ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ተቃውሞ የሚንጣት ድሬዳዋ
ሰኞ የእግዜርአብ ታቦት ገብቶ ሲመለስ ፖሊስ መሬት በሚባል አካባቢ በተፈጠረ ግጭት የጀመረው የድሬዳዋ ውጥረት ዛሬም ቀጥሏል።
ደውለን ያነጋገርናቸው የድሬዳዋ ነዋሪዎች እንደነገሩን ከሆነ አርብ ዕለት ከማለዳ ጀምሮ ወጣቶች ሰልፍ ሲያካሄዱ፣ የተቃሞው ድምጾችን ሲያሰሙ፣ አልፎ አልፎም ድንጋይ ሲወራወሩ ነበር።
የወጣቶች ጥያቄ እየሰፋ መጥቶ የሥራ አጥነት፣ የመልካም አስተዳደር፣ የፍትህና የእኩልነት ጥያቄዎች ጎልተው መውጣት ጀምረዋል። በተለይም የድሬዳዋን ፍቅር አታደፍርሱ፣ በብሔር አትከፋፍሉን፣ «40/40/20» የተሰኘው የአስተዳደር ቀመር ይውደም፣ የሚሉ ተቃውሞዎች ሲሰሙ ነበር።
ረፋድ ላይ ድሬዳዋ ራስ ሼል አካባቢ «ከንቲባው ይውረድ! ድምጻችን ይሰማ!» የሚሉ ድምጾችም ከፍ ብለው ይሰሙ ነበር። በዚያ ያልፉ የነበሩ ሦስት መቶ የሚገመቱ ወጣቶች ባንዲራዎችን ከመያዝ ውጭ ተቃውሟቸውን በሰላማዊ መንገድ ያቀርቡ እንደነበር አቶ ሰለሞን ኃይሌ የተባሉ የድሬዳዋ ነዋሪ ነግረውናል።
ትናንትናና ከትናንት በስቲያ ረቡዕ ባንኮች ተዘግተው መዋላቸውንና የከተማዋ እንቅስቃሴ በአመዛኙ ታውኮ እንደነበረም ሰምተናል። ተቃውሞው ሙሉ ከተማውን ያካለለ ባይሆንም ተቃውሞወቹ ዋና ዋና የንግድ እንቅስቃሴዎች በከፊል እንደተስተጓጎለም ነዋሪዎች ነግረውናል።
«ወጣቶቹ ሆ ብለው ሲመጡ ሱቆች ይዘጋሉ፣ በረድ ሲል ደግሞ መልሰው ይከፈታሉ ብለዋል» አቶ ሰለሞን ለቢቢሲ።
ዛሬ ከዚራ፣ በዋናነት ደግሞ «ጂቲዜድ» የሚባል ሰፈር፣ እንዲሁም ድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ የሚገኝበት አካባቢ ፖሊስና ወጣቶች ተፋጠው ማርፈዳቸውን የዓይን እማኞች ነግረውናል።