ኢንተርኔት ኤክስፕሎረር ከ26 አመታት አገልግሎት በኋላ ከጥቅም ውጭ ሊሆን ነው

የማይክሮሶፍት አርማ

የፎቶው ባለመብት, Microsoft/Getty

የማይክሮሶፍቱ ኢንተርኔት ኤክስፕሎረር ከ26 አመታት አገልግሎት በኋላ ከጥቅም ውጭ እንደሚሆን ግዙፉ ኩባንያ አስታውቋል።

ኢንተርኔት ኤክስፕሎረር ደንበኞች ኢንተርኔት መጠቀም በሚፈልጉበት ወቅት የሚጠቀሙት ቀዳሚ የድር አሳሽ ሆኖም ለዘመናት አገልግሏል።

በቅርብ ጊዜያት ግን በተጠቃሚዎች ዘንድ ተመራጭ አለመሆኑ እየተሰማ ነው።

የቴክኖሎጂ ምርቶችን በማምረት የሚታወቀውና ከኢንተርኔት ኤክስፕሎረር ጀርባ ያለውም ማይክሮሶፍት ኩባንያ ኢንተርኔት ኤክስፕሎረር በማመርታቸው አዲሶቹ ኮምፒውተሮች ላይ አይኖርም ብሏል።

ተጠቃሚዎች ኮምፒውተሮቻቸው ዊንዶውስ 10 ከሆነ ኢንተርኔት ኤክስፕሎረርም አይኖርም ብሏል።

ይህም ከአንድ ወር በኋላ ተግባራዊ እንደሚሆን የማይክሮ ሶፍት ኩባንያ በመግለጫው አስታውቋል።

ማይክሮ ሶፍት ይህንን አንጋፋ የድር አሳሽ ከጥቅም ውጭ ለማድረግ ለብዙ አመታት ሞክሯል።

ከሁለት አመታት በፊት ያለውን መረጃ ስናይ 8 በመቶ የሚሆነው የቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ኢንተርኔት ኤክስፕሎረርን ይገለገልበት ነበር ተብሏል።

በኢንተርኔት ኤክስፕሎረር ፈንታ ለሱ የሚጣጣም ማይክሮሶፍት ኤጅ የተባለ ድር አሳሽ ይተካል ተብሏል።

የድሮ ድረ ገፆች አብዛኛዎቹ በድሮ የቴክኖሎጂ ስርአት ጋር ተጣጥመው ከመሰራታቸው አንፃር አዲሶቹ የድር አሳሾችም የነሱን ሂደት ማቀላጠፍ ያዳግታቸውዋል ተብሏል።

የማይክሮሶፍት ኤጅ ፕሮግራም ስራ አስኪያጅ ሲን ሊንደርሳይ በበኩላቸው አዲሱ የድር አሳሽ " የበለጠ ፈጣን፣ ደህንነቱ የተጠበቀና በአዲስና በተቀላጠፈ መልኩ የተለያዩ ድረ ገፆችን ማሰስ የሚያስችል ነው" ካሉ በኋላ የቀድሞ መተግበሪያዎችም ጋር እንዲጣጣም ተደርጎ የተሰራ ነው ብለዋል።

ነገር ግን ማይክሮሶፍት ከደንበኞች ለቀረቡለት ጥያቄ በሚመልስበት ወቅት እንዳስታወቀው ኢንተርኔት ኤክስፕሎረር በአዲሶቹ ኮምፒውተሮች ላይ ብቻ ሳይሆን የድሮ መተግበሪያ በሚጠቀሙትም ላይ ከጥቅም ውጭ ሊሆን እንደሚችል ጠቁሟል።

ከአውሮፓውያኑ 2000-2005 ባለው ወቅት ኢንተርኔት ኤክስፕሎረር 90 በመቶ የሚሆነውን ገበያ ተቆጣጥሮት ነበር። በአሁኑ ወቅት የድር አሳሽነትን ከፍተኛ ስፍራ እየመራ ያለው ጉግል ክሮም ነው።