ደቡብ ኮሪያ ውስጥ በአመት አንድ ሚሊዮን ውሻዎች ታርደው ይበላሉ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የደቡብ ኮሪያ ባለስልጣናት በሃገሪቱ ትልቁ የሚባለውን የውሻዎች ማረጃና ማቀነባበሪያ ማዕከል ማፈራረስ ጀምራለች።
ታዪፒዮንግ ዶንግ የተባለው እጅግ ሰፊ ማዕከል የሚገኘው ሲዮንግናም በምትባል ከተማ ውስጥ ሲሆን፤ በቅርቡ ለከተማዋ ነዋሪዎች የመዝናኛ ማዕከል ይገነባበታል ተብሏል።
ደቡብ ኮሪያ ውስጥ በየዓመቱ እስከ 1 ሚሊዮን የሚደርሱ ውሻዎች ለምግብነት ይውላሉ።
በእዚች ሃገር የውሻ ስጋ ትልቅ የክብር ምግብ ሆኖ ለዘመናት ቢቆይም፤ አሁን አሁን ግን ከዘመናዊነት ጋር በተያያዘ ይህ አስተሳሰብ እየቀነሰ መጥቷል።
አንድ የኮሪያ የእንስሳት መብት ተሟጋች የሃላፊዎቹን ውሳኔ ታሪካዊ በማለት ገልጾታል። ጨምሮም ይህ እንቅስቃሴ በመላው ሃገሪቱ ያሉ ሌሎች የውሻ እርድ የሚካሄድባቸው ማዕከላትን ለማስዘጋት የሚደረገውን እንቅስቃሴ ያበረታታል ብሏል።
የታዪፒዮንግ ዶንግ ማዕከል በሃገሪቱ ለሚገኙ ብዙ ምግብ ቤቶች ዋነኛ የስጋ አቅራቢ ሲሆን፤ በአንድ ጊዜ በመቶዎች የሚቆጠሩ ውሻዎችን ማስተናገድ የሚችል ነው።
ሌላኛዋ የከተማዋ ነዋሪ ናራ ኪም በበኩሏ ማዕከሉ ለከተማዋ ጥሩ ያልሆነ ገጽታ አላብሷት ስለነበረ በመፍረሱ እጅግ መደሰቷን ገልጻለች።
ኮሪያ ውስጥ በየዓመቱ ለሶስት ቀናት በሚቆይ በአል ላይ የውሻ ስጋ በተለየ መልኩ ተሰርቶ የሚበላ ሲሆን፤ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ግን ዜጎች ለበአላቱ የዶሮ ስጋን ማዘውተር ጀምረዋል።
ከዚህ በተጨማሪ በሃገሪቱ ዋና ከተማ ሴዉል የውሻ ስጋን የሚያቀርቡ 1500 ምግብ ቤቶች የነበሩ ሲሆን፤ በቅርቡ በተደረጉ ቆጠራዎች ወደ 700 ዝቅ ማለታቸው ተገልጿል።
የደቡብ ኮሪያውያ አንድ አምስተኛ የሚሆነው ህዝቧ ደግሞ ውሻዎች ከምግብነት ይልቅ የቤት እንስሳ ነው መሆን ያለባቸው ብለው ያምናሉ።
በአሁኑ ሰአት በሃገሪቱ ውስጥ የውሻ ስጋን መመገብም ሆነ ማረጃ ቤቶች መክፈትን የሚከለክል ምንም አይነት ህግ የለም።












