ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
የኢትዮጵያ የባሕር በር ፍላጎት እና የባሕር በር ለማግኘት ያሏት አማራጮች
ኤርትራ ነጻነቷን ካወጀች በኋላ የባሕር በር አልባ በሆነችው ኢትዮጵያ ውስጥ በመንግሥት ደረጃ ስለ ወደብ ባለቤትነት ጉዳይ በይፋ ተነስቶ አያውቅም። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ወደ ሥልጣን መምጣታቸውን ተከትሎ ግን ከባሕር በር ጋር የተያያዙ ጉዳዮች በቀጥታ እና በተዘዋዋሪ ሲነሱ ቆይተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የመሪነት መንበሩን እንደያዙ ከሰላሳ ዓመታት በፊት የፈረሰውን የኢትዮጵያ ባሕር ኃይልን መልሶ በማዋቀር የአገሪቱ ጦር ኃይሎች አባል ሲያደርጉ፣ ከባሕርም ሆነ ከውቅያኖስ ጋር የሚያጎራብት ድንበር የሌላት አገር ስለምን የባሕር ኃይል ያስፈልጋታል በሚል ጥያቄ ሲነሳ ቆይተዋል።
በተለይ ባለፈው ዓመት ውስጥ የኢትዮጵያ የባሕር በር የማግኘት ፍላጎት ከፓርቲ አባላት ስብሰባ አንስቶ እስከ ታዋቂ ሰዎች በተሳተፉባቸው ስብሰባዎች ላይ በቀጥታ እና በተዘዋዋሪ ሁኔታ ሲነሳ እና ውይይት ሲደረግ እንደቆየ በተደጋጋሚ ተሰምቷል።
በዚህ ዓመት መጀመሪያ ላይ ደግሞ በመንግሥት መገናኛ ብዙኃን በተመሳሳይ ዕለት በተላለፈው እና ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ለአገሪቱ ሕግ አውጪዎች ባደረጉት ንግግር ላይ ኢትዮጵያ የባሕር በር እንደሚያስፈልጋት እና ለዚህም ውይይት መጀመር እንዳለበት ሲናገሩ ተደምጠዋል።
ኤርትራ ነጻ አገር ስትሆን ወደብ አልባ የሆነችው ኢትዮጵያ በምሥራቅ እና በአፍሪካ ቀንድ ውስጥ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሕዝብ እንዲሁም ሰፊ የቆዳ ስፍት ኖሯት የባሕር በር የሌላት ትልቋ አገር ከሆነች ከሦስት አስርት ዓመታት በላይ ሆኗታል።
በዚህ ጊዜም ለተወሰኑ ዓመታት የኤርትራን እና የጂቡቲን ወደቦች ለገቢ እና ወጪ ጭነቶች ስትጠቀም ቆይታ ከኤርትራ ጋር ጦርነት ሲቀሰቀስ አጠቃላይ የወደብ ፍላጎቷ በጂቡቲ በኩል ሆኖ፣ አሁንም ድረስ አብዛኛው እንቅስቃሴዋ በጂቡቲ ወደብ ላይ ጥገኛ ሆኖ ይገኛል።
ባለፉት አምስት ዓመታት ፈርሶ የነበውን ባሕር ኃይሏን መልሶ ለመገንባት ስታደርግ የነበረውን ጥረት ተከትሎ ኢትዮጵያ በቀይ ባሕር በኩል የባሕር በር እንደሚያስፈልጋት፣ ይህም የህልውናዋ ጉዳይ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በይፋ መናገራቸው ጉዳዩን ዋነኛ መነጋገሪየ ርዕስ አድርጎት ቆይቷል።
“ቀይ ባሕር እና አባይ ኢትዮጵያን የሚበይኑ፣ ከኢትዮጵያ ጋር የተቆራኙ፣ ለኢትዮጵያ ዕድገት እና ጥፋት መሠረት ናቸው” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በሌላ ሥነ ሥርዓት ላይ ደግሞ ከዚሁ ጋር በተያያዘ አገራቸው በኃይል እና በወረራ ማሳካት የምትፈልገው ነገር የለም ሲሉ ተናግረዋል።
ዓለም አቀፉ ሕግ ምን ይላል?
የባሕር በር ለሌላቸው አገራት የባሕር መተላለፊያ በር የማግኘት መብትን በተመለከተ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የወጣ ኮንቬንሽን አለ።
ይህም ከባሕር እና ከውቂያኖስ ጋር የሚጎራበት ድንበር የሌላቸው ዝግ አገራት በዙሪያቸው በሚገኙ ባለ ወደብ አገሮች አማካይነት አገልግሎት ማግኘት የሚያስችል ስምምነት ነው።
የባሕር በር የሌላቸው አገራት የባሕር መተላለፊያ የማግኘት መብት እንዳላቸው በኮንቬንሽኑ ላይ መስፈሩን የሚናገሩት ዓለም አቀፍ የሕግ ባለሙያ እና በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ውስጥ ከሦስት አሥርት ዓመታት በላይ የሠሩት አቶ ባይሣ ዋቅወያ፣ ይህም “በሁለት አገራት መካከል በሚያደረግ ስምምነት እንደሚሆን አስፍሯል” ይላሉ።
በዚህም ምክንያት የኮንቬንሽኑ ዋነኛ ማዕከልም የባሕር በር አጠቃቀም ጉዳይ በሁለት አገራት መካከል ባለ የወዳጅነት ደረጃ ላይ የሚወሰን መሆኑን በማመልከት፣ “አገራት የባሕር በር የለኝምና በሌላ አገር ውስጥ አልፌ የባሕር በር ላግኝ የማለት መብት የላቸውም፤ ዓለም አቀፍ ሕግም አይደግፋቸውም” ይላሉ።
ኮንቬንሽኑ ተግባራዊ የሚሆነው በአገራት መካከል በሚደረግ ስምምነት መሠረት በመሆኑ “የተገደበ መብት ነው” የሚሉት አቶ ባይሣ፣ ነገር ግን የባሕር በር የሌላቸው አገራት የባሕር መተላለፊያ ቢያገኙ ለራሳቸው ብቻ ሳይሆን ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብም ጭምር ጥቅም የሚያስገኝ በመሆኑ ከዚህ አንጻር ሊታይ እንደሚገባው ማስቀመጡን ጠቅሰዋል።
ምን አማራጮች አሉ?
ሰፊው ክፍሏ በባሕሮች እና በውቅያኖሶች በተሸፈነው ዓለም ላይ ከሚገኙት ወደ ሁለት መቶ ከሚጠጉ ሉዓላዊ አገራት መካከል 44ቱ የባሕር በር የላቸውም።
ከእነዚህም መካከል እንደካዛኪስታን ያሉ ሰፊ ግዛት ያላቸው አገራት በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ። ኢትዮጵያም ትልቅ የሕዝብ ብዛት እና ሠፊ ግዛት ይዛ የባሕር በር ከሌላቸው የአፍሪካ ሆነ የዓለም አገራት ዋነኛዋ ናት።
ነገር ግን ኢትዮጵያ በባሕር አማካይነት ለሚፈረጉ የንግድ ልውውጦች በዙሪያዋ የሚገኙትን የጂቡቲን፣ የኤርትራን፣ የሶማሊያን፣ የኬንያን እና የሱዳንን ወደቦች ለመጠቀም የሚያስችል ሰፊ አማራጭ አላት።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የአገራቸውን የባሕር በር የማግኘት ፍላጎትን ከማንሳታቸው እና ከኤርትራ ጋር ከነበረው ግንኙነት አንጻር ብዙዎች ጉዳዩን ከአሰብ ወደብ ጋር አያይዘውታል።
የዓለም አቀፍ ሕግ ባለሙያው አቶ ባይሣም ለኢትዮጵያ ድንበር ካለው ቅርበት እና ከዚህ በፊትም ሲሰጥ ከነበረው አገልግሎት በመነሳት ስለኢትዮጵያ የባሕር በር የማግኘት አማራጭ የሚያስረዱት አሰብን በመጥቀስ ነው።
ኢትዮጵያ በዙሪያዋ ካሉ አገራት ጋር መግባባት እና ስምምነት ላይ መድረስ ከቻለች የባሕር በር ለማግኘት ሦስት አማራጮች እንዳሉ አቶ ባይሣ በዝርዝር ያስረዳሉ።
የመጀመሪያው ግዛት መቀያየር ነው። በዚህም የወደብ መተላለፊያ የሚሠጠው አገር ይጠቅመኛል የሚለውን ኢትዮጵያ ክፍል የሆነ መሬትን አሳልፎ በመስጠት በምላሹ የባሕር በር ማግኘት ይቻላል።
ሁለተኛው በምርት መቀያየር ነው። ኢትዮጵያ ምርቶቿን ለዚያ አገር መስጠት ይጠበቅባታል። ለምሳሌ ኢትዮጵያ ቡና፣ የኤሌክትሪክ ኃይል ወይም ሌላ ምርት መስጠት ትችላለች ማለት ነው። በተቃራኒው ደግሞ ሌላኛው አገር ወደቡን ለኢትዮጵያ ጥቅም ይሰጣል።
ሦስተኛው አማራጭ በገንዘብ ነው። ኢትዮጵያ ተወዳዳሪ ወይም በቅናሽ ክፍያ ወደቡን የምትጠቀምበትን አማራጭ ማግኘት ነው። በዚህም በዙሪያዋ ያሉ አገራትን በማወዳደር በቅናሽ የወደብ አገልግሎት ታገኛለች። በተጨማሪም ሰፊ አማራጭ እና አስተማማኝ የመተላለፊያ መስመር እንድታገኝ ያደርጋታል።
አቶ ባይሣ “መንግሥት ከእነዚህ ሦስቱ አንዱን ለመተግበር ይወስናል” ሲሉ ግምታቸውን ከማስቀመጥ በተጨማሪ፣ ይህ ሁሉ ግን የሚሆነው በአገራቱ መካከል ባለ ወዳጅነት እና ስምምነት አማካይነት በሚደረስ ውሳኔ መሆኑን አስምረውበታል።
የባሕር በር ባለቤት መሆን ይቻላል?
የባሕር በር የሌላቸው አገራት እንዲሁ ፍላጎት ስላላቸው የባሕር በር ባለቤት መሆን አይችሉም፤ የባሕር በር ካላቸው አገራት ጋር ባላቸው ስምምነት ግን እውን ሊሆን ይችላሉ ይላሉ አቶ ባይሣ።
“ነገር ግን ይህ የባሕር መተላለፊያ የማግኘት ዕድል በአገራት መካከል በሚኖር ወዳጅነት እና ስምምነት የሚገኝ እንደ መሆኑ፣ ስምምነቱ ሊሻሻል እና ሊፈርስ የሚችል ነው” ይላሉ።
አቶ ባይሣ እንደሚሉት ኤርትራ አሰብን አልፈልገውም ብላ በገዛ ፈቃዷ ኢትዮጵያ እንድትጠቀምበት መስጠት ትችላለች። ያ ማለት ግን የአሰብ ወደብ የኢትዮጵያ ግዛት ሆነ ማለት ላይሆን ይችላል። የመጠቀም መብትን እንጂ ግዛትን ቆርጦ የሚሰጥ አገር አለ ብለው አያምኑም።
በምሳሌነትም ሞልዶቫን እና ዩክሬንን የሚያነሱት አቶ ባይሣ፣ ሞልዶቫ ከዩክሬን 600 ሜትር የባሕር በር በመውሰድ ወደብ ግንብታ በዚህ በር አማካይነትም በጥቁር ባሕር በኩል የወጪ እና ገቢ ንግዷን እያሳለጠችበት ነው።
በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መካከል ያለው ጉዳይም በተመሳሳይ በአሥመራ ፈቃድ የሚወሰን ይሆናል። “አሰብን በተመለከተ ከኤርትራ መንግሥት ፈቃድ ውጪ ሊሆን አይችልም” ሲሉ የዓለም አቀፍ ሕግ ባለሙያው ይናገራሉ።
በኃይል የባሕር ባለቤት መሆን ይቻላል?
የኢትዮጵያ የባሕር በር ፍላጎት በመንግሥት በኩል በይፋ ተነስቶ የመነጋገሪያ ርዕስ ከሆነ በኋላ በአፍሪካ ቀንድ የኃይል እርምጃ እና ግጭት ሊከተል ይችላል ይሆን የሚል ስጋት በበርካቶች ዘንድ እየተፈጠረ ነው።
ነገር ግን ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ በተደጋጋሚ የአገራቸውን የባሕር መተላለፊያ የማግኘት ፍላጎት በንግግር እና በመግባባት የማስፈጸም ፍላጎትን አጽንኦት በመስጠት፣ ኢትዮጵያ ፍላጎቷን በኃይል ለማስፈጸም ጦር እንደማትሰብቅ ተናግረዋል።
አቶ ባይሣ ቀደም ባለው የዓለም ታሪክ ውስጥ በአገራት መካከል ትልልቅ የሚባሉ ጦርቶች የተካሄዱት “የባሕር መውጫ እና መግቢያን እንዲሁም የባሕር ንግድ መስመሮችን ለመቆጣጠር የተደረጉ ናቸው” በማለት የባሕር በሮችን በበላይነት ለመያዝ የነበሩ ፍላጎቶች ለበርካታ ጦርነቶች ምክንያት መሆኑን ገልጸዋል።
አሁን ጊዜው ተቀይሯል የሚሉት የሕግ ባለሙያው “አሁን ጉልበት አለኝ ብሎ ጎረቤት አገርን በመውረር የባሕር በር ባለቤት ለመሆን መሞከር ጊዜው ያለፈበት ከመሆኑም በላይ፣ ከዓለም አቀፉ ማኅበረሰብም ምንም አይነት ምክንያት ቢኖር ተቀባይነት ማግኘት አይቻልም” ይላሉ።
ነገር ግን ጦርነት ተነስቶ አንደኛው አገር የበላይነት በመያዝ የባሕር በሩን ሊይዝ ይችላል። “ባለቤትነቱ ሕጋዊ ሳይሆን በጉልበት የባሕር በር ይዞ የተባበሩ መንግሥታት ድርጅት የፀጥታ ኃይልን በማስገባት መጠቀም ይቻል ይሆናል። ሕጋዊ ያልሆነውን በጉልበት ተይዞ በረዥም ጊዜ (በ30 እና 40 ዓመት) ወደ ሕጋዊነት የሚቀየርበት ሁኔታ ሊኖር ይችላል” ብለዋል።
ዓለም አቀፍ ድርጅቶች እና አገራት ይህንን ዓይነት አካሄድ ባይደግፉትም፣ ሊሆን እና ተቀባይነት ሊያገኝ የሚችልበት መንገድ ግን የለም ማለት እንደማቻል ይጠቅሳሉ።
ታሪካዊ ጥያቄ
የኤርትራ የነጻነት ጥያቄ ሲነሳ የኢትዮጵያ የባሕር በር የማግኘት ፍላጎት እና ጥያቄ አብሮ ሲነሳ ለዘመነት ቆይቷል።
በተለያዩ ወገኖችም የኤርትራ ነጻ አገርነት እውን ሲሆን፣ የኢትዮጵያ የባሕር መተላለፊያ የማግኘት መብት አብሮ መታየት እንዳለበት ሲጠይቁ ቆይተዋል።
ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ማብቃት በኋላ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሲቋቋም በርካታ የላቲን አሜሪካ እና አረብ አገራት የኤርትራን ነጻነት ሲደግፉ እንደነበር የሚያወሱት አቶ ባይሣ፤ የቀድሞዋ ሶቪየት ኅብረትም ተመሳሳይ አቋም ብትይዝም አሰብ ለኢትዮጵያ ይሰጥ በሚል መከራከሯን ይጠቅሳሉ።
ነገር ግን ኤርትራ ነጻነቷን ባወጀችበት ጊዜ ኢትዮጵያን ሲመራ የነበረው መንግሥት፣ የኢትዮጵያን የወደብ የይገባኛል ጥያቄ የማቅረብ ዕድል የነበረው ቢሆንም ጥያቄው በአግባቡ አለመነሳቱን አቶ ባይሣ ያነሳሉ።
ከዚህ አንጻርም ኢትዮጵያ ወቅታዊውን ሁኔታ በማንሳት ከኤርትራ ጋር የተጠቃለለችው “የአሰብ ወደብ ለእኔ ይገባኛል ብላ በተባበሩት መንግሥታት ወይም በሌላ ዓለም አቀፍ ደረጃ ብታሰመዝግብ የፈለገውን ያህል ትውልድ ቢቆይ መልሳ መጠየቅ ትችል ነበር” ይላሉ።
ከዚህ አንጻር በምሳሌነትም ሩሲያ ከዩክሬን የወሰደችውን ክራይሚያን ያነሳሉ። ክራይሚያ በ2014 (እአአ) በሩሲያ በኃይል ሲወሰድባት ዩክሬን ከመጀመሪያው ጀምሮ “ግዛቴ ተወስዶብኛል ብላ አስመዝግባለች” በዚህም ሳቢያ አገራት እና ተቋማት አሁን ድረስ ክራይሚያ የዩክሬን እንጂ የሩሲያ ናት ብለው ዕውቅና አልሰጡም።
ከዚህ አኳያ ኤርትራ ነጻ ስትወጣ ኢትዮጵያ “የአሰብ ወደብ የእኔ ነው። ጉልበት ስላጣሁ ነው የተወሰደው ብላ አስመዝግባ ቢሆን ኖሮ በየትኛውም ጊዜ በታሪክ ውስጥ የባለቤትነት ጥያቄው ይቀጥላል። ከዚያም በሽማግልናም ሆነ ወደ ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት በመሄድ መጠየቅ ይቻል ነበር” ብለዋል።
አቶ ባይሣ እንደሚሉት በጊዜው የነበሩ ሁለት የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት “አሰብ መቼም የኢትዮጵያ አካል ሆና አታውቅም። አሰብን ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጭንቅላት ፍቀን ማውጣት አለብን ብለው ሲናገሩ ሰምቻለሁ” በማለት ፍላጎት እንዳልነበረ ያስታውሳሉ።
ስለዚህም ኤርትራ ነጻ አገር ስትሆን “ኢትዮጵያ ምንም ዓይነት የይገባኛልም ሆነ የባለቤትነት ጥያቄ አላነሳችም። በመንግሥት ደረጃም በይፋ ወደቡ የእኔ ነው ወይም ይገባኛል ብላ አታውቅም። በዚህም ጥያቄ የማቅረብ ዕድሏ ተበላሽቷል” በማለት ጥያቄው ሊነሳበት የሚያስችልበት ዕድል መጥበቡን ያስረዳሉ።
“ዕድሉ አምልጧል” የሚሉት አቶ ባይሣ ከአሁን በኋላ ከኤርትራ ጋር መሆን የሚችለው ንግግር እና ድርድር ብቻ መሆኑን ያነሳሉ። “በሠላማዊ እና በመልካም ጉርብትና ላይ የተመሠረቱ አማራጮችን ማየት እንጂ በጦርነት እና በጉልበት አሰብን ማስመለስ አይቻልም” ብለዋል።