ትራምፕ ስፔን ሰሃራ በረሃ ላይ አጥር እንድትገነባ መከሩ

የፎቶው ባለመብት, AFP/GETTY IMAGES
በአውሮፓ ላጋጠመው የስደተኞች ቀውስ የሰሃራ በረሃን የሚያካልል አጥር መገንባት መፍትሄ ነው ሲሉ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ለስፔን የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር መምከራቸው ተነገረ።
የቀድሞው የአውሮፓ ፓርላማ ፕሬዝዳንት የነበሩትና አሁን የስፔን የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር የሆኑት ጆሴፍ ቦሬል ግን ትራም በሰጧቸው ምክር እንዳልተስማሙ ገልፀዋል።
ሚኒስትሩ ይህን ምክር ከትራምፕ የሰሙት ባለፈው ሰኔ ወር ላይ በአሜሪካ ባደረጉት ጉብኝት ወቅት ነበር።
ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለምርጫ በሚወዳደሩበት ጊዜ በሜክሲኮና በሃገራቸው መካከል ግንብ እንደሚገነቡ የገቡት ቃል በተለይ የሚታወቁበት የቅስቀሳቸው ዋና ጉዳይ ነበር።
የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ ቦሬል ይህን ከፕሬዝዳንት ትራምፕ ጋር የነበራቸውን ውይይት ይፋ ያደረጉት በዚህ ሳምንት ማድሪድ ውስጥ በተካሄደ የምሳ ግብዣ ላይ ሲሆን፤ የስፔን የውጪ ጉዳይ መስሪያ ቤትም ይህንኑ ለቢቢሲ አረጋግጠወል።
ትራምፕ "ከሰሃራ ጋር የሚያዋስናችሁ ድንበር ርዝመት እኛን ከሜክሲኮ ጋር ከሚያዋስነን ድንበር የሚበልጥ ሊሆን አይችልም" ማለታቸውን ቦሬል ጠቅሰዋል።
አሜሪካንን ከሜክሲኮ ጋር የሚያዋስናት ድንበር ርዝመቱ 1954 ማይሎች ሲሆን የሰሃራ በረሃ ግን 3ሺህ ማይሎችን ይረዝማል።
ስፔን ከሰሃራ በረሃ ጋር የሚያገናኝ ግዛት የሌላት ቢሆንም በሰሜን አፍሪካ የባሕር ዳርቻ አካባቢ በአወዛጋቢ የሽቦ አጥር ከሞሮኮ ተለይተው የሚገኙ ሁለት ትንንሽ ግዛቶች አሏት።
እነዚህ ግዛቶችም ግጭቶችንና ጭቆናን በመሸሽ የተሻለ ህይወት ፍለጋ ወደ አውሮፓ ለመሻገር ለሚፈልጉ አፍሪካዊያን ስደተኞች ተመራጭ ስፍራዎች ሆነው ቆይተዋል።
ከባለፈው ዓመት ጥር ወር አንስቶም ቢያንስ 35 ሺህ የሚሆኑ ሰነድ የሌላቸው ስደተኞች ወደ ስፔን የገቡ ሲሆን ይህም ከየትኛውም አውሮፓዊ ሃገር በላቀ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ስደተኛ የተቀበለች ሃገር ያደርጋታል።















