ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
የድሬዳዋ ቀለማት
በስምጥ ሸለቆ ምሥራቃዊ ዳርቻ ላይ የምትገኘው የድሬዳዋ ከተማ ምሥረታዋ በ19ኛው መቶ ክፍለ-ዘመን መደምደሚያ ላይ ከተዘረጋውና መዲናይቱ አዲስ አበባን ከጅቡቲ ጋር ከሚያገናኘው የባቡር መስመር ጋር ይያያዛል።
የባቡር መስመሩ እና ከእርሱም ጋር ተያይዞ በከተማዋ እምብርት የተቋቋመው ጣቢያ ለንግድ መጧጧፍ ትልቅ በር ከመክፈቱም ባሻገር በሺህዎች ለሚቆጠሩ የአካባቢው ኗሪዎች ሥራን ፈጥሮ ነበር።
ከጥቂት ዓመታት አንስቶ ግን መስመሩ ለዕድሜ ጫና እጅ ሰጥቶ የወትሮ አገልግሎቱን መስጠት ተስኖታል። ቀድሞ ይታወቅበት የነበረው ግርግር እና ሞቅታ ርቆት ድብታ ተጭኖታል።
ሁለቱን ራስ ገዝ የከተማ አስተዳደሮች፤ አዲስ አበባ እና ድሬዳዋን ማገናኘቱ ቢቀርም ግን ወደ ጅብቲ በየሳምንቱ የተወሰኑ ጉዞዎችን ያደርጋል። የአዲሱ የኢትዮ-ጅቡቲ የባቡር መስመር እውን መሆን ተስፋቸውን እንዳወገገው ሰራተኞች ይናገራሉ።
በ1920ዎቹ መጨረሻ የጣልያን ወራሪ ኃይሎች ድሬዳዋ ከተማ እና የባቡር መስመሩን ይዘዋቸዋል። በከተማዋ ውስጥ በነበሩት ከፍተኛ ቁጥር ባላው አውሮፓውያን ምክንያት የጣልያን ኃይሎች በከተማዋ ላይ የበረታ ዱላ ከማሳረፍ እንደተቆጠቡ የሚያትቱ ፀሐፍት አሉ። ከተማዋ ከጣልያን ኃይሎች ነፃ ከወጣች በኋላ የብሪታንያ ተፅዕኖ ጎላ ብሎ ቆይቷል። "ነምበር ዋን" ተብሎ የሚጠራው አካባቢ ለዚህ ምስክር ሲሆን፥ አካባቢው ከጣልያን ኃይሎች ጋር ሲፋለሙ ህይወታቸውን ላጡ 73 አፍሪካዊ ወታደሮች እና 3 የብሪታንያ ዘውዳዊ አየር ኃይል መኮንኖች መካነ መቃብር ይገኝበታል።
በ1999 ዓ.ም የተከናወነው የሕዝብ ቆጠራ ድሬዳዋ ከ340 ሺህ በላይ ኗሪዎች እንዳሏት አሳይቷል። ይህ ቁጥር በእርግጥ በከተማዋ አስተዳደር ስር የሚገኙ አጎራባች የገጠር ቀበሌዎችንም የሚጨምር ነው። አሁን ቁጥሩ ግማሽ ሚሊዮን እንደደረሰ ይገመታል። ድሬዳዋ ለዘመናት በንግድ ማዕከልነት ባለፉት ጥቂት ዓመታት የንግድ እንቅስቃሴ መፋዘዝ እንዳጋጠመው ቢቢሲ በከተማዋ ተገኝቶ ያነጋገራቸው ነጋዴዎች ይገልፃሉ። አሁንም ግን ልዩ ልዩ አሻራ ያረፈባቸው ዝብርቅርቅ ቀለማቷን እና ጣፋጭ ምግቦቿን አቅፋ ይዛ ትገኛለች።