ጨቅላ ልጅዎትን ከአቅም በላይ እየመገቡ ይሆን?

እንደው ሳያስተውሉት ልጅዎን ከሚገባው በላይ እየመገቡ ይሆን?

የሕፃናት ከመጠን ያለፈ ውፍረት ከ21ኛው ክፍለ ዘመን የጤና እክሎች መካከል አንዱ ነው ይላል የዓለም ጤና ድርጅት።

ታድያ እንደሚያስቡት ያደጉ አገራትን ብቻ የሚያጠቃ ችግር አይደለም። ከመጠን ያለፈ ውፍረት የምጣኔ ሃብት ዕድገታቸው ዝቅ ባለ አገራትም በሰፊው ይታያል።

ሕፃናት ከመጠን በላይ እንዲወፍሩ ከሚያደርጉ ምክንያቶች ዋነኛው ከመጠን በላይ መመገብ ነው። ለዚህ ደግሞ ተጠያቂው ቤተሰብ ወይም አሳዳጊ ነው።

ታድያ ሕፃናት ምን ያህል መመገብ እንዳለባቸው እንዴት እናውቃለን? የሚመገቡት የምግብ ዓይነትስ? እነሆ አራት መላዎች።

የጡት ወተት

የእናት ጡት ወተት ለሕፃናት የመከላከል አቅም ይሰጣቸዋል። የጡት ወተት ከተወለዱ በኋላ ለስድስት ወራት ያገኙ ሕፃናት ከተላላፊ በሽታዎች የመጠበቅ ዕድላቸው የሰፋ ነው።

ለዚህ ነው ለስድስት ወራት ከጡት ወተት ውጭ የማይሞከረው። አልፎም ለመጀመሪያዎቹ 12 ወራት የላም ወተት ባይመግቧቸው ይመከራል። ይህ የሚመከረው የላም ወተት ያለው የአይረን መጠን ዝቅ ያለ ስለሆነ ነው።

ደረቅ ምግብ

ሕፃናትን ለመጀመሪያዎቹ ስድስት ወራት የጡት ወተት ከተመገቡ በኋላ ደረቅ ምግብ እንደሚገቡ ማድረግ አይረን የበዛባቸው ምግቦች መመገብን ይመከራል።

ሕፃናት ከጡት ወተት ወደ ደረቅ ምግብ ሲተላለፉ ዳተኝነት ይታይባቸው ይሆናል። እንዲሁም ላይለምዱትም ይችላሉ። ነገር ግን ማስለመድ የግድ ነው።

ታድያ የጡት ወተቱ እንዳይረሳ።

ጨው እና ስኳር ካላቸው ምግቦች ማራቅ

ሥጋና መሰል ምግቦች እንዲሁም ለስላሳ መጠጦች ብዙ ካሎሪ አላቸው። ሕፃናት ይህንን ከለመዱ ለጤናማ ምግብ ያላቸው አምሮት ይዘጋል።

ጭማቂም ቢሆን አይመከርም። ምንም እንኳ ጁስ ከፍራፍሬ ቢመጣም ሲብላላ ወይም ሲጨመቅ ብዙ ስኳር ስለሚወጣው ለሕፃናት አይመከርም፤ በተለይ ደግሞ የታሸጉ ጭማቂዎች።

ምንም እንኳ ሕፃናት ለብስኩታ ብስኩት ያላቸው ፍቅር ከፍ ያለ ቢሆንም በውስጡ ያለው ጨው የሚመከር አይደለም።

ለውዝ እና እንቁላል

ሕፃናት ከስድስት ወራቸው በኋላ ለውዝ እና የዶሮ እንቁላል ቢመገቡ ይመረጣል።

ይህ ከአለርጂ ጋር እንጂ ከመጠን ካለፈ ውፍረት ጋር ብዙም ግንኙነት የለውም። የጤና ባለሙያዎች ሕፃናት ለውዝና እና እንቁላል ዘግይተው መመገብ ከጀመሩ ለአለርጂ ሊጋለጡ ይችላሉ ባይ ናቸው።

ስለዚህ ከእነዚህ ምግቦች ጋር በጊዜ ማስተዋወቅ የተገባ ነው። በተለይ ደግሞ ከስድስተኛ ወራቸው በኋላ። ነገር ግን ቤተሰቦት ውስጥ ለእነዚህ ምግቦች አለርጂ ያለበት ሰው ካለ የሕክምና ባለሙያ ማማከሩ የሚጎዳ አይደለም። ለነገሩ የሕክምና ባለሙያ ማማከር ለዚህ ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ይመከራል።