትራምፕ፤ ሞጅታባ ኻሜኒ ላይ ያላቸውን ተቃውሞ በግልጽ አስቀምጠዋል። “ለእኔ የኻሜኒ ልጅ ተቀባይነት የለውም” ሲሉ ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ ተናግረዋል።

    ሹመቱ ይፋ ከመደረጉ ከሰዓታት አስቀድሞ ደግሞ ያለ እርሳቸው ይሁንታ ሥልጣኑን የሚረከብ ማንም ሰው “ረጅም ጊዜ እንደማይቆይ” በመጥቀስ ዝተዋል።

    እስራኤልም በተመሳሳይ የጠቅላይ መሪነቱን ሥልጣን የሚረከበውን “ሁሉንም ተተኪ ማደኗን እንደምትቀጥል” ተናግራለች።

    የ56 ዓመቱ ሞጅታባ ኻሜኒ ከአባታቸው በተቃራኒም ሕይወታቸውን የመሩት ራሳቸውን በመሸሸግ ነው። ከመጋረጃ ጀርባ ሆነው አገሪቱን ላይ ተጽዕኖ ከሚያሳድሩ ሰዎች እንዱ እንደሆኑ ይገመታሉ።

    በፕሬዝዳንታዊ ምርጫዎች ላይ እጅቸውን እንዳስገቡ፣ የባስጂ ታጣቂዎችን እንደሚያዝዙ እንዲሁም ከእስላማዊ አብዮታዊ ዘቡ ጋር የጠበቀ ግንኙነት እንዳላቸው ይገለጻል።

    በአገሪቱ ውስጥ ከፍ ያለ ተጽዕኖ እንዳላቸው ቢነገርም በእስላማዊ ሪፐብሊኩ ውስጥ አንድም የመንግሥት ሥልጣን ይዘው አያውቁም።

    አያቶላህ አሊ ኻሜኒ እና የእስላማዊ ሪፐብሊኩ መሪ ሩሆላህ ኾሜኒ በአገሪቱ ሥልጣን ላይ በዘር መተካካት ይተቹ ነበር።