በሴኔጋል የጡት እና የማህጸን ጫፍ ካንሰር ህክምና ነጻ ሊደረግ ነው

የፎቶው ባለመብት, SPL
የሴኔጋል መንግሥት በጡትና በማህጸን ጫፍ ካንሰር በሽታዎች ለሚሰቃዩ ሴቶች ከመጪው ጥቅምት ጀምሮ በሁሉም የመንግሥት ሆስፒታሎች ነጻ የኬሞቴራፒ ህክምና ማግኘት እንደሚጀምሩ አስታወቀ።
''በውሳኔው በጣም ተደስተናል፤ ምክንያቱም እነዚህ ሁለት የካንሰር አይነቶ ሴቶችን በብዛት እያጠቁ ያሉ ናቸው'' ብለዋል የሴኔጋል ካንሰር መከላከያ ሊግ ፕሬዝደንት የሆኑት ዶክተር ፋትማ ጉዌኖን።
ከዚህ በተጨማሪ በሌሎች የካንሰር አይነቶች የሚጠቁ ደግሞ ለህክምና ከሚያወጡት ወጪ 60 በመቶ የሚሆነው በመንግሥት እንደሚሸፈን ተገልጿል።
እርምጃው ለብዙዎች ምሳሌ መሆን የሚችል እንደሆነና ምናልባትም በሃገሪቱ ያለውን የሞት መጠን ለመቀነስና ድህነትን ለመዋጋት ቁልፍ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አንድ የዓለም ጤና ድርጅት ባለሙያ ለቢቢሲ ገልጸዋል።
ባለሙያው ዶክተር ባራንጎ ፕሬቦ እንደሚሉት እንደ ሩዋንዳ፣ ናሚቢያ እና ሲሸልስ ያሉ የአፍሪካ ሃገራት ከሴኔጋል ቀድመው ይህንን እርምጃ የወሰዱ ቢሆንም አሁንም ለሌሎች ሃገራት ምሳሌ መሆን ትችላለች።
ነጻ የጡትና የማህጸን ካንሰር ህክምናው ፕሮግራሙን ለማስጀመር የሴኔጋል መንግስት 1.6 ቢሊየን ዶላር መድቢያለሁ ብሏል። እ.አ.አ. በ2015 ደግሞ የማንኛውም ካንሰር ህክምና 30 በመቶ ወጪ መንግሥት ለመሸፈን ተስማምቶ ነበር።
ነገር ግን ካንሰርን በተገቢውና ውጤታማ በሆነ መልኩ ለማከም ብዙ የአፍሪካ ሃገራት ሲቸገሩ ይስተዋላል።
የጡት ካንሰርን ለመመርመር የሚረዳው 'ማሞግራም' የተባለው መሳሪያ በሴኔጋል የሚገኙ ሴቶች በቀላሉ ማግኘት የሚችሉበት ሁኔታ መፈጠር እንዳለበት ዶክተር ፋትማ ጉዌኖን ይናገራሉ።












