ፑቲን ሩሲያ በመካከለኛው ምሥራቅ ሰላም ለማምጣት ማንኛውንም ነገር ታደርጋለች አሉ

የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock
የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ለኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አገራቸው በመካከለኛው ምሥራቅ ሰላም ለማምጣት ማንኛውንም ነገር እንደምታደርግ መናገራቸውን ታስ የዜና ወኪል ዘገበ።
የሩሲያ ብሔራዊ የዜና ወኪል ታስ፣ የሩሲያው ፕሬዚዳንት ለቴህራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ የኢራን ሕዝቦች ለሉዓላዊነታቸው በድፍረት መታገላቸውን እንደተናገሩ ዘግቧል።
ታስ አክሎም ፑቲን ኢራን ይህንን አስቸጋሪ ጊዜ ካለፈች በኋላ ሰላም እንደምትፈልግ ያላቸውን ተስፋ መግለጣቸውን ጠቅሷል።
የዜና ኤጀንሲው ፑቲን ለኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራጋቺ፣ ሩሲያ “በመካከለኛው ምሥራቅ በተቻለ ፍጥነት ሰላም ለማምጣት ማንኛውንም ነገር እንደምታደርግ” መናገራቸውን ዘግቧል።
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በበኩላቸው በሞስኮ እና በቴህራን መካከል ያለው ግንኙነት "እየተጠናከረ የሚሄድ" ስትራቴጂካዊ አጋርነት መሆኑን መናገራቸውን የሩሲያ የመንግሥት ቴሌቪዥን ዘግቧል።
የሩሲያውን ፕሬዚዳንት ለማነጋገር ወደ ሞስኮ የተጓዘው የኢራን ልዑካን ቡድን ውስጥ ምክትል የውጭጉዳይ ሚኒስትር ካዜም ጋሪባባዲ እና በሞስኮ የኢራን አምባሳደር ካዜም ጃላሊ ይገኙበታል።
የክሬምሊን ቃል አቀባይ ዲሚትሪ ፔስኮቭ ሩሲያ ቴህራን እና ዋሺንግተን በሚያደርጉት ቀጣይ ድርድሮች "በሁለቱም ወገኖች ተቀባይነት ያለው የማደራደር አገልግሎት" ለማቅረብ ዝግጁ መሆኗን ተናግረዋል።
“የተረጋገጠ ሰላም፤ በዘላቂነት የሚቆይ እና ወደ ግጭት ዳግም መመለስ የሌለበት ሰላምን ለማረጋገጥ ማንኛውንም ነገር ለማድረግ ዝግጁ ነን” ሲሉ መናገራቸውን መገናኛ ብዙኃኑ ዘግቧል።










