አሜሪካ፡ የስድስት ቀን ጨቅላ በቦርሳዋ ይዛ የተገኘችው ሴት ተከሰሰች

የፎቶው ባለመብት, EPA
የስድስት ቀን ጨቅላን በቦርሳዋ ደብቃ ከፊሊፒንስ ልትወጣ ስትል በፖሊስ የተያዘችው አሜሪዊት በሕገ ወጥ የሰው ዝውውር ክስ ተመሰረተባት።
ጄኔፈር ታልቦት የተባለችው የ43 ዓመት ሴት በቁጥጥር ሥር የዋለችው ባለፈው ረቡዕ ፊሊፒንስ በሚገኝ የአውሮፕላን ማረፊያ ውስጥ ነበር። ወደ አሜሪካ የሚበር አውሮፕላን እየጠበቀች የነበረችው ጄኔፈር፤ ቦርሳዋ ውስጥ ከተወለደ ስድስት ቀን የሆነው ጨቅላ ቦርሳዋ ውስጥ መገኘቱን ፖሊስ አስታውቋል።
የኢሚግሬሽን ኃላፊዎች እንደተናገሩት ጄኔፈር ልጅ እንደያዘች አልነገረቻቸውም ነበር። የፊሊፒንስ የወንጀል ምርመራ ቡድን፤ ግለሰቧ ጨቅላውን ደብቃ ከአገር ለማስወጣት ሞክራለች ብሏል።
የጨቅላው እናትና አባት፤ የልጆችን መብት በመጋፋት ክስ ተመስርቶባቸዋል። የስድሰት ቀን ልጃቸውን ማኅበራዊ ሠራተኞች ተረክበዋል።

የፎቶው ባለመብት, Photo courtesy of Bureau of Immigration
ጄኔፈር ታልቦት ክሱ ከቀረበባት በኋላ፤ ልጁን ወደ አሜሪካ ለመውሰድ ፍቃድ አግኝቼበታለሁ ያለችውን ሰነድ ብታቀርብም፤ ሰነዱ ላይ የልጁ እናት ፊርማ አልሰፈረም ተብሏል።
ጥፋተኛ ሆና ከተገኘች የእድሜ ልክ እሥራት ይጠብቃታል።












