የ63 ሚሊዮን ብር መኪና ሰርቆ የተሰወረው ግለሰብ ዱካው ጠፍቷል

2.2 ሚሊየን ዶላር የሚያወጣው መኪና

የፎቶው ባለመብት, Polizei Dusseldorf

የምስሉ መግለጫ, 2.2 ሚሊየን ዶላር የሚያወጣው መኪና

ጀርመን ውስጥ መኪና ለማስተዋወቅ በተዘጋጀ መሰናዶ ላይ ቀርቦ የነበረና 2.2 ሚሊየን ዶላር (63 ሚሊዮን ብር ገደማ) የሚያወጣ መኪና ተሰርቆ እንደነበር ፖሊሶች ይፋ አድርገዋል።

ቅንጡ ከሆኑ ተሽከርካሪዎች አንዱ የሆነው ፌራሪ መኪናን ዘርፏል የተባለው ግለሰብ፤ መሰናዶው ላይ ተገኝቶ መኪናውን ለሙከራ ለመንዳት ጥያቄ ያቀርባል። ግለሰቡ መኪናውን የመግዛት ፍላጎት ስላሳየ መኪናውን ነድቶ እንዲሞክረው ተፈቀደለት።

ግለሰቡ ግን የመኪናውን መሪ ጨብጦ ብዙም ሳይቆይ መኪናውን በፍጥነት እየነዳ ከአካባቢው ተሰውሯል።

ፓሊሶች እንዳሉት፤ መኪናውን ያያችሁ ሰዎች ጠቁሙን የሚል ማሳሳሰቢያ ማስነገራቸውን ተከትሎ መኪናው አንድ ጋራዥ ውስጥ ተደብቆ ተገኝቷል። ተጠርጣሪው ግለሰብ ግን እስካሁን በቁጥጥር ስር አልዋለም።

መኪናውን ለሽያጭ ያቀረበው ድርጅት ኃላፊ እንዳሉት፤ ተጠርጣሪው መኪናውን ይዞ ከመሰወሩ በፊት ለድርጅቱ በተደጋጋሚ ይደውል፣ ኢሜልም ይልክ ነበር።

አየርላንዳዊው የፎርሙላ 1 ተወዳዳሪ ኤዲ አይርቪን በመኪናው እ. አ. አ. ከ1996 እስከ 1999 ተወዳድሮበታል። መኪናው ታሪካዊ እንደመሆኑ በሚሊዮኖች ማውጣቱም ብዙም አያስገርምም።

መሰል መኪናዎች ከአንድ እስከ ሦስት ሚሊየን ዶላር ይሸጣሉ።

የመኪናው አምራች ድርጅት የተሰረቀው ፌራሪ 288 GTO መኪና 272 ብቻ ነበር የሠራው።