እውቁ ተጫዋች እግር ኳሰኞች ዘረኝነትን በመጠየፍ ማሕበራዊ ሚድያን መተው አለባቸው ይላል

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የእንግሊዝ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝና የቀድሞው የማንቸስተር ዩናይትድ ተጫዋች ፊል ኔቪል እግር ኳስ ተጫዋቾች እራሳቸውን ከማሕበራዊ ሚድያ በማግለል ዘረኝነትን እንደሚጠየፉ ማሳየት አለባቸው ሲል አሳስቧል።
ሰኞ ምሽት ማንችስተር ዩናይትድ ከዎልቭስ ጋር በነበረው ጨዋታ ፖል ፖግባ ፍፁም ቅጣት መሳቱን ተከትሎ ማሕበራዊ ድር አምባዎች ላይ ዘረኝነት የተጠናወታቸው ትችቶች ቀርበውበት ነበር።
«እስከመቼ ነው እንዲህ የምንዘልቀው? ተጫዋቾቼ ያጋጥማቸዋል፤ ፕሪሚዬር ሊግ ላይ አለ፤ እንዲሁም ቻምፒዮንስ ሊግ ላይ። ትዊተርም ሆነ ኢንስታግራም ግድ ከሌላቸው እኛ የሆነ ነገር ማድግ አለብን» ብሏል ኔቪል።
በሁኔታው እግጅ የበገነው ኔቪል «እኔ ማሕበራዊ ድር አምባን በሚዘውሩ ሰዎች ተስፋ ቆርጫለሁ» ይላል። «ሁኔታውን እየተከታተልን ነው ብለው ኢሜይል ይልኩልሃ። ነገር ግን ምን ሲፈጠር አታይም።»
ለዚያም ነው ማሕበራዊ ሚድያን ማግለል ያዋጣል የሚለው ኔቪል። «ቢያንስ ለ6 ወራት ማቋረጥ። እስቲ ምን እንደሚፈጠር እንይ» ብሏል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ፖል ፖግባ ላይ ዘረኛ አስተያየቶች ከተሰጡ በኋላ ትዊተር ሁኔታውን 'አምርሮ እንደሚቃወም' አሳውቆ 'የተወሰኑ ገፆችን ዘግቻለሁ' ብሏል።
ድርጅቱ 'በተለይ እንግሊዝ ውስጥ በሚጫወቱ ተጫዋቾች ላይ የበይነ-መረብ ዘረኝነት ጥቃት እየተሰነዘረ መሆኑን ተረድናል' ሲል አትቷል።
ፌስቡክም እንዲሁ ለዘረኛ አስተያየቶች 'ቦት እንደሌለው' አሳውቆ ኢንስታግራምን ጨምሮ በሌሎች መድረኮች ላይ የሚሰነዘሩ ጥቃቶችን ለመመከት እየሠራን ነው ሲል ገልጿል።
የፈረንሳዊው እግር ኳሰኞ ፖግባ የሥራ ባልደረቦች በይነ-መረብ ላይ ያስተዋሏቸውን ፀያፍ እና ዘረኛ ጥቃቶች አምርረው አውግዘዋል።
ሃሪ ማክጓዬር፣ ማርከስ ራሽፎርድ እና ዴቪድ ዲ ሂያ ጥቂቶቹ ናቸው። የዩናይትድ አመራሮችም ጥቃቱን እንደሚቃወሙ ለማሳወቅ ጊዜ አልወሰደባቸውም።













