ቀጥታ, ከፕሬዚዳንት ፑቲን ጋር የተገናኙት የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ድርድሩ ላለመሳካቱ አሜሪካን ወቀሱ

ወደ ሩሲያ ያመሩት የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ በፓኪስታን ሲደረግ የነበረው የሰላም ድርድር ያልተሳካው አሜሪካ ባቀረበቻቸው ከልክ ያለፉ ጥያቄዎች ምክንያት ነው ሲሉ ለመገናኛ ብዙኃን ተናገሩ። በሩሲያዋ ሴንት ፒተርስፐርግ ከተማ ያረፉት አራግቺ በመካከለኛው ምሥራቅ የሚደረገውን ጦርነት በተመለከተ ከሩሲያ አጋሮች ጋር እንደሚነጋገሩ በፐርሺያ ቋንቋ በሰጡት ቃለ መጠይቅ ገልጸዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ፑቲን ሩሲያ በመካከለኛው ምሥራቅ ሰላም ለማምጣት ማንኛውንም ነገር ታደርጋለች አሉ

    የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን እና የኢራኑ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ለኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አገራቸው በመካከለኛው ምሥራቅ ሰላም ለማምጣት ማንኛውንም ነገር እንደምታደርግ መናገራቸውን ታስ የዜና ወኪል ዘገበ።

    የሩሲያ ብሔራዊ የዜና ወኪል ታስ፣ የሩሲያው ፕሬዚዳንት ለቴህራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ የኢራን ሕዝቦች ለሉዓላዊነታቸው በድፍረት መታገላቸውን እንደተናገሩ ዘግቧል።

    ታስ አክሎም ፑቲን ኢራን ይህንን አስቸጋሪ ጊዜ ካለፈች በኋላ ሰላም እንደምትፈልግ ያላቸውን ተስፋ መግለጣቸውን ጠቅሷል።

    የዜና ኤጀንሲው ፑቲን ለኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራጋቺ፣ ሩሲያ “በመካከለኛው ምሥራቅ በተቻለ ፍጥነት ሰላም ለማምጣት ማንኛውንም ነገር እንደምታደርግ” መናገራቸውን ዘግቧል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በበኩላቸው በሞስኮ እና በቴህራን መካከል ያለው ግንኙነት "እየተጠናከረ የሚሄድ" ስትራቴጂካዊ አጋርነት መሆኑን መናገራቸውን የሩሲያ የመንግሥት ቴሌቪዥን ዘግቧል።

    የሩሲያውን ፕሬዚዳንት ለማነጋገር ወደ ሞስኮ የተጓዘው የኢራን ልዑካን ቡድን ውስጥ ምክትል የውጭጉዳይ ሚኒስትር ካዜም ጋሪባባዲ እና በሞስኮ የኢራን አምባሳደር ካዜም ጃላሊ ይገኙበታል።

    የክሬምሊን ቃል አቀባይ ዲሚትሪ ፔስኮቭ ሩሲያ ቴህራን እና ዋሺንግተን በሚያደርጉት ቀጣይ ድርድሮች "በሁለቱም ወገኖች ተቀባይነት ያለው የማደራደር አገልግሎት" ለማቅረብ ዝግጁ መሆኗን ተናግረዋል።

    “የተረጋገጠ ሰላም፤ በዘላቂነት የሚቆይ እና ወደ ግጭት ዳግም መመለስ የሌለበት ሰላምን ለማረጋገጥ ማንኛውንም ነገር ለማድረግ ዝግጁ ነን” ሲሉ መናገራቸውን መገናኛ ብዙኃኑ ዘግቧል።

  2. የሊባኖስ ፕሬዚዳንት የተኩስ አቁሙን በመጣስ ሄዝቦላህን ተቹ

    የእስራኤል እና የሊባኖስ ባንዲራዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የሊባኖስ ፕሬዚዳንት ጆሴፍ አውን ከእስራኤል ጋር የሚደረገውን ጦርነት ለማስቆም በሚያደርጉት ጥረት “የሚያሳፍር ስምምነት” እንደማይቀበሉ ገለፁ።

    ፕሬዚዳንቱ በመግለጫቸው ከድርድሩ መጀመርያው ጀምሮ ለአሜሪካ “የተኩስ አቁም አስፈላጊ የመጀመርያ እርምጃ” መሆኑን መናገራቸውን ገልጸዋል።

    አክለውም በደቡባዊ ሊባኖስ የሚኖሩ “የሌሎች ጦርነትን ዋጋ በግዛታችን ላይ እየከፈሉ ነው” ብለዋል።

    እስራኤል እና ሊባኖስ የደረሱት የተኩስ አቁም በሦስት ሳምንት የተራዘመው ባለፈው ሳምንት ነው።

    ነገር ግን እስራኤል እና በኢራን የሚደገፈው ሄዝቦላህ የሚያደርጉት ውጊያ ቀጥለዋል።

    ሄዝቦላህ በቀጠናው ስላለው ሰላም በሚደረግ ድርድር ላይ አልተካተተም።

    ኦውን ጦርነቱ የተካሄደው “ለሊባኖስ ተብሎ ቢሆን” እደግፈው ነበር፤ ነገር ግን “ጦርነቱ የሚካሄደው የሌሎችን ፍላጎት ለማሳካት ሲሆን ሙሉ በሙሉ ውድቅ አደርገዋለሁ” ብለዋል።

    “እኛ እያደረግን ያለነው የአገር ክህደት አይደለም፤ ይልቁንም የአገር ክህደት የሚፈጸመው የውጭ ጥቅሞችን ለማስከበር አገራቸውን ወደ ጦርነት በወሰዱት ነው” ሲሉ ሄዝቦላህን ሸንቁጠዋል።

    በደቡባዊ ሊባኖስ የእስራኤል የአየር ድብደባ እንደቀጠለ ነው። እሁድ ዕለት ብቻ በእስራኤል የአየር ድብደባ 14 ሰዎች ሲገደሉ ሁለት ሕጻናት እና ሁለት ሴቶችን ጨምሮ 37 ሰዎች መጎዳታቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።

    ቅዳሜ ዕለት የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ የአገሪቱ ጦር ሊባኖስ ውስጥ የሚገኙ “የሄዝቦላህ ዒላማዎችን በኃይለኛው እንዲያጠቁ” ትዕዛዝ ሰጥተዋል። በዚሁ ዕለት ደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ በተፈጸሙ ጥቃቶች ስድስት ሰዎች ተገድለዋል።

  3. የኢራን ባለሥልጣናት በጦርነቱ የፈራረሱ ሕንጻዎችን ለመጽዳት 200,000 መኪናዎች ያስፈልጋሉ አሉ

    ፍርስራሽ እያነሳ የጭነት መኪና ላይ የሚጭን ኤክስካቬተር

    የፎቶው ባለመብት, SM

    የኢራን አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን በጦርነት ምክንያት የፈራረሱ የመኖሪያ ሕንጻዎችን ለማጽዳት “200 ሺህ የጭነት መኪናዎች” ያስፈልጋሉ አለ።

    የአካባቢ ጥበቃ ምክር ቤት አባል የሆኑት አቡ አሊ ጎልዛሪ እስራኤል እና አሜሪካ በፈጸሙት የአየር ድብደባ “በሺህዎች የሚቆጠሩ የመኖሪያ ሕንጻዎች ወድመዋል፤ እንዲሁም 10 ሚሊዮን ቶን ፍርስራሾች ተቆልለዋል። በተጨማሪም ይህንን ፍርስራሽ ለማንሳት ወደ 200,000 የጭነት መኪናዎች እንፈልጋለን” ብለዋል።

    ጎልዛሪ አክለውም “በኢራን ውሃ፣ አፈር፣ አየር እና የብክለት አስተዳደርን ጨምሮ ከባድ የሆነ የአካባቢ ጥበቃ ቀውስ ገጥሞናል። እነዚህ ደግሞ በጦርነቱ ምክንያት የተባባሱ ናቸው” ብለዋል።

  4. ክሬምሊን ከኢራን ጋር የሚደረገው ውይይት በጣም ጠቃሚ መሆኑን ገለጸች

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚንስትር አባስ አራግቺ ከፕሬዚዳንት ፑቲን ጋር ለመወያየት ሰኞ ዕለት ሞስኮ ደርሰዋል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚንስትር አባስ አራግቺ ከፕሬዚዳንት ፑቲን ጋር ለመወያየት ሰኞ ዕለት ሞስኮ ደርሰዋል

    የሩሲያው ፕሬዚዳንት ከኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስተር አባስ አጋራቺ ጋር ዛሬ በሴንት ፒተስበርግ እንደሚገናኙ ክሬምሊን አስታወቀ።

    የክሬምሊን ቃል አቀባይ ዲሚትሪ ፔስኮቭ ለመንግሥት የዜና ወኪል ታስ እንደተናገሩት "ይህ ውይይት በጣም አስፈላጊ መሆኑን በኢራን እና በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው ሁኔታ እንዴት እየጎለበተ ነው የሚለውን በመመልከት መናገር ይቻላል" ብለዋል።

    አራጋቺ አገራቸው ጦርነቱን ይቋጫል ተብሎ ተስፋ የተጣለበት ንግግር ከአሜሪካ ጋር ማድረግ ሳትችል ከቀረች በኋላ ወቅት ሰኞ ማለዳ ሩሲያ ደርሰዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን የሚያደርጉት ሁለተኛው ዙር የሰላም ንግግር ቅዳሜ ዕለት ፕሬዚዳንት ትራምፕ ልዑካኖቻቸው ወደ ኢዝላማባድ እንዳይሄዱ ካደረጉ በኋላ ባለበት ቆሟል።

  5. ኦማን ከቴህራን ጋር በሆርሙዝ ላይ ባላቸው “የጋራ” ኃላፊነት ላይ መነጋገራቸውን አስታወቀች

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ እሁድ ዕለት በሙስካት የኦማንን ሱልጣን ሃይታም ቢን ታሪቅን አነጋግረዋል

    የፎቶው ባለመብት, IRANIAN FOREIGN MINISTRY/HANDOUT/EPA/Shutterstock

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ እሁድ ዕለት በሙስካት የኦማንን ሱልጣን ሃይታም ቢን ታሪቅን አነጋግረዋል

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ወደ ሩሲያ ከማምራታቸው በፊት እሁድ ዕለት ኦማን ደርሰው ከአገሪቱ መሪ እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር መወያየታቸው ታውቋል።

    የኦማን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ባድር አልቡሳይዲ በኤክስ ገጻቸው ላይ ከአባስ አረጋቺ ጋር በሆርሙዝ ወሽመጥ ዙሪያ “ጥሩ ውይይት” ማድረጋቸውን ገልጸዋል።

    አክለውም ሁለቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች በወሽመጡ ላይ “ለዓለም አቀፉ ማኅበረስብ ስለሚኖር የጋራ ኃላፊነት እንዲሁም ለረዥም ጊዜ መንቀሳቀሻ አጥተው ለተቀመጡ ባህረተኞች ስለሚያስፈልግ አስቸኳይ የሰብዓዊ እርዳታ” መነጋራቸውን አስታውቀዋል።

    የኢራን ከፍተኛ ዲፕሎማት “ኦማን በክብር ተቀብላ ስላስተናገደችኝ” በማለት አመስግነዋል።

    አራጋቺ በማኅበራዊ ሚዲያ ልጥፋቸው ላይ ንግግራቸው ቁልፍ በሆነው የሆርሙዝ ወሽመጥ የመርከቦች እንቅስቃሴ “ደህንነቱ የተጠበቀ እንዲሆን” መነጋገራቸውን ገልጸዋል።

  6. ወደ ሩሲያ የተጓዙት የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ድርድሩ ላለመሳካቱ አሜሪካ ያቀረበቻቸውን ጥያቄዎች ወቀሱ

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ሩሲያ የተደረገላቸው አቀባበል

    የፎቶው ባለመብት, Iranian Foreign Ministry/Getty Images

    ወደ ሩሲያ ያመሩት የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ በፓኪስታን ሲደረግ የነበረው የሰላም ድርድር ያልተሳካው አሜሪካ ባቀረበቻቸው ከልክ ያለፉ ጥያቄዎች ምክንያት ነው ሲሉ ለመገናኛ ብዙኃን ተናገሩ።

    በሩሲያዋ ሴንት ፒተርስፐርግ ከተማ ያረፉት አራግቺ በመካከለኛው ምሥራቅ የሚደረገውን ጦርነት በተመለከተ ከሩሲያ አጋሮች ጋር እንደሚነጋገሩ በፐርሺያ ቋንቋ በሰጡት ቃለ መጠይቅ ገልጸዋል።

    ከሩሲያ በፊት ወደ ፓኪስታን አቅንተው የነበሩት ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በኢስላማባድ የነበራቸው ቆይታ በምን አይነት ሁኔታ ውስጥ ድርድሩ ሊቀጥል ይችላል የሚለው ላይ ያተኮረ እንደነበር አስረድተዋል።

    አራግቺ በቃለ መጠይቃቸው በኢራን ስለተዘጋው የሆርሙዝ ወሽመጥ አንስተዋል። በወሳኙ የባሕር መስመር በኩል ደኅንነቱ የተጠበቀ ጉዞ ማድረግ ዓለም አቀፍ ጉዳይ ሆኖ መቀጠሉን የጠቀሱት ጠቅሰዋል።

    እንደ ኦማን ያሉ ጎረቤት አገራት ወሽመጡን በተመለከተ ከኢራን ጋር ባላቸው የጋራ ፍላጎት ላይ እንዲሰሩ ጠይቀዋል።

    ኢራን እና ኦማንን የሚያስማሙ በርካታ ነጥቦች መኖራቸውን ጠቁመውም፤ ሁለቱ አገራት ሆርሙዝን በተመለከተ ተጨማሪ ንግግር ለማድረግ ስምምነት ላይ እንደደረሱ ተናግረዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በሩሲያ ቆይታቸው ከፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር እንደሚገናኙ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ዘግቧል።

    የፓኪስታን ቆይታቸውን “እጅግ ውጤታማ” ሲሉ የገለጹት አራግቺ፤ “ኢራን ላይ የተከፈተውን ጦርነት በዘላቂነት ለመቋጨት የሚያስችል ማዕቀፍን በተመለከተ የኢራንን አቋም” ማሳወቃቸውን ጠቅሰዋል።

    “እውነትም አሜሪካ ዲፕሎማሲን በቁም ነገር ትወስደው እንደሆነ እናያለን” ሲሉ ቅዳሜ ዕለት በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ጽፈዋል።

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው ኢራን መደራደር ከፈለገች በስልክ መነጋገር እንደሚቻል እና ልዑካኖቻቸውን ወደ ፓኪስታን እንደማይልኩ ተናግረዋል።

  7. “መቼ ወደ ቤታቸው እንደሚመለሱ እርግጠኛ አይደሉም” - በሆርሙዝ መውጫ ያጡት ባሕርተኞች

    ባሕርተኞች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የነዳጅ ጫኝ መርከብ ኩባንያዎች ማኅበር መረጃ እንደሚያመለክተው በሺህዎች የሚቆጠሩ ባሕርተኞች እና ከ105 በላይ መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ መዘጋት ምክንያት መንቀሳቀስ አልቻሉም።

    ኢራን ከዓለም ነዳጅ እና ፈሳሽ የተፈጥሮ ጋዝ 20 በመቶው በሚጓጓዝበት ይህ የባሕር መስመር አሜሪካ እና እስራኤል በፈጸሙት “ግልጽ የተኩስ አቁም ጥሰት” ምክንያት እንደማይከፈት አስታውቃለች።

    ከቢቢሲ ‘ቱዴይ’ ፕሮግራም ጋር ቆይታ ያደረጉት ‘ኢንተርታንኮ’ የተሰኘው የነዳጅ ጫኝ መርከቦች ማኅበር ማኔጂንግ ዳይሬክተር ቲም ዊልኪንስ፤ የወሽመጡ መዘጋት በኢራን ባሕር ዳርቻ መንቀሳቀሻ ያጡ ባሕርተኞች ላይ ያደረሰውን ተጽዕኖ አስረድተዋል።

    ዊልኪንስ እንደሚናገሩት፤ የመርከብ ሠራተኞች እንደ ምግብ፣ ውሃ ማቅረብ እንዲሁም ቆሻሻዎችን እንደማስወገድ ያሉ መሠረታዊ ተግባራት የማስተዳደር ኃላፊነት ስላለባቸው “ከፍተኛ የሆነ ጭንቀት፣ ውጥረት እና መታከት” ተፈጥሮባቸዋል።

    “ብዙዎቹ መቼ መመለስ እንደሚችሉ ምንም እርግጠኝነት ሳይኖራቸው መርከብ ላይ መውጫ አጥተዋል” ብለዋል።

    በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የተኩስ አቁም ስምምነት ቢደረስም አሁንም በቀጣናው ግጭቶች ቀጥለዋል።

    ባለፈው ሳምንት ኢራን ሁለት በወሽመጡ ሊያልፉ የነበሩ የጭነት መርከቦች “ለምርመራ” መያዟን ገልጻለች። በወሽመጡ ለማለፍ የሞከሩ ሌሎች መርከቦችም ጥቃት እንደተከፈተባቸው ተዘግቧል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ ጉዞዎችን ያገደችው አሜሪካም በርካታ መርከቦችን ጠልፋለች።

  8. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ራት ግብዣው ላይ ተኩስ ሲከፈት “አልሰጋሁም ነበር” አሉ

    የደኅንነት አባላት ትራምፕን ሲያስወጡ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ቅዳሜ ምሽት ሲካሄድ በነበረው የጋዜጠኞች ራት ግብዣ ላይ የተከፈተው ተኩስ ፕሬዝዳንቱን እና ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልታናትን ዒላማ በማድረግ እንደሆነ ቢታመንም ዶናልድ ትራምፕ በወቅቱ “ሰግተው እንዳልነበረ” ተናግረዋል።

    ትራምፕ ከሲቢኤስ ኒውስ ’60 ሚኒትስ’ የቴሌቪዥን ፕሮግራም ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ “አልሰጋሁም ነበር። ሕይወትን እረዳለሁ። የምንኖረው ያበደ ዓለም ውስጥ ነው” ብለዋል።

    የዋይት ሀውስ ዘጋቢ ጋዜጠኞች ራት ግብዣ ላይ የተፈጠረው ክስተት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ላይ እንደተቃጣ ሦስተኛ የግድያ ሙከራ ተወስዷል። ሐምሌ 2016 ዓ.ም. ፔንስልቬኒያ ውስጥ የምርጫ ቅስቀሳ በሚያደርጉበት ሰዓት እንዲሁም ባለፈው መስከረም ላይ በጎልፍ ክለባቸው ውስጥ የግድያ ሙከራ ተደርጎባቸዋል።

    ምክትል ፕሬዝዳንቱ ጄዲ ቫንስ በመጀመሪያ እንዲወጡ የተደረገበት የቅዳሜው ጥቃት እንዴት እንደተከሰተ ትራምፕ ተጠይቀዋል። ፕሬዝዳንቱ የሴክሬት ሰርቪስ አባላት ከክፍሉ እንዲያስወጧቸው ሁኔታዎች “ቀላል እንዳላደረጉ” በመጥቀስ ምላሽ ሰጥተዋል።

    “ምን እንደተፈጠረ መመልከት ፈልጌ ነበር… ምን እየተካሄደ መሆኑን ማየት ፈልጌ ነበር። ሁኔታውን በተገነዘብኩበት ሰዓት፤ ምናልባትም መጥፎ ሁኔታ ነበር” ብለዋል።

    ከክፍሉ ሲወጡ “እንዲያጎነብሱ” ስለመደረጉ የተነሳላቸው ትራምፕ፤ “[ከደኅንነት አባላት ጋር] መራመድ ጀመርኩ። ዞርኩ፣ መራመድ ጀመርኩ፤ ከዚያም ‘እባክህ አጎንብስ፣ እባክህ ወደ ወለሉ አጎንብስ’ አሉኝ” በማለት ሁኔታውን ገልጸዋል።

    “ስለዚህ አጎነበስኩ፤ ቀዳማዊት እመቤቷም አጎነበሰች” ሲሉም አክለዋል።

    በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ከተጠርጣሪው ኮል አለን ጋር ግንኙነት እንዳለው የሚታመን በእጅ የተጻፈ ሰነድን ተመልክቷል። ሰነዱ፤ “ከከፍተኛ ደረጃ እስከ ታች” ያሉ የትራምፕ አስተዳደር አባላትን ዒላማ ማድረግ እንደሚፈልግ ያሳያል።

    ጽሑፉ ላይ “የህጻናት ወሲብ ጥቃት ፈጻሚ፣ ደፋሪ እና ከሃዲ” በሚል ስለሰፈሩት አገላለጾች በቃለ መጠይቁ በተነሳበት ወቅት በትራምፕ እና በጋዜጠኛዋ ኖራህ ኦ’ዶኔል መካከል ውጥረት ተስተውሎ ነበር።

    ጋዜጠኛዋ ስለ እነዚህ አገላለጾች በመጠየቋ “ወራዳ” ሲሉ ጠርተዋታል። “ይህንን በማንበብሽ ልታፍሪ ይገባል፤ ምክንያቱም እኔ ከእነዚህ ነገሮች አንዱንም አይደለሁም” ብለዋል።

  9. ኢራን ሆርሙዝ እንዲከፈት እና የኒውክሌር ንግግር እንዲዘገይ የሚጠይቅ እቅድ ለአሜሪካ ማቅረቧ ተዘገበ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥ እንዲከፈት እና ጦርነቱ እንዲቋጭ፤ የኒውክሌር ጉዳይ ግን በስምምነቱ ቀጣይ ደረጃ ንግግር እንዲደረግበት የሚጠይቅ የሰላም እቅድ ማቅረቧን የአሜሪካው የዜና ምንጭ አክሲዮስ ዘገበ።

    አክሲዮስ አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣንን እና ከጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮችን ጠቅሶ ያወጣው ዘገባ እንደሚያስረዳው፤ ኢራን እቅዱን ያቀረበችው በአሸማጋይዋ ፓኪስታን በኩል ነው።

    እቅዱ በዋነኛነት የሚያተኩረው ከሁሉም በፊት በሆርሙዝ ወሽመጥ እና አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ ጉዞዎች ላይ በጣለችው እገዳ ምክንያት ለተፈጠረው ቀውስ መፍትሔ ማበጀት ላይ ነው።

    በዚህም መሠረት የተኩስ አቁሙ ለረጅም ጊዜ እንዲራዘም ወይም ሁለቱ አገራት በቋሚነት ጦርነት ለማቆም እንዲስማሙ የሚጠይቅ ሀሳብ እቅዱ ውስጥ መካተቱን ዘገባው ጠቅሷል።

    በኢራን እቅድ መሠረት የኒውክሌር ድርድር የሚጀመረው የሆርሙዝ ወሽመጥ ከተከፈተ እና የአሜሪካ እገድ ከተነሳ በኋላ ነው።

    ዋይት ሀውስ የኢራን እቅድ የደረሰው ሲሆን የትራምፕ አስተዳደር የኢራንን እቅድ ይመለከተው እንደሆነ አለመታወቁን አክሲዮስ ዘገቧል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ በሳምንቱ መጨረሻ ወደ ፓኪስታን ሲጓዙ ከአሜሪካ ጋር የሚደረገው ንግግር በድጋሚ ይጀምራል የሚል ተስፋን ጭሮ ነበር። አራግቺ እንደተጠበቀው ከአሜሪካ ልዑካን ጋር ባይነጋገሩም ስለ ሰላም ድርድር ማንሳታቸውን ዘገባው ጠቅሷል።

    አክሲዮስ እንዳስነበበው ከሆነ፤ አራግቺ በኢስላማባድ ቆይታቸው የኒውክሌር ጉዳይን ወደ ጎን የማድረግ ሀሳብን አንስተዋል።

    አክሲዮስ ያነጋገራቸው አንድ ምንጭ የአሜሪካ ጥያቄ የሚመለስበትን መንገድ በተመለከተ በኢራን አመራር መካከል ስምምነት አለመኖሩን አራግቺ ለፓኪስታን፣ ግብጽ፣ ቱርክ እና ኳታር አሸማጋዮች መናገራቸው ገልጸዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው ከኢራን ጋር ለሚደረግ ድርድር ልዑካኖቻቸውን እንደማይልኩ እና በስልክ ንግግር ማድረግ እንደሚቻል ተናግረዋል።

  10. እስራኤል ሊባኖስ ውስጥ በፈጸመችው ጥቃት 14 ሰዎች ተገደሉ

    ሊባኖስ ውስጥ የተፈጸመ ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    እስራኤል እሁድ ዕለት ሊባኖስ ውስጥ በፈጸመችው ጥቃት 14 ሰዎች ሲገደሉ፤ ሁለት ሕጻናት እና ሁለት ሴቶችን ጨምሮ 37 ሰዎች መጎዳታቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር ገለጸ።

    የደረሰው ጉዳት ከመገለጹ አስቀድሞ የእስራኤል ጦር ቃል አቀባይ በተለያዩ የደቡባዊ ሊባኖስ መንደሮች የሚገኙ ነዋሪዎች ለቅቀው እንዲጡ አስጠንቅቀው ነበር።

    ነዋሪዎች በአፋጣኝ “መውጣት እንዳለባቸው” የሚያስጠነቅቅ መልዕክት የጻፈው ጦሩ፤ እዚያው መቆየት “ሕይወታቸውን አደጋ ላይ እንደሚጥለው” ገልጿል።

    የእስራኤል ጦር ከቆይታ በኋላ የሄዝቦላህ ወታደሮች እና “የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት ወታደሮች ላይ ጥቃት ለመፈጸም” ይውላሉ ያላቸው የደቡባዊ ሊባኖስ ስፍራዎችን “በከባድ መሣሪያ እና የአየር ጥቃት” መምታቱን አስታውቋል።

    ሄዝቦላህ በፈጸመው ጥቃት የ19 ዓመት የእስራኤል ወታደር መገደሉን እና ስድስት ሰዎች መቁሰላቸውንም ገልጿል።

    እስራኤል እና ሊባኖስ ለሦስት ሳምንት የሚቆይ ተኩስ አቁም ተግባራዊ እንዲሆን ባለፈው ሳምንት ሐሙስ ዕለት መስማማታቸው ይታወሳል።

    ይህ ስምምነት “በየትኛውም ጊዜ ራሷን ከታቀደ፣ አይቀሬ እና ቀጣይነት ያለው ጥቃት ለመከላከል አስፈላጊውን እርምጃ በሙሉ የመውሰድ መብትን” ለእስራኤል ሰጥቷል።

    ተኩስ አቁሙ ተግባራዊ መሆን ከጀመረ አንስቶ እስራኤል እና ሄዝቦላህ አንዳቸው ሌላኛቸውን ስምምነቱን በመጣስ ከስሰዋል።

    14 ሰዎችን ከገደለውን ጥቃት አስቀድሞ ቅዳሜ ዕለትም የእስራኤል ጦር የሄዝቦላህ “ወታደራዊ ይዞታዎች” ባላቸው ስፍራዎች ላይ ጥቃት ፈጽሟል።

    ጦሩ ይህንን ጥቃት የፈጸመው በኢራን የሚደገፈው ሄዝቦላህ ሁለት ፈንጂ የተሸከሙ ድሮኖችን ወደ እስራኤል አስወንጭፏል በሚል ነው።

    ቅዳሜ ዕለት የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ የአገሪቱ ጦር ሊባኖስ ውስጥ የሚገኙ “የሄዝቦላህ ዒላማዎችን በኃይለኛው እንዲያጠቁ” ትዕዛዝ ሰጥተዋል። በዚሁ ዕለት ደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ በተፈጸሙ ጥቃቶች ስድስት ሰዎች ተገድለዋል።

  11. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን ጋር በስልክ መነጋገር እንደሚመርጡ እና ተደራዳሪዎቻቸውን እንደማይልኩ ተናገሩ

    የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ጃሬድ ኩሽነር (ግራ) እና ስቲቭ ዊትኮፍ (ቀኝ) ቅዳሜ ዕለት ወደ ኢስላማባድ እንዲጓዙ ቀጠሮ ተይዞ የነበረ ቢሆንም የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አስቀድመው ከፓኪስታን ከወጡ በኋላ ጉዟቸው ተሰርዟል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ጃሬድ ኩሽነር (ግራ) እና ስቲቭ ዊትኮፍ (ቀኝ) ቅዳሜ ዕለት ወደ ኢስላማባድ እንዲጓዙ ቀጠሮ ተይዞ የነበረ ቢሆንም፤ የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አስቀድመው ከፓኪስታን በመውጣታቸው ጉዞው ተሰርዟል

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ሁለት ወር ሊደፍን የተቃረበውን ጦርነት የሚቋጭ ድርድር ማድረግ የምትፈልግ ከሆነ በስልክ መነጋገር እንችላን አሉ።

    ትራምፕ እሁድ ዕለት ለፎክስ ኒውስ በሰጡት ቃለ መጠይቅ “መነጋገር ከፈለጉ፤ ማውራት እንችላለን። ሰዎችን ግን አንልክም” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ከፎክስ ኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ይህንን የተናገሩት አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረግ ጉዞ ላይ እንደጣለችው ገደብ ያሉ የስምምነት እንቅፋቶች እንዲወገዱ ከጠየቀች በኋላ ነው።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ቅዳሜ ዕለት ተደራዳሪዎቻቸው ስቲቭ ዋትኮፍ እና ጃሬድ ኩሽነርን ወደ ፓኪስታን ዋና ከተማ ኢስላማባድ እንደሚልኩ ከተናገሩ በኋላ ሁለቱ አገራት በድጋሚ ድርድር ይጀምራሉ የሚል ተስፋ ጭሮ ነበር።

    አርብ ዕለት ፓኪስታን ገብተው የነበሩት የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራግቺ ግን የአሜሪካኑ ልዑካን ከመድረሳቸው አስቀድሞ ወደ ኦማን ተጉዘዋል።

    ትናንት እሁድ ለአጭር ቆይታ ተመልሰው ወደ ፓኪስታን ተጉዘው የነበረ ቢሆንም የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ተደራዳሪዎቻቸውን የመላክ እቅዳቸውን አስቀድመው ሰርዘዋል።

    አራግቺ ከፓኪስታን ወጥተው ወደ ሩሲያ አምርተዋል። በዚያም ከፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር እንደሚገናኙ ይጠበቃል።

    የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከዚህ ቀደም ኢራን እና አሜሪካን ስታደራድር ወደ ነበረችው ኦማን ባደረጉት ቆይታ ስለ ወሳኙ የባሕር መተላለፊያ ሆርሙዝ እንደተነጋገሩ ተገልጿል።

    ትራምፕ በፎክስ ቃለ መጠይቃቸው “መነጋገር ከፈለጉ ወደ እኛ መምጣት ወይም ሊደውሉልን ይችላሉ። ታውቃለህ፤ ቴሌፎን አለ። ጥሩ፣ ደኅንነቱ የተጠበቀ መስመር አለን” ሲሉ በድጋሚ ልዑካን እንደማይልኩ ጠቁመዋል።

    አክለውም፤ “ስምምነቱ ውስጥ ምን መኖር እንዳለበት ያውቃሉ። በጣም ቀላል ነው፤ የኒውክሌር መሣሪያ ሊኖራቸው አይችልም። ይህ ካልሆነ የምንገናኝበት ምክንያት አይኖርም” ማለታቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ከቆይታ በኋላ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ “ማድረግ ያለባቸው መደወል ነው” በማለት ጽፈዋል።

    ትራምፕ ይህንን ያሉት የፓኪስታን የፖለቲካ እና ወታደራዊ አመራሮች በቴህራን እና ዋሽንግተን መካከል የተኩስ አቁም እንዲፈረም እየጣሩ ባሉበት ወቅት ነው።

    የዜና ወኪሉ አሶሺዬትድ ፕሬስ ያነጋገራቸው አንድ የፓኪስታን ባለሥልጣን ቀጥተኛ ያልሆኑ ንግግሮች መቀጠላቸውን ገልጸዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን ለሁለት ሳምንት እንዲቆይ የተስማሙት ተኩስ አቁም ባለፈው ሳምንት ረቡዕ ቢጠናቀቀም፤ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ላልተወሰነ ጊዜ አራዝመውታል። ይህም የካቲት ላይ የተጀመረው ውጊያ እንዲገታ አድርጓል።

    በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የተገደሉበት እና የዓለምን ኢኮኖሚ ቀውስ ውስጥ የከተተውን ጦርነት በዘላቂነት የሚቋጭ መፍትሔ ላይ ግን እስካሁን አልተደረሰም።