ትራምፕ በብራዚል ላይ 50 በመቶ ታሪፍ፤ የቦልሶናሮን ክስ በያዙት ዳኛ ላይ ደግሞ ማዕቀብ ጣሉ

ዳኛ አሌክሳንደር ዴ ሞሬስ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የምስሉ መግለጫ, ዳኛ አሌክሳንደር ዴ ሞሬስ፤ በቀድሞው የብራዚል ፕሬዝዳንት ዣየር ቦልሶናሮ ላይ የሚካሄደውን ምርመራ ሲመሩ ቆይተዋል

የአሜሪካ ባለስልጣናት፤ የቀድሞውን የብራዚል ፕሬዝዳንት ዣይር ቦልሶናሮ የሚካሄደውን ምርመራ በሚመሩት የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኛ አሌክሳንድር ዴ ሞሬስ ላይ ማዕቀብ እንደሚጣል ተናገሩ።

ባለስልጣናቱ፤ ቀኝ አክራሪው የቀድሞ ፕሬዝዳንት እና አጋሮቻቸው በአውሮፓውያኑ 2022 ምርጫ ከሸነፉ በኋላ መፈንቅለ መንግሥት አሲረዋል በሚል የቀረበውን ክስ የሚመሩትን ዳኛ ሞሬስን፤ "የዘፈቀደ የቅድመ ክስ እስር" በመፈጸም እና " ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን" በማፈን ወንጅለዋል።

የቀረበባቸውን ከስ ውድቅ ያደረጉት ቦልሶናሮ፤ ዳኛ ሞሬስን "አምባገነን" ሲሉ ጠርተዋቸዋል።

የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ ይህ ማዕቀብ ይፋ ከተደረገ በኋላ ወዲያኑ በብራዚል ላይ 50 በመቶ ታሪፍ የሚጥል ፕሬዝዳንታዊ ትዕዛዝ ፈርመዋል።

ትራምፕ በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ የብራዚል ፕሬዚዳንት ሉዊዝ ኢናሲዮ ሉላ ዳ ሲልቫ በጻፉት እና በማህበራዊ ሚዲያ ገጻቸው በለጠፉት ደብዳቤ፤ ሀገሪቱ ላይ ከፍተኛውን ታሪፍ እንደሚጥሉ ዝተው ነበር።

ትራምፕ በዚህ ደብዳቤያቸው፤ ብራዚልን በአሜሪካ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ላይ "ጥቃት" በመፈጸም እና ዣየር ቦልሶናሮ ላይ "የሀሰት ውንጀላ ምርመራ" በማካሄድ ወንጅለዋል።

በብራዚል ላይ ተጣለው ታሪፍ እንደ የብርቱካን ጭማቂ፣ የተወሰኑ የአውሮፕላን ክፍሎችን እና የኃይል ምርቶችን ያሉ በርካታ የሀገሪቱ ዋነኛ የወጪ ንግድ ምርቶችን አላካተተም።

ይህ የትራምፕ ውሳኔ፤ ብራዚል "ቦልሶናሮ ላይ ከተመሰረተው ፖለቲካዊ ምክንያት ያለው ክስ፣ ማስፈራራት፣ ትንኮሳ፣ ሳንሱር እና ክስ" ጋር በቀጥታ እንደሚገናኝ ተገልጿል።

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

ብራዚል በበኩሏ በአሜሪካ በሚጣልባት ማንኛውንም ታሪፍ ልክ የአጸፋ ቀረጥ እንደምትጥል አስጠንቅቃለች።

አሜሪካ ከቻይና ቀጥሎ ሁለተኛዋ ትልቅ የብራዚል የንግድ አጋር በመሆኗ፤ የዋጋ ጭማሪው ደቡብ አሜሪካዊቷን ሀገር በእጅጉ ሊጎዳት ይችላል።

ብራዚል ለአሜሪካ 15ኛዋ ትልቅ የንግድ አጋር ነች። ብራዚል ከአሜሪካ የምታስገባቸው ዋና ዋና ምርቶች የማዕድን ነዳጆች፣ አውሮፕላኖች እና ማሽኖች ናቸው። አሜሪካ በበኩሏ ጋዝ እና ነዳጅ እንዲሁም አይረን እና ቡና ከብራዚል ታስገባለች።

የአሜሪካ ግምጃ ቤት ኃላፊ ስኮት ቤሰንት ረቡዕ ዕለት በዳኛ ሞሬስ ላይ የተጣለውን ማዕቀብ ይፋ ባደረጉበት ወቅት፤ ዳኛውን "በአሜሪካ እና በብራዚል ዜጎች እና ኩባንያዎች ላይ ህገወጥ የወንጀል ምርመራ" በመፈጸም ከስሰዋል።

ቤሰንት አክለውም ዳኛው "በቀድሞው ፕሬዝዳንት ዣይር ቦልሶናሮ [ላይ የተፈጸመውን] ጨምሮ የሰብአዊ መብቶችን በሚጥስ ጨቋኝ የሳንሱር ዘመቻ፣ በዘፈቀደ እስራት እና በፖለቲካዊ ክሶች ተጠያቂ ናቸው" ብለዋል።

"የዛሬው እርምጃ ግምጃ ቤቱ የአሜሪካን ጥቅም እና የዜጎቻችንን ነጻነት አደጋ ላይ የሚጥሉ አካላት ተጠያቂ ማድረግ እንደሚቀጥል ግልጽ ያደርጋል" ብለዋል።

ቢቢሲ የዳኛ ሞሬስን አስተያየት ለመቀበል ጥያቄ አቅርቧል።

ዳኛ ሞሬስ፤ በቦልሶናሮ ላይ የሚካሄደውን የክስ ሂደት ከመምራት በተጨማሪ፤ የአሜሪካ ገጾችን ጨምሮ አንዳንድ የማህበራዊ ሚዲያ አካውንቶች እንዲዘጉ ትዕዛዝ ሰጥተዋል።

ይህንን የእግድ ትዕዛዝ በመቃወም ለማስነሳት እየታገሉ ካሉ የአሜሪካ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች መካከል የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ትራምፕ ንብረት የሆነውን ትሩዝ ሶሻል የተባለ የማህበራዊ ሚዲያ መድረክ በሚያስተዳድረው ትራምፕ ሚዲያ ኩባንያ ይገኝበታል።

ሚዲያ የእርሱን የእውነት ማህበራዊ መድረክ ከሚያስተዳድሩት የአሜሪካ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች መካከል አንዱ ሲሆን የማህበራዊ ሚዲያ አካውንቶችን የማገድ ትዕዛዞችን በተመለከተ የብራዚል ፍርድ ቤት ውሳኔዎችን በመቃወም ላይ ይገኛል።

በተጨማሪም ብራዚል ከዚህ ቀደም ትዊተር ተብሎ ይጠራ የነበረውን የኤለን መስክን 'ኤክስ' ለአጭር ጊዜ አግዳ ነበር። ኤክስ እገዳ የተጣለበት በ2022 የተካሄደውን የብራዚል ፕሬዚዳንታዊ ምርጫን በተመለከተ የተሳሳተ መረጃ የሚያሰራጩ አካውንቶችን ለመዝጋት ፈቃደኛ ባለመሆኑ ነው።

የብራዚል ጠቅላይ ፍርድ ቤት፤ የማህበራዊ ሚዲያ ኩባንያዎች በገጾቻቸው ላይ ለተለጠፈው ይዘት ተጠያቂ ሊሆኑ እንደሚችሉ ባለፈው ወር ወስኗል።