በቀጣዩ ስምንት ዓመት ቻይና በምጣኔ ሃብት አሜሪካን ትበልጣለች ተባለ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ቻይና በፈረንጆቹ 2028 በዓለም ትልቁ የምጣኔ ሃብት ባለቤት በመሆን አሜሪካን ልትቀድማት እንደምትችል ተገምቷል።
ከዚህ ቀደም ቻይና አሜሪካን በ2033 ነበር ትቀድማታለች ተብሎ የተገመተው።
መቀመጫውን ዩናይትድ ኪንግደም ያደረገው የምጣኔ ሃብት እና ቢዝነስ ጥናት ማዕከል ነው ይህን የገመተው።
ማዕከሉ እንደሚለው ቻይና ኮቪድ-19ኝን የተቋመመችበት መንገድ ዕድገቷን ሊያፋጥን ይችላል።
በተቃራኒው አሜሪካና አውሮፓ በኮሮናቫይረስ ክፉኛ መደቆሳቸው ጉዳት አለው ተብሏል።
በሌላ በኩል ሕንድ በ2030 ከዓለም ሦስተኛዋ ታላቅ ምጣኔ ሃብት ያላት አገር ትሆናለች ተብሎ ተገምቷል።
ማዕከሉ በየዓመቱ ታኅሣሥ ወር ላይ የምጣኔ ሃብት ግምትና ትንታኔ ያወጣል።
ምንም እንኳ ቻይና በኮቪድ-19 የተመታች የመጀመሪያዋ አገር ብትሆንም በሽታውን በተሳካ ሁኔታ በቁጥጥር ሥር ማዋል ችላለች።
ነገር ግን የአውሮፓ አገራት ሰዎች ከቤታቸው እንዳይወጡ እግድ ጥለዋል። ይህ ደግሞ ምጣኔ ሃብታቸው ላእ ከፍ ያለ ጉዳትን ያስከትላል ይላል ትንታኔው።
ቻይና ሌሎች አገራት እንዳጋጠማቸው የምጣኔ ሃብት ድቀት ውስጥ አልገባችም። እንዲያውም ዘንድሮ 2 በመቶ ዕድገት ታመጣለች ተብሎ ይጠበቃል።
የዩናይትድ ስቴትስ ምጣኔ ሃብት ደግሞ በተቃራኒው በወረርሽኙ እጅጉን ተመቷል፤ ከ300 ሺህ በላይ ሰዎችም በቫይረሱ ምክንያት ሞተዋል።
አሜሪካ ወረርሽኙ ያመጣባትን ድቀት በገንዘብ ፖሊሲና ለዜጎቿ ድጎማ በማድረግ ብትሸፍነው ብታስብም ለሁለተኛ ጊዜ ሊደረግ በታሰበው ድጎማ ላይ ፖለቲከኞች አለመስማማታቸው ጉዳቱ የከፋ እንዲሆን ሊያደርገው ይችላል የሚል ስጋት አስከትሏል።
ይህ ጉዳይ ሊጠናቀቅ ቀናት በቀሩት የፈረንጆቹ አዲስ ዓመት 14 ሚሊዮን ሥራ አጥ አሜሪካዊያንን ያለ ድጎማ ሊያስቀራቸው ይችላል።
ማዕከሉ ያወጣው ዘገባ እንደሚለው ቻይና እና አሜሪካ ለዓመታት የምጣኔ ሃብት የበላይነቱን ለመቆጣጠር ሲፎካከሩ ከርመዋል።
ነገር ግን የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ተከትሎ የመጡ ለውጦች እንደሚያሳዩት ቻይና የመጪው ጊዜ የዓለማችን ቁንጮ ናት።
ዘገባው እንደሚተነብየው ከሆነ ድኅረ-ኮቪድ-19 ባለው ጊዜ ውስጥ የአሜሪካ ምጣኔ ሃብት ከ2022 አስከ 2024 ድረስ ባለው ጊዜ 1.9 በመቶ ያድጋል። ከዚያ በኋላ ደግሞ ወደ 1.6 በመቶ ይወርዳል።
በተቃራኒው የቻይና ምጣኔ ሃብት እስከ 2025 ድረስ በ5.7 በመቶ ያድግና ከ2026 ወዲያ ባለው ጊዜ 4.5 በመቶ ያድጋል ይላል።
ቻይና በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላት የምጣኔ ሃብት ድርሻ በፈረንጆቹ 2000 ዓመት ላይ 3.6 ነበር። ዘንድሮ ግን ወደ 17.8 አድጓል።
ቻይና በ2023 ከፍተኛ ገቢ ያላት አገር እንደምትሆን ነው የማዕከሉ ምክትል ሊቀመንበር ዳግላስ ማክዊሊያምስ የሚናገሩት።
ምንም እንኳ የቻይና ምጣኔ ሃብት ከአሜሪካ ሊበልጥ እንደሚችል ይገመት እንጂ፤ የአንድ ቻይናዊ አማካይ ገቢ ግን ከአንድ አሜሪካዊ ጋር ሲነፃፀር ዕድገት ላያሳይ ይችላል ተብሏል።















