ቀጥታ, የኢራንን መንግሥት ለመጣል ዓለም ተቃዋሚዎችን እንዲረዳ በስደት ላይ የሚገኙት ልዑል ጠየቁ

በስደት ላይ የሚገኙት የመጨረሻው የኢራን ንጉሥ ልጅ የዓለም መንግሥታት የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክን ለመጣል ተቃዋሚዎችን እንዲደግፉ ጥሪ አቀረቡ። በአሜሪካ የሚኖሩት የተቃዋሚ መሪ ሬዛ ፓህላቪ፣ ዓለም የኢራንን አብዮታዊ ዘብ አመራርን ዒላማ እንዲያደርግ ጠይቀዋል። ከሐያ ቀን በፊት በኢራን የኑሮ ውድነትን ተከትሎ በተቀሰቀሰው ሕዝባዊ ዓመጽ እስካሁን ድረስ ከ2,600 በላይ ሠልፈኞቸ በኢራን የጸጥታ አካላት መገደላቸውን የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች አስታውቀዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ትራምፕ የኢራን አመራሮች ‘ተቃዋሚዎችን ባለመግደላቸው’ አመሰገኑ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አርብ ዕለት የኢራን መንግሥት በመቶዎች የሚቆጠሩ የፖለቲካ እስረኞችን ለመግደል የያዘውን ዕቅድ በማስቀረቱ አመሰገኑ።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ አርብ ዕለት 800 ሰዎችን በስቅላት ለመቅጣት ተይዞ የነበረው ቀጠሮን በመቅረቱ ባልተለመደ ሁኔታ የኢራን ባለሥልጣትን አመስግነዋል።

    “. . .ሊፈጸሙ ታቅደው የነበሩት (ከ800 በላይ ስቅላቶች) በሙሉ በኢራን አመራሮች በመሰረዛቸው ያለኝን አክብሮት እገልጸለሁ፤ አመሰግናለሁ” ሲሉ በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    ዶናልድ ትራምፕ የሳምንቱን መጨረሻ ፍሎሪዳ በሚገኘው መኖሪያቸው ለማሳለፍ ሲሄዱ እስራኤል እና የአረብ አገራት ኢራንን ላይ ጥቃት እንዳይፈጽሙ አሳምነዋቸው እንደሆን ተጠይቀው ነበር።

    “ማንም አላሳመነኝም፤ ራሴን አሳምኛለሁ። ከ800 በላይ ሰዎችን ለመግደል አቅደው ነበር። ማንንም አልገደሉም። ስቅላቶቹ ተሰርዘዋል። በጣም አስደናቂ ነበር” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

    ከዚህ ቀደም ዶናልድ ትራምፕ የኢራን መንግሥት ተቃዋሚ ሠልፈኞችን የሚገድል ከሆነ "ጠንካራ እርምጃ" እንደሚወስዱ አስጠንቅቀው ነበር።

    በተጨማሪም ሠልፈኞቹን በማበረታታት "ድጋፍ እየመጣላችሁ" ነው ሲሉ ተናግረው እንደነበር ይታወሳል።

  2. የኢራን ተቃውሞ መሪ የሆኑት ልዑል ሬዛ ፓህላቪ ትራምፕ ቃላቸውን እነደሚጠብቁ ተናገሩ

    በስደት ላይ የሚገኙት የመጨረሻው የኢራን ንጉሥ ልጅ የዓለም መንግሥታት የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክን ለመጣል ተቃዋሚዎችን እንዲደግፉ ጥሪ አቀረቡ።

    ተቃውሞውን አሜሪካ ተቀምጠው የሚመሩት ሬዛ ፓህላቪ ትራምፕ ቃላቸውን የሚጠብቁ መሪ መሆናቸውን እና ከኢራናውያን ጎን እንደሚቆሙ እንደሚያምኑ ተናግረዋል።

    “እስላማዊው ሪፐብሊክ ይወድቃል፤ ሊወድቅ ይችላል የሚለው ሳይሆን መቼ“ የሚለው ነው ጥያቄው ሲሉ ተናግረዋል።

    በአሜሪካ የሚኖሩት የተቃዋሚ መሪ የሆኑት ሬዛ ፓህላቪ፣ ዓለም የኢራንን አብዮታዊ ዘብ አመራርን ዒላማ እንዲያደርግም ጠይቀዋል።

    ይህም "ዓላማችንን ያመቻቻል እንዲሁም ተጨማሪ የሰው ሕይወት እንዳይጠፋ ይከላከላል" ብለዋል።

    ከሃያ ቀን በፊት በኢራን የኑሮ ውድነትን ተከትሎ በተቀሰቀሰው ሕዝባዊ አመጽ እስካሁን ድረስ ከ2,600 በላይ ተቃዋሚዎች በኢራን የፀጥታ አካላት መገደላቸውን የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች አስታውቀዋል።

    የኢራን መንግሥት ተቃውሞዎቹን በኢራን ጠላቶች የተደገፉ "ረብሻዎች" ሲል ጠርቷቸዋል።

    ፓህላቪ በኢራን የሚካሄደው ተቃውሞ መሪ ሆነው ብቅ ያሉ ሲሆን፣ ኢራናውያን ተቃውሟቸውን እንዲቀጥሉ አሳስበዋል።

    በኢራን የተቀሰቀሰውን መጠነ ሰፊ ተቃውሞ ተከትሎ የኢንተርኔት እና ሌሎች የመገናኛ አገልግሎቶች ሙሉ በሙሉ የተቋረጡ ሲሆን፣ የአገሪቱ የፀጥታ ኃይሎችም ጠንካራ እርምጃ መውሰዳቸውን ቀጥለዋል።

    ፓህላቪ አርብ ዕለት በዋሽንግተን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የኢራን የደኅንነት ክፍል በዘመቻው ለመሳተፍ ፈቃደኛ አለመሆኑን እና የኢራን ባለሥልጣናት ተቃውሞውን ለማብረድ ከውጭ ሚሊሻዎች ማምጣታቸውን ተናግረዋል።

    ዓለም የኢራንን አብዮታዊ ዘብ ኃይሎች ዒላማ እንዲያደርግ እና መሠረተ ልማቶችን እንዲቆጣጠር እንዲሁም እንዲያዝ አሳስበው "ወሳኝ የሆነ ጥቃት" እንዲፈጸም ጥሪ አቅርበዋል።

    በተጨማሪም ዓለም አቀፍ ኃያላን አገራት የኢኮኖሚ ጫና እንዲፈጥሩ፣ የኢራን ዲፕሎማቶችን እንዲያባርሩ፣ ሁሉም የፖለቲካ እስረኞች እንዲፈቱ እንዲጠይቁ እና በኢራን ውስጥ ግንኙነት እንዲኖር የሳተላይት ኢንተርኔት፣ ስታርሊንክ እና ሌሎች ደኅንነታቸው የተጠበቀ ግንኙነቶችን እንዲፈቅዱ ጠይቀዋል።

    “የኢራን ሕዝብ ወሳኝ እርምጃ እየወሰደ ነው። ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ሙሉ በሙሉ እንዲቀላቀል ጊዜው አሁን ነው” ብለዋል።

    "በዓለም እርዳታ ወይም ያለ ምንም ድጋፍ ሥርዓቱ ይወድቃል። ዓለም ቃሉን ወደ ተግባር ከቀየረ ፈጥኖ ይወድቃል፤ ብዙ ሕይወትም ይድናል።"

    ከከፍተኛ የአሜሪካ ባለሥልጣናት ጋር ውይይት አድርገዋል ስለሚሉ ዘገባዎች ለመናገር ፈቃደኛ ባይሆኑም፣ “ፕሬዝዳንት ትራምፕ ቃላቸውን የሚያከብሩ ሰው እንደሆኑ እና በመጨረሻም ከኢራናውያን ሕዝብ ጋር እንደሚቆሙ አምናለሁ” ብለዋል።

  3. ተዋናይ እና የቴሌቪዥን መሰናዶ አቅራቢ ነጻነት ወርቅነህ ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ

    በቴአትሮች፣ በአስቂኝ ፊልሞች ላይ በመተወን እና የቴሌቭዥን መሰናዶ በመምራት የሚታወቀው ነጻነት ወርቅነህ ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ።

    ‘ኤፍቢአይ’፣ ‘ፍሬሽማን’ እና ‘ያንቺው ሌባ’ን ጨምሮ በሌሎችም አስቂኝ ፊልሞች እንዲሁም ተውኔቶች የሚታወቀው ነጻነት ባደረበት ሕመም ማረፉ ተገልጿል።

    ነጻነት ወርቅነህ ለዓመታት ተወዳጅ በሆነው እና በኢቢኤስ ቴሌቪዥን የሚተላለፈው ‘የቤተሰብ ጨዋታ’ ፕሮግራም አዘጋጅ እና አቅራቢ የነበረ ሲሆን በቴሌቪዥን ማስታወቂያዎችም ዝነኛ ነበር።

    ኢቢኤስ ቴሌቭዥን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጹ ላይ አርቲስቱ ባደረበት ሕመም በድንገት ሕይወቱ ማለፉን ገልጾ ኅልፈት የተሰማውን ሐዘን ገልጿል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድም በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው በሕልፈቱ የተሰማቸውን ሐዘን ገልጸው “ነጻነት በተለይም በሕዳሴ ግድብ በተዘጋጀው የ2016 አዲስ ዓመት የመቀበያ ፕሮግራም የነበረውን አስተዋጽዖ ሁሌም አስታውሰዋለሁ" በማለት በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ላይ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጨምረውም ነጻነት የመራው እና እሳቸውም የታደሙበትን የአዲስ ዓመት ዝግጅtእ በማስታወስ "ሁላችንም አዲሱን ዓመት በደስታ እንድንቀበል አድርጎን ነበር። ለቤተሰቦቹ እና ለአድናቂዎቹ መጽናናትን እመኛለሁ” ብለዋል።

    ነጻነት ባለ ትዳር እና የሦስት ልጆች አባት ነው።

    የነጻነት የእረፍት ዜና መሰማቱን ተከትሎ የተለያዩ የማኅበራዊ ሚዲያ ገጾች ላይ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጀምሮ ታዋቂ ሰዎች፣ የሙያ ባልደረቦቹ እንዲሁም አድናቂዎቹ ከምሥሉ ጋር የሐዘን መግለጫዎችን እያጋሩ ነው።

  4. ኢራን በብሪክስ የባሕር ኃይል ልምምድ ላይ መሳተፏ ውዝግብ አስነሳ

    በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው የብሪክስ አገራት የባሕር ኃይል ልምምድ ላይ ኢራን ተሳታፊ መሆኗ አሜሪካንን ሲያስቆጣ በደቡብ አፍሪካ መንግሥት ውስጥ ውዝግብ ፈጠረ።

    አሜሪካ የኢራን መንግሥት በተቃዋሚዎች ላይ ጭካኔ የተሞላበት እርምጃ እየወሰደ ባለበት ጊዜ ኢራን በልምምዱ ላይ ተሳታፊ እንድትሆን ደቡብ አፍሪካ መጋበዟን በጽኑ ተችታለች።

    ሩሲያ፣ ቻይና እና ሌሎች የብሪክስ አባል አገራት ባሕር ኃይሎች በተሳተፉበት በደቡብ አፍሪካ የባሕር ክልል ውስጥ በተካሄደው ልምምድ ላይ ኢራን የተሳተፈችው የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስቴር የፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎሳን ትዕዛዝ ችላ ብሎ ነው የሚል ክስም ተሰንዝሯል።

    ለዚህም ምላሽ የደቡብ አፍሪካ የመከላከያ ሚኒስቴር ለዚህ “ከባድ ክስ” ምላሽ ማጣራት ምርመራ እያካሄደ መሆኑን ገልጿል።

    በደቡብ አፍሪካ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ባወጣው ጠንካራ የተቃውሞ መግለጫ የደቡብ አፍሪካ መከላከያ ሚኒስቴር እና የጦር ኃይሎች ለፕሬዝዳንቱ ትዕዛዝ ባለመገዛት ኢራን በልምምዱ እንድትሳተፍ ማድረጋቸው “የሚያስደነግጥ እና የሚያሳስብ “ ነው ብሎታል።

    የደቡብ አፍሪካ የመከላከያ ሚኒስትሯ የፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎሳ መመሪያ “ለሚመለከታቸው ሁሉ በግልጽ ተላልፎ ስምምነት ተደርሶበት እና ተግባራዊ እንዲሆን” መወሰኑን ይፋ አድርገዋል።

    ነገር ግን ኢራን ከብሪክስ አገራት የባሕር ኃይል ልምምዱ እንድትወጣ የተላላፈው ውሳኔ ተጥሶ በቻይና በተመራው እና ለአንድ ሳምንት በቆየው ልምምድ ላይ ተሳትፋለች።

    ብሪክስ በብራዚል፣ በሩሲያ፣ በሕንድ፣ በቻይና ተመሥርቶ ደቡብ አፍሪካ ዘግይት ብላ ነበር የተቀላቀለችው። በቅርቡም ኢትዮጵያ፣ ግብፅ፣ ኢንዶኔዢያ፣ ኢራን እና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የስብስቡ አባል ሆነዋል።

  5. “ከኢራን ጋር ያለው ቅራኔ በዲፕሎማሲ ይፈታል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ”- የትራምፕ ልዩ መልዕክተኛ

    የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ልዩ መልዕክተኛ የሆኑት ስቲቭ ዊትኮር ከኢራን ጋር ያለው ቅራኔ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ይፈታል ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ ተናገሩ።

    በእስራኤላውያን እና አሜሪካውያን ጥምር ካውንስል ላይ ንግግር ያደረጉት መልዕክተኛው፤ ኢራን ላይ ወታደራዊ እርምጃ ይወሰድ እንደሆነ ተጠይቀው “በዲፕሎማሲ ይቋጫል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ” ሲሉ መልሰዋል።

    ከኢራን ጋር በተያያዘ እልባት ያላገኙ አራት ጉዳዮች “ኒውክሌር፣ ኒውክሌር ማበልጸግ፣ ሚሳዔል እና የውክልና ኃይሎች” መሆናቸውን አክለዋል።

    የፕሬዝዳንት ትራምፕ ልዩ መልዕክተኛ የሆኑት ስቲቭ ዊትኮር ከኢራን ጋር ያለው ቅራኔ በዲፕሎማሲ የማይፈታ ከሆነ “ለኢራን የከፋ ይሆናል” ብዋል።

    ዊትኮፍ ኢራናውያንን “ጀግኖች” ብለው ያሞካሹ ሲሆን፤ አሜሪካ ከኢራናውያን ጎን እንደምትቆምም ተናግረዋል።

  6. የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ከሞቃዲሾ መውጣት ጀመረች

    የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ከሶማሊያ ጓዟን ጠቅልላ መውጣት ጀመረች።

    ሐሙስ ዕለት የዩኤኢ መንግሥት ንብረት የሆኑ ቁሳቁሶችን የጫኑ ሦስት አውሮፕላኖች ከአደን አዴ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ መነሳታቸውን ምንጮችን ጠቅሶ የቢቢሲ የሶማሊኛ አገልግሎት ዘግቧል።

    ሶማሊያ ከኤምሬትስ ጋር ያላትን የደህንነት እና የመከላከያ ስምምነት ከሰረዘች በኋላ ከሞቃዲሿ ያላትን ቁሳቁስ ማውጣት ጀምራለች።

    አርብ ዕለት ተጨማሪ ቁሳቁሶችን ለማውጣት ሁለት ተጨማሪ አውሮፕላኖች ሞቃዲሾ ይደርሳሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    ሶማሊያ ከኤምሬትስ ጋር ያላትን ግንኙነት ለማቋረጥ የወሰነችው ያለፈቃድ የአየር ክልሏን እና ግዛቷን በመጠቀም የየመን ተገንጣይ ቡድን መሪ የሆኑት አይዳሮስ አል-ዙባይዲን ማስወጣቷን ተከትሎ ነው።

    ኤምሬትስ ከሶማሊያ ማዕከላዊ መንግሥት እና ከክልል መንግሥታት ጋር ባላት ስምምነት መሠረት በቦሳሶ፣ በኪስማዮ እና በበርበራ ወደቦች የልማት ሥራዎች ስታከናውን ቆይታለች።

    ነገር ግን ባለፈው ሰኞ የሶማሊያ ፌዴራል መንግሥት ከዩኤኢ ጋር የገባውን የወደብ ማልማት እና የፀጥታ ስምምነት ሙሉ በሙሉ መሰረዙን አስታውቋል።

    ሶማሊያ ይህን ያደረገችው ዩኤኢ ሉዓላዊነቴን ጥሳለች በሚል ነው።

    በሁለቱ አገራት መካከል የተፈጠረውን በቅርበት የሚከታተሉ ምንጮች እንዳሉት በሶማሊያ እና በኤምሬትስ ባለሥልጣናት መካከል በሰነድ እና በፍቃድ ዙሪያ በነበሩ ሂደቶች የተነሳ አለመግባባት ተፈጥሮ ነበር።

    የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ባለሥልጣናት በመጀመሪያ የሶማሊያ መንግሥት መመሪያዎችን ተቃውመው ነበር ያሉት ምንጮቹ አውሮፕላኑ ከመነሳቱ በፊት የበረራ መግለጫዎችን እና ሌሎች አስፈላጊ መረጃዎችን አቅርበው ንብረቶቻቸውን መውጣት ችለዋል ብለዋል።

  7. ሙሴቪኒ በጊዜያዊ የምርጫ ውጤት በከፍተኛ ልዩነት እየመሩ ነው

    የኡጋንዳው ፕሬዝዳንት ዮዌሪ ሙሴቬኒ ሐሙስ ዕለት በተካሄደው የፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ጊዜያዊ ውጤት መሠረት በከፍተኛ ልዩነት እየመሩ መሆኑን የአገሪቱ የምርጫ ኮሚሽን አስታወቀ።

    አርብ ጠዋት ይፋ በተደረገው ጊዜያዊ ውጤት መሠረት ሙሴቬኒ 76 በመቶ ድምጽ በማግኘት መሪነቱን ይዘዋል። ይህ የምርጫ ውጤት የተሰበሰበው ከ45 በመቶ የአገሪቱ የምርጫ ጣቢያዎች ነው ተብሏል።

    እንደ ኤጀንሲው ጊዜያዊ የምርጫ ውጤት ከሆነ የተቃዋሚው መሪ ቦቢ ዋይን 20 በመቶ ገደማ የመራጮች ድምጽን ማግኘት ችሏል።

    ኡጋንዳውያን ከተደጋጋሚ ተቃውሞ እና አመጽ በኋላ ሐሙስ ዕለት በተካሄደው ውጥረት የበዛበት ብሔራዊ ምርጫ በቀጣይ አገሪቱን ለሚያስተዳድራት ተወዳዳሪ ድምጻቸውን ሰጥተዋል።

    የ81 ዓመቱ ፕሬዝዳንት ሙሴቬኒ የተወዳደሩት የአገሪቱን መሪነት መንበር ለሰባተኛ ጊዜ ለማሸነፍ ነው።

    የቀድሞው ድምጻዊ የ43 ዓመቱ ፖለቲከኛ ቦቢ ዋይን በምርጫው ወቅት "ከፍተኛ" ማጭበርበር እንደተፈጸመ ተናግሯል።

    ምርጫወe የተካሄደው በመላው አገሪተ ኢንተርኔት ከተቋረጠ በኋላ ነው።

    ቦቢ ዋይን ተፈፀመ ስላለው የምርጫ ማጭበርበር ምንም ዓይነት ማስረጃ ያላቀረበ ሲሆን የምርጫ ኮሚሽንም ምንም ዓይነት ምላሽ አልሰጠም።

    የቀድሞው የአማፂ መሪ ሙሴቪኒ የሚያሸንፉ ከሆነ የአራት አስርት ዓመታት የሥልጣን ዘመናቸውን ያራዝመዋል።

    ሙሴቪኒ የጦር ጄነራል የሆኑት ልጃቸው ሙሁዚ ካይነሩጋባን ተተኪ አድርገው እንደሚመርጡ በሰፊው ይታመናል።

    ይህንን ግን ፕሬዚዳንቱ አስተባብለዋል።

    የአገሪቱ የምርጫ ኮሚሽን የመጨረሻው የፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ውጤት ቅዳሜ እንደሚያሳውቅ ገልጿል።

  8. በኢራን ኢንተርኔት ከተቋረጠ 180 ሰዓታት አለፉ

    ኔት ብሎክስ የተሰኘውና በዓለም የኢንተርኔት ስርጭትን የሚከታተለው ድርጅት በኢራን የኢንተርኔት አገልግሎት ከተቋረጠ 180 ሰዓታት ማለፉን አስታወቀ።

    ድርጅቱ በኤክስ ገጹ ላይ ባሰፈረው መልዕክት አገሪቱ አሁን ያጋጠማት እአአ በ2019 ከነበረው የኢንተርኔት መቆራረጥ የበለጠ መሆኑን ገልጿል።

    በኢራን ከሁለት ሳምንት በላይ የቀጠለ ሕዝባዊ አመጽ እየተካሄደ ነው።

    አመፁ የተቀሰቀሰው የኑሮ ውድነትን ምክንያት አድርጎ ቢሆንም አገሪቱን ለረዥም ዓመታት ያስተዳደረው መንግሥት ከሥልጣን እንዲወርድ የሚጠይቁ ድምጾች ተሰምተዋል።

    የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች መንግሥት ተቃውሟቸውን ለመግለጽ አደባባይ በወጡ ኢራናውያን ላይ በወሰደው እርምጃ ከ2400 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ገልጸዋል።

    ኔት ብሎክስ እአአ በ2019 ለአንድ ሳምንት ያህል የዘለቀውን የኢንተርኔት መቋረጥ ጠቅሶ መንግሥት የወሰደው እርምጃ ምን ያህል የከፋ እንደነበር የታወቀው ኢንርኔት ዳግም ሲጀመር ነው ብሏል።

  9. የሐማስ ከፍተኛ ወታደራዊ መሪ በእስራኤል ጥቃት ተገደሉ

    እስራኤል ሐሙስ ዕለት በጋዛ ሰርጥ ዴይር አል ባላህ በፈጸመችው ጥቃት ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ መገደላቸውን ሐማስ አስታወቀ።

    ሐማስ አክሎም እስራኤል የተኩስ አቁም ስምምነቱን እየጣሰች ነው ሲል ወንጅሏል።

    በእስራኤል ጥቃት ተጨማሪ አምስት ሰዎች መገደላቸው ተገልጿል።

    እስራኤል ስለ አየር ጥቃቱ እስካሁን ድረስ ያለችው ነገር የለም።

    መቀመጫቸውን በሊባኖስ ያደረጉ ከፍተኛ የሐማስ ባለሥልጣን የአልቃሰም ብርጌዶች አዛዥ ሙሐመድ አል ሐዋሊ በእስራኤል የአየር ጥቃት መገደሉን ተናግረዋል።

    አክለውም “እስራኤል የተኩስ አቁም ስምምነቱን ለመጣስ ያላትን ፍላጎት ያሳያል’ ሲሉ ድርጊቱን ኮንነዋል።

    በተጨማሪም የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና ልየ መልዕክተኛው ስቲቭ ዊትኮፍ እስራኤል ተጠያቂ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።

    “ኳሱ ያለው በትራምፐ እና በዊትኮፍ ሜዳ ነው፤ ዋሽንግተን እስራኤል ለተኩስ አቁሙ ስምምነት ያላትን ቁርጠኝነት ማሳየት አለባቸው” ብለዋል።

    የአየር ጥቃቱ የተፈጸመው የጋዛ ጦርነትን ለመቋጨት የተፈረመው የሰላም ስምምነት ግዛቱን የሚያስተዳድር በባለሙያዎች የሚመራ መንግሥት ወደሚቋቋምበት ሁለተኛ ምዕራፍ መሸጋገሩ ከተገለፀ በኋላ ነው።

    የፍልስጤም መገናኛ ብዙኃን ሐሙስ ምሽት በሐዋሊ ቤተሰብ መኖሪያ ላይ በተፈጸመ ጥቃት የአልቃሰም ብርጌዶች ኮማንደር አል ሐዋሊ ባለቤት እና ሴት ልጅ እንዲሁም ሦስት ሰዎች መገደላቸውን ተናግረዋል።

    የሕክምና ባለሙያዎች ከተገደሉት ሰዎች መካከል የ16 ዓመት ልጅ እንደሚገኝበት ተናግረዋል።

  10. የቀድሞው የደቡብ ኮሪያ ፕሬዚዳንት በአገሪቱ ላይ ወታደራዊ አገዛዝን ለመጫን በመሞከራቸው የአምስት ዓመት እስር ተፈረደባቸው

    የደቡብ ኮሪያ የቀድሞ ፕሬዝዳንት ዮን ሱክ ዮል ሥልጣንን ያለ አግባብ በመጠቀም፣ ፍትህን በማደናቀፍ እና ሰነዶችን በማጭበርበር የአምስት ዓመት እስር ተፈረደባቸው።

    የቀድሞው ፕሬዚዳንት እአአ በ2024 ከከሸፈው የወታደራዊ አገዛዝ ሕግ በኋላ ከተመሰረቱባቸው አራት ክሶች ጋር በተያያዘ የተሰጠ የመጀመርያው ፍርድ ነው።

    ፕሬዚዳንቱ በአገሪቱ ወታደራዊ አገዛዝን ለማስፈን ያደረጉት ሙከራ አጭር ጊዜ ብቻ የቆየ ቢሆንም በመላው አገሪቱ ነውጥ ፈጥሮ ነበር።

    የቀድሞው ፕሬዚዳንት በዚህ ውሳኔያቸውም ለስድስት ሰዓታት ያህል ወታደራዊ አገዛዝን በአገሪቱ ላይ እንዲሰፍን አድርገዋል።

    ይህንን ተከትሎ ደቡብ ኮሪያውያን ለተቃውሞ አደባባይ በመውጣታቸው የሕዝብ እንደራሴዎች ዮንን ለማውረድ ብሔራዊ ጉባዔ እንዲጠሩ አስገድዷቸዋል።

    አርብ ዕለት ጉዳዮን የሚመለከቱት ዳኛ የዮን ድርጊት “አገሪቱን ወደ ፖለቲካ ቀውስ ከቷታል” በማለት የቀድሞው ፕሬዚዳንት በጥፋታቸው “ምንም ዓይነት መጸጸት አላሳዩም” ብለዋል።

    አርብ ዕለት የተሰጠው ውሳኔ ዮን ላይ የተመሠረቱት ሌሎች ክሶች ላይ የሚሰጠው ፍርድ ምን ሊሆን እንደሚችል አመላክቷል።

    ከቀረበባቸው ክሶች መካከል ከባዱ መንግሥት ላይ ማመጽ የሚል ሲሆን በዚህም አቃቤ ሕግ የሞት ቅጣት አንዲጣል ጠይቋል።

    ውሳኔው በየካቲት ወር ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል።

  11. የአፍሪካ ኅብረት በሶማሊያ ባካሄደው ዘመቻ ከ30 በላይ የአል ሸባብ ታጣቂዎች ተገደሉ

    የአፍሪካ ኅብረት በደቡብ ሶማሊያ ሐሙስ ዕለት ባካሄደው ወታደራዊ ዘመቻ ከ30 በላይ የአልሸባብ ተዋጊዎች መገደላቸው ተገለፀ።

    በታችኛው ሸበሌ ክልል የተካሄደው ወታደራዊ ዘመቻው በአየር ኃይል የታገዘ እንደነበር የገለፀው ኅብረቱ፣ የሶማሊያ ጦር እና የአፍሪካ ኅብረት ወታደሮች በጋራ መሳተፋቸውን ገልጿል።

    አፍሪካ ኅብረት ባወጣው መግለጫ በቅርቡ ከጌንዴርሼ እና ጂሊብ ማርካ የባሕር ዳርቻ አካባቢዎች ተገፍተው እንዲወጡ የተደረጉ ታጣቂዎች በወታደሮቹ ላይ ጥቃት መክፈታቸውን ተከትሎ እርምጃ መወሰዱን ተናግሯል።

    “በምድር እና በአየር በጥምረት በተፈጸመ ዘመቻ ከ30 በላይ የአልሸባብ ወታደሮች ሲደመሰሱ በርካቶች ደግሞ ቆስለዋል።”

    በዘመቻው የሶማሊያ መከላከያ ወታደሮች፣ የአፍሪካ ኅብረት የሶማሊያ ድጋፍ እና ማረጋጋት ተልዕኮ (አውሶም)፣ የቀጠናዊ እና ዓለም አቀፍ አጋሮች እንዲሁም የኡጋንዳ ጦር ተሳትፈዋል።

    አፍሪካ ኅብረት አክሎም ለጸጥታ አካላት እና ለሰላማዊ ዜጎች ስጋት የሆኑትን ለማስወገድ ፈጣን እርምጃ መውሰዱን ገልጾ ተልዕኮው ሰላማዊ ዜጎችን መከላከል እና የሰብዓዊ ድጋፍ ደህንነቱ በተጠበቁ መንገድ እንዲደርስ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆኑን አስታውቋል።

    አልሸባብ የሶማሊያ መንግሥትን ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ ሲዋጋ የነበረ ሲሆን አፍሪካ ኅብረት ወሰድኩት ባለው እርምጃ ላይ ያለው ነገር የለም።

    አፍሪካ ኅብርት የአልሸባብን እንቅስቃሴ ለመገደብ እና በሶማሊያ ዘላቂ ሰላም፣ መረጋጋት እና ደህንነት እንዲኖር ለማድረግ በጋራ የሚሠራቸውን ሥራዎች እንደሚቀጥል ገልጿል።

  12. የታዋቂዋ ናይጄሪያዊት ደራሲ ቺማማንዳ ልጅ ሞትን ተከትሎ በናይጄሪያ የሕክምና አሰጣጥ ላይ ቅሬታ ቀረበ

    የታዋቂዋ ናይጄሪያዊት ደራሲ ቺማማንዳ ንጎዚ ልጅ በሕክምና ቸልተኝነት ምክንያት መሞቱ ከተገለፀ በኋላ በናይጄሪያ ከፍተኛ ውዝግብ ተነሳ።

    የደራሲዋ ልጅ በሕክምና ቸልተኝነት ምክንያት መሞቱ ከተገለፀ በኋላ ተመሳሳይ ይዘት ያላቸው በርካታ ውንጀላዎች በናይጄሪያ የሕክምና ስርዓት ላይ ቀርበዋል።

    ዓለም አቀፍ ዕውቅና ያገኘችው ቺማማንዳ የ21 ወር ልጇ የሞተው ባለፈው ሳምንት ነበር።

    የደራሲዋ ልጅ በሌጎስ በሚገኝ የግል ሆስፒታል የሕክምና ክትትል እያገኘ እንደነበር ተገልጿል።

    ልጇ ኦክስጅን እንዳያገኝ በመደረጉ እና ከመጠን በላይ የሕመም ማስታገሻ ስለተሰጠው የልብ ድካም አጋጥሞት ሕይወቱ ሊያልፍ ቸሏል ተብሏል።

    ሆስፒታሉ በልጁ ሞት የተሰማውን ጥልቅ ሐዘን ገልጾ ምንም ዓይነት የሕክምና ስህተት አለመፈጸሙን በመግለጽ ተከራክሯል።

    የሌጎስ ከተማ አስተዳዳሪዎች በሕክምና ቸልተኝነት የተነሳ በሚከሰቱ ሞቶች የተቀሰቀሰውን የሕዝበ ቁጣ ተከትሎ በሟች ላይ ተጨማሪ ምርምራ እንዲደረግ አዝዘዋል።

  13. የኢራን የጸጥታ አካላት የተቃዋሚ ሠልፈኞችን አስከሬን ለመስጠት ከፍተኛ ገንዘብ ይጠይቃሉ ተባለ

    በኢራን የተቃውሞ ሠልፍ ወቅት የተገደሉ ሠዎችን አስከሬን ወስዶ ለመቅበር የጠየቁ የቤተሰብ አባላት ከፍተኛ ገንዘብ በባለሥልጣናት መጠየቃቸውን ለቢቢሲ ተናገሩ።

    ቢቢሲ ፐርዢያ ያነጋገራቸው በርካታ ሰዎች ከሆስፒታሎች የቤተሰቦቻቸውን አስከሬን ለመውሰድ የሚፈልጉ የቤተሰብ አባላት ገንዘብ ካልከፈሉ በስተቀር መውሰድ እንደማይችሉ በጸጥታ አካላት መከላከላቸውን ገልጸዋል።

    ከሁለት ሳምንት በላይ በመላ አገሪቱ በተካሄደው የተቃውሞ ሠልፍ ቢያንስ 2,435 ሰዎች መገደላቸውን የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች አስታውቀዋል።

    በራሻት የሚኖር አንድ ኢራናዊ የቤተሰቡን አስከሬን ለመውሰድ 5,000 ዶላር (700 ሚሊዮን ቶማን) እንዲከፍል እንደተጠየቀ ለቢቢሲ ተናግሯል።

    የቤተሰቡ አስከሬን በፖርሲና ሆስፒታል እንደሚገኝ የተናገረው ይህ ግለሰብ የሌሎች 70 ተቃዋሚ ሠልፈኞችንም አስከሬን በዚሁ እንዳለ ገልጿል።

    በግንባታ ሥራ ላይ የተሰማሩ እና አስከሬኖችን ለመውሰድ የጠየቁ ኩርዶች 7000 ዶላር እንዲከፍሉ መጠየቃቸውን ተናግረዋል።

    ቤተሰቡ የተጠየቀውን ገንዘብ መክፈል ስላልቻለ አስከሬኑ በማቆያ ውስጥ እንደተቀመጠ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል። በኢራን የግንባታ ሠራተኞች በወር የሚያገኙት ከ100 ዶላር በታች ነው።

    አንዳንድ አካባቢዎች የሆስፒታል ሠራተኞች ለሟች ቤተሰቦች በመደወል የደህንነት አባላት የልጃቸውን አስከሬን ይዘው ገንዘብ ከመጠየቃቸው በፊት በፍጥነት መጥተው እንደሚወስዱ እንደሚያስጠነቅቅቁ ቢቢሲ ሰምቷል።

    በቴህራን ምንጮች ለቢቢሲ ፐርዢያ እንደተናገሩት ባለሥልጣናት የልጆቻቸውን አስከሬን ለመውሰድ ገንዘብ ይጠይቁናል ብለው የፈሩ የቤተሰብ አባላት የአስከሬን ማቆያ ክፍል ሰብረው የወዳጅ ዘመዶቻቸውን አስከሬን መውሰዳቸውን ተናግረዋል።

    የልጆቻቸውን አስከሬን ያገኙ ቤተሰቦች የግል አምቡላንስ መጥቶ እስኪወስድላቸው ድረስ በሆስፒታል ቅጥር ግቢ ውስጥ አስከሬኑን አስቀምጠው ሲጠብቁ መታየታቸውን ምንጮች ተናግረዋል።

    በኢራን የተቃውሚ ሠልፍ ምክንያት የኢንተርኔት አገልግሎት በመቋረጡ በአገሪቱ ውስጥ ያለውን ሁኔታ ለመረዳት አስቸጋሪ አድርጎታል።

    ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ድርጅት ቡድኖች እንዲሁም ዓለም አቀፍ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ያላቸው ግንኙነት መቋረጡን ተናግረዋል።

    ቢቢሲ ኢራን ውስጥ ገብቶ እንዲዘግብ አልተፈቀደለትም።

  14. ትራምፕ በኢራን ላይ ጥቃት ላይፈጽሙ እንደሚችሉ ከተናገሩ በኋላ የዓለም የነዳጅ ዋጋ ቀነሰ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በኢራን ላይ ጥቃት ላይፈጽሙ እንደሚችሉ ከተናገሩ በኋላ በዓለም ገበያ የነዳጅ ዘይት ዋጋ ቅናሽ አሳየ።

    የአንድ በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ ወደ 64 ዶላር ዝቅ በማለት የአራት በመቶ ቅናሽ አስመዝግቧል።

    ባለፉት ቀናት የአንድ በርሜል ነዳጅ ዋጋ 67 ዶላር ነበር።

    በሌላ በኩል ረቡዕ ዕለት የወርቅ ዋጋ ወደ 4ሺህ 600 ዶላር ከፍ ያለ ሲሆን፣ ይህም ማክሰኞ ከነበረው በ0.4 በመቶ ከፍ ያለ ሆኗል።

    ትራምፕ በጽህፈት ቤታቸው ለተሰበሰቡ ጋዜጠኞች "ኢራን ዜጎቿን በሞት መቅጣት ማቆሟን ሰምተናል። . . . .በሞት የመቅጣት ዕቅድ የለም” ብለው ነበር።

    ፕሬዚዳንቱ ከዚህ ቀደም የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ላይ “በጣም ጠንከር ያለ እርምጃ” እንደሚወስዱ ዝተው ነበር።

    የነዳጅ ዘይት ዋጋ ከ1 በመቶ በላይ ጭማሪ አሳይቶ የነበረ ቢሆንም የትራምፕን አስተያየት ተከትሎ ወዲያውኑ ቅናሽ ተመዝግቧል።

    ትራምፕ በኢራን ላይ ወታደራዊ እርምጃ መውሰዳቸውን ትተውት እንደሆን ሲጠየቁ ያለውን ሁኔታ እየተከታተሉ መሆኑን ገልጸዋል።

  15. የዴንማርክ የአውሮፓ አጋሮች በግሪንላንድ ወታደራዊ ተልዕኳቸውን ጀመሩ

    አስራ አምስት የፈረንሳይ ጦር አባላት ግሪንላንድ ዋና ከተማ ኑክ መድረሳቸውን ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    በርካታ የአውሮፓ አገራት ወታደሮቻቸውን ወደ ግሪንላንድ ለቅኝት ተልዕኮ አሰማርተዋል።

    ጀርመን፣ ስዊዲን፣ ኖርዌይ እና ዩናይትድ ኪንግደምን ወታደሮቻቸውን የላኩ ሲሆን፣ ዶናልድ ትራምፕ የዴንማርክ ራስ ገዝ የሆነችው ግሪንላንድ ትገባኛለች ማለታቸውን ቀጥለውበታል።

    የኔቶ የአውሮፓ አጋሮች ወታደሮቻቸውን ወደ ግሪንላንድ መላካቸው ያልተጠበቀ እርምጃ ነው ተብሏል።

    የፈረንሳይ ልዩ መልዕክተኛ ኦሊቪር ዲ አርቮር ጠንካራ የፖለቲካ መልዕክት ያስተላልፋል ሲሉ ተናግረዋል።

    “ይህ የመጀመሪያው ልምምድ ነው. . . ለአሜሪካ ኔቶ መኖሩን እናሳያታለን።”

    የወታደሮች የጋራ ልምምድ የተሰማው የዴንማርክ እና የግሪንላንድ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ወደ ዋሺንግተን አቅንተው ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ ካገኙ በኋላ ነው።

    ከስብሰባው በኋላ የዴንማርክ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ላርስ ሎኬ ራስሙሰን እንደተናገሩት ውይይቱ ገንቢ ቢሆንም፣ በሁለቱ ወገኖች መካከል "መሠረታዊ አለመግባባት" እንዳለ ጠቀወሰው ትራምፕ ግሪንላንድን ለመግዛት ያቀረቡትን ጥያቄ ተችተዋል።

  16. ሩሲያ በሰላይነት የወነጀለችውን የብሪታንያ ዲፕሎማት አባረረች

    ሩሲያ ሞስኮ በሚገኘው የብሪታኒያ ኤምባሲው ውስጥ በድብቅ የሚሠራ ሰላይ ነው የሚል የወነጀለችው የብሪታኒያ ዲፕሎማት አገሪቱን ለቅቆ እንዲወጣ አዘዘች።

    የዲፕሎማቲክ እውቅናው የተሰረዘው ይህ ማንነቱ ያልተገለጸው ግለሰብ፤ በሁለት ሳምንት ጊዜ ውስጥ አገሪቱን ለቅቆ መውጣት እንዳለበት የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።

    ሚኒስቴሩ ባወጣው መግለጫ፤ በሩሲያ የሚገኙት የብሪታንያ ጉዳይ ፈጻሚ ዳኔ ዶላኪያ በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ እንዲሰጡ መጥራቱንም ገልጿል።

    የዩናይትድ ኪንግደም መንግሥት እስካሁን ውንጀላውን በተመለከተ አስተያየት አልሰጠም።

    ሞስኮ ወደ ግዛቷ የሚገቡ "በይፋ የማይታወቁ የብሪታንያ የደኅንነት መኮንኖችን" እንደማትታገስ ገጻለች። ዩናይትድ ኪንግደም ሁኔታውን የምታባብሰው ከሆነም ተጨማሪ እርምጃ እንደምትወስድም አስጠንቅቃለች።

    ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የዩናይትድ ኪንግደም እና የሩሲያ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት እየሻከረ መጥቷል። በሩሲያ በ2022 ዩክሬን ላይ ሙሉ ወረራ ከከፈተች በኋላ ሁለቱም አገራት በግዛቶቻቸው ውስጥ የሚገኙ በርካታ ዲፕሎማቶችን አባርረዋል።

    ባለፈው ዓመት መጋቢት ላይ ሩሲያ ሰላይ ናቸው በሚል የወነጀለቻቸውን ሁለት የብሪታንያ ባለሥልጣናትን አባርራ ነበር። የዩናይትድ ኪንግደም የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት በወቅቱ በሰጠው ምላሽ፤ ሞስኮ በሠራተኞቹ ላይ "ተንኮል ያዘለ እና መሠረተ ቢስ ክስ" አቅርባለች በማለት ወቅሶ ነበር።

    "በብሪታንያ ኤምባሲ ሠራተኞች እና ቤተሰቦቻቸው ላይ የሚደረግ ማስፈራራትን አንታገስም" ያለችው ዩናይትድ ኪንግደም በምላሹ የአንድ ሩሲያዊ ዲፕሎማት እና ባለቤቱን እውቅና ሰርዛለች።

  17. የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታ ምክር ቤት በድጋሚ በኢራን ጉዳይ ሊሰበሰብ ነው

    የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት በኢራን የተከሰተውን ተቃውሞ እና የተፈጠረውን ውጥረት ተከትሎ ለሁለተኛ ጊዜ ዛሬ ሐሙስ ስብሰባ ያካሂዳል።

    በአሜሪካ ጠያቂነት ይካሄዳል በተባለው የምክር ቤቱ ስብሰባ ላይ ከሁለት ሺህ በላይ ተቃዋሚዎች ተገድለውበታል ስለተባለው የኢራናውያን የተቃውሞ እንቅስቃሴ እና በአገሪቱ ስላለው ሁኔታ ውይይት ይደረጋል ተብሏል።

    ሦስተኛ ሳምንቱን እያጠናቀቀ ያለው የኢራን ሕዝባዊ ተቃውሞ አብዛኛውን የአገሪቱ ከተሞች ያዳረሰ ሲሆን፣ መንግሥትም ተቃውሞውን ለመቆጣጠር እርምጃ እየወሰደ ነው።

    እስካሁን ከ2,500 በላይ ሰዎች መገደላቸው ሲነገር ጥቂት የማይባሉ የመንግሥት ፀጥታ ኃይል አባላት መገደላቸው ተዘግቧል።

    የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታ ምክር ቤት ከሳምንት በፊት በኢራን ጉዳይ ላይ አስቸኳይ ስብሰባ ማድረጉ የሚታወስ ሲሆን፣ የአሁኑ ደግሞ በአገሪቱ ስላለው ሁኔታ ማብራሪያ እንደሚቀርብበት ተገልጿል።

    ረቡዕ ዕለት የመብት ተከራካሪው አምነስቲ ኢንተር ናሽናል የመንግሥታቱ ድርጅት የፀጥታ ምክር ቤት "ኢራን ውስጥ ተጨማሪ ግድያዎችን ለማስቆም" አስቸኳይ ስብሰባ እንዲጠራ የሚጠይቅ መግለጫ አውጥቷል።

    አምነስቲ ዓለም አቀፉ የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ የኢራን ባለሥልጣናት የሕጋዊ ጥበቃ መብታቸው ማብቃቱን እንዲያውቁ ማድረግ አለበት ሲል ጥሪ አቅርቧል።

    ድርጅቱ ጨምሮም ኢራን ውስጥ መጠነ ሰፊ ከሕግ ውጪ ግድያ መፈጸሙን ከቪዲዮዎች እና ከታማኝ የዓይን ምስክሮች እንዳረጋገጠ በሪፖርቱ ገልጿል።

  18. ስታርሊንክ ኢራናውያን በነጻ ኢንተርኔት እንዲጠቀሙ ፈቀደ

    የዓለማችን ቁጥር አንድ ሀብታም ኢላን መስክ ንብረት የሆነው የሳተላይት ኢንተርኔት አቅራቢው ስታርሊንክ፤ ኢራን ውስጥ ከክፍያ ነጻ የሆነ የኢንተርኔት አገልግሎት አቀረበ።

    የኢራን መንግሥት በአገሪቱ ውስጥ ያለውን የኢንተርኔት አቅርቦት በማቋረጡ ምክንያት በሳተላይት የሚሠራው ለስታርሊንክ ወርሃዊ ክፍያ እየፈጸሙ ይጠቀሙ የነበሩ ኢራናውያን አገልግሎቱን በነጻ እንዲያገኙ ፈቅዷል።

    ምንም እንኳን ስታርሊንክ በኢራን ውስጥ ሕገወጥ ቢሆንም በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ ኢራናውያን በድብቅ አገልግሎቱን ይጠቀማሉ።

    የኢራን መንግሥት ከሚሰጠው የኢንተርኔት አገልግሎት ውጪ ቁጥጥር የሚያደርግበትን ስታርሊንክን ሲጠቀሙ የሚገኙ ሰዎች እስከ ሁለት ዓመት የሚደርስ የእስር ቅጣት ይጠብቃቸዋል።

    ሦስት ሳምንት የሞላውን ተቃውሞ ተከትሎ ባለፈው ሳምንት ሐሙስ በመላው ኢራን ኢንተርኔት የተዘጋ ሲሆን፣ ባለሥልጣናትም ዜጎች ኢንተርኔት እንዳይጠቀሙ ለማገድ የስታርሊንክ ማገናኛ የሳተላይት ሳህኖችን እያሰሱ ነው።

    ኢራን ውስጥ ኢንተርኔት በመቋረጡ ምክንያት በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች ግንኙነት ከመስተጓጎሉም በላይ መንግሥት በተቃዋሚዎች ላይ እየወሰደ ያለው የሰዎችን ሕይወት የቀጠፈ እርምጃ በቀሪው ዓለም እንዳይታወቅ አድርጓል።

  19. ግሪንላንድ፣ ዴንማርክ እና አሜሪካ ያደረጉት ውይይት ያለስምምነት ተጠናቀቀ

    ከአሜሪካ አቻቸው ጋር የተወያዩት የዴንማርክ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በግሪንላንድ ጉዳይ “ከአሜሪካ ጋር መሠረታዊ ልዩነት” እንዳላቸው ተናገሩ።

    ላርስ ሎክ ራስሙሰን ከአሜሪካው ምክትል ፕሬዝደንት ጄዲ ቫንስ እና ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማርኮ ሩቢዮ ጋር በዋይት ሐውስ ተወያይተዋል።

    “ውይይታችን ግልፅ እና ገንቢ ነው” ያሉት ላርስ የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ግሪንላንድን “እንጠቀልላታለን” ማለታቸው “ተቀባይነት የለውም” ብለዋል።

    አሜሪካ፣ ዴንማርክ እና ግሪንላንድ ያደረጉት አንድ ሰዓት የወሰደ ውይይት ያለስምምነት ተጠናቋል። ነገር ግን የግሪንላንድ ዕጣ ፈንታን ለመወሰን በከፍተኛ ባለሥልጣናት ዘንድ ንግግር ሊኖር እንደሚገባ እንደተስማሙ ተዘግቧል።

    የአሜሪካው ፕሬዝደንት በተደጋጋሚ ግሪንላንድን መቆጣጠር ለብሔራዊ ደኅንነት ወሳኝ ነው ሲሉ ይሰማል።

    ይህ የትራምፕ አቋም የኔቶ አባል የሆነችውን ዴንማርክ ያስቆጣ ነው።

    ከመሬት ስፋቷ አንፃር እጅግ ትንሽ ሰው የሚኖርባት ግሪንላንድ በሰሜን አሜሪካ እና አርክቲክ መካከል መገኘቷ የሚሳዔል ጥቃት ቢመጣ ቀድሞ ለማሳወቅ እና በአካባቢው የሚንቀሳቀሱ መርከቦችን ለመቆጣጠር ወሳኝ ሥፍራ ያደርጋታል።

    አሜሪካ ሰሜን ምዕራብ ግሪንላንድ በሚገኘው ፒቱፊክ የጦር ካምፕ 100 ያክል ወታደሮች ያሏት ሲሆን፣ ይህ ካምፕ ከሁለተኛ ዓለም ጦርነት ጀምሮ በአሜሪካ ሲመራ ቆይቷል።

    አሜሪካ ከዴንማርክ ጋር ባላት ስምምነት መሠረት የፈለገችውን ያህል የወታደር ቁጥር ወደ ግሪንላንድ መላክ ትችላለች።

  20. ትራምፕ ኢራን ተቃዋሚዎችን መግደል “እያቆመች ነው” አሉ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ ኢራን ተጨማሪ ተቃዋሚዎችን የመግደል “እቅድ የላትም” ቢሉም ቴህራን በመንግሥት ተቃዋሚ ሰልፈኞችን ላይ የወሰደችውን እርምጃ ተከትሎ አሜሪካ ለመውሰድ የዛተችው እርምጃ ስለመቅረቱ ግን አልገለጹም።

    ረቡዕ ዕለት በዋይት ሀውስ ንግግር ያደረጉት ትራምፕ፤ “በኢራን ግድያው እየቆመ መሆኑ እና ግድያ ለመፈጸም እቅድ እንደሌለ”፤ አስተዳደራቸው በአንድ “ጥሩ ባለሥልጣን” እንደተነገረው ገልጸዋል።

    ትራምፕ ጋዜጠኞች ለተነሳላቸው ጥያቄ ምላሽ ሲሰጡ፤ ይህንን መረጃ የሰጣቸው “በሌላው ወገን ያለ በጣም ጠቃሚ ምንጭ” እንደሆነ ተናግረዋል። ይህ መረጃ እውነት ይሆናል ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉም አክለዋል።

    ታህሳስ ላይ የጀመረው የኢራን ተቃውሞ የተቀሰቀሰው የአገሪቱ ገንዘብ አቅም በከፍተኛ ደረጃ መውደቁን ተከትሎ ነበር። ይሁን እንጂ በተለያዩ ግዛቶች በፍጥነት የተስፋፋው ተቃውሞ፤ የኢራን ሃይማኖታዊ አገዛዝ ላይ የቅቡልነት ቀውስ ፈጥሯል።

    ትራምፕ፤ የኢራን መንግሥት ተቃዋሚዎችን የሚገድል ከሆነ “እጅግ ጠንካራ እርምጃ” እንደሚወስዱ ዝተው ነበር። ፕሬዝዳንቱ ይህንን ያሉት፤ በተቃውሞው ወቅት የተያዘ ኤፍራን ሶልታኒ የተባለ የ26 ዓመት ሰልፈኛ የሞት ፍርድ እንደተፈረደበት መገለጹን ተከትሎ ነው።

    ተቃዋሚው ረቡዕ ዕለት የሞት ቅጣት ሊፈጸምበት ቀጠሮ ተይዞ እንደነበር ቤተሰቦቹ ተናግረዋል። ኋላ ላይ ግን ቅጣቱ ተፈጻሚ የሚሆንበት ቀን እንደተራዘመ በኖርዌይ ለሚገኝ የሰብአዊ መብቶች ተሟጋች ቡድን ገልጸዋል።

    መንግሥት ሊፈጽመው ስለሚችል የሞት ቅጣት ጥያቄ ከጋዜጠኞች ጥያቄ የቀረበላቸው የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ፤ “ስቅላት ከጥያቄ ውጪ ነው” ብለዋል። “ዛሬ ወይም ነገ ምንም ስቅላት አይኖርም” ሲሉም ተናግረዋል።