ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ቦይንግ 20 በመቶ ሰራተኞቹን ለመቀነስ ማቀዱን አስታወቀ
ቦይንግ በቅርቡ 7 ሺህ የሚሆኑ ሰራተኞቹን እንደሚቀንስ ይፋ አድርጓል።
በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የተጎዳው የአሜሪካኑ አውሮፕላን አምራች ቦይንግ በከፍተኛ ሁኔታ የሰራተኞቹን ቁጥር ለመቀነስ እንዳሰበ ያሳወቀ ሲሆን በመጪው አውሮፓውያኑ አመት መጨረሻም 20 በመቶ የሚሆኑትን ወደ 30 ሺህ ሰራተኞቹን እንደሚቀንስ አስታውቋል።
ከቀውሱ በፊት ኩባንያው የነበሩት የሰራተኞች ቁጥር 160 ሺህ ነበር።
የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በተጨማሪ ከ337 ማክስ የደህንነት ስጋቶች ጋር ተደራርቦ ኩባንያውን ለኪሳራ ዳርገውታል።
እስከ መስከረም አጋማሽ ባለውም ሶስት ወራት ውስጥ 466 ሚሊዮን ዶላር ከስሬያለሁ ብሏል።
ይህም ሁኔታ ለአመት ያህልም ቀጥሏል።
ከበረራ ውጭ ሆነው የነበሩት 737 ማክስ አውሮፕላኖቹ በረራ ሊጀምሩ ይችላሉ መባሉም ጋር ተያይዞም ኩባንያው በእነዚህ አውሮፕላኖች ሽያጭ እንደሚያገግም ተስፋ አድርጓል።
737 ማክስ ሁለት አውሮፕላኖች ተከስክሰው የ346 ሰዎች ህይወት ከጠፋ በኋላ ከበረራ ከታገደ ከአንድ አመት በላይ ሆኖታል።
አውሮፕላኑ ሙሉ ሙሉ ከበረራ የታገደው በጎርጎሳውያኑ መጋቢት ወር 2019 ዓ.ም ነበር።
የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በአየር ጉዞ ኢንዱስትሪው ላይ ከፍተኛ ቀውስን ያስከተለ ሲሆን በርካታ አየር መንገዶችንም ኪሳራ ውስጥ ጥሏል።
በዚህም ምክንያት በርካታ አየር መንገዶች ሰራተኞቻቸውን አባረዋል እንዲሁም አዳዲስ ሊገዟቸው ያሰቧቸውን አውሮፕላኖች በይዋል ይደር ትተውታል።
ቦይንግም ሰራተኞችን ከመቀነስ በተጨማሪ ምርቱንም ዝቅ ለማድረግ ተገዷል። ከዚህ ቀደም 10 በመቶ ሰራተኞቹን የቀነሰው ቦይንግ እስከ 2023 ባለው ወቅትም ካለበት ቀውስ እንደማይወጣ ግምቱን አስቀምጧል።
ገቢውም በከፍተኛ ሁኔታ ማሽቆልቆሉ የተነገረለት ቦይንግ በዘጠኝ ወራትም 30 በመቶ ዝቅ ብሏል።
የቦይንግ ፕሬዚዳንትና ዋና ስራ አስፈፃሚ ዴብ ካልሁን እንዳሉት የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በከፍተኛ ሁኔታ ኢንዲስትሪው ላይ ጉዳት ማድረሱን ነው።