የደቡብ ኮሪያው ፕሬዝዳንት ወታደራዊ ሕግ በመደንገጋቸው ይቅርታ ጠየቁ

ፕሬዚዳንት ዩን ሱክ ማክሰኞ ዕለት ወታደራዊ ሕግ ደንግገው ነበር።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ወታደራዊ ህግ ያወጁት የደቡብ ኮሪያው ፕሬዝዳንት ዩን ሱክ ዮል ለተግባራቸው ይቅርታ ጠየቁ።

ፕሬዝዳንቱ አክለውም ሌላ እንደዚህ ዓይነት ድንጋጌ እንደማይኖር ቃል ገብተዋል።

የማክሰኞ ምሽት መግለጫቸውን የአገሪቱ ብሔራዊ ምክር ቤት በፍጥነት የቀለበሰው ሲሆን፣ እርሳቸውም ከስልጣን ሊነሱ ይችላሉ ተብሎ ይጠበቃል።

የፕሬዚዳንቱ ንግግር ምላሽ ተከትሎ የገዥው ፓርቲ ፣ ፒፕል ፓወር ፓርቲ መሪ (ፒፒፒ) ለጋዜጠኞች እንደተናገረው ዩን መደበኛ ስራቸውን ማከናወን ከብዷቸዋል።

ሃን ዶንግ-ሁን "ከሥልጣናቸው ቀድመው መልቀቃቸው የማይቀር ነው" ብለዋል።

"በጣም አዝናለሁ እናም የተደናገጡትን ሰዎች ከልብ ይቅርታ መጠየቅ እፈልጋለሁ" ሲሉ ዩን በቴሌቪዥን በተላለፈ አጭር ንግግራቸው ይቅርታ ጠይቀዋል።

"አገሪቱ በወታደራዊ ዕዝ ስር እንድትሆን ማወጄን በተመለከተ፣ ራሴን ከማንኛውም የሕግ ወይም እና ፖለቲካዊ ኃላፊነቶች አላሸሽም"

ፕሬዝዳንቱ አገሪቱ በወታደራዊ ዕዝ ሥር እንድትሆን ከደነገጉ በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ ለሕዝባቸው ንግግር ሲያደርጉ ከሥልጣን እንደሚወርዱ ያሳውቃሉ ተብሎ ቢጠበቅም ይህንን አላደረጉም፤ ይልቁንም ሁኔታውን የማረጋጋት ስራ ለገዥው ፓርቲያቸው አሳልፈው መስጠታቸውን ገልጸዋል።

ከስልጣን እንዲነሱ ክስ ስለመቅረቡም ያሉት ነገር የለም።

ቅዳሜ ዕለት ተቃዋሚዎች ዮንን ከስልጣን ለማውረድ በቀረበው ጥያቄ ላይ ድምጽ እንዲሰጥ ግፊት እያደረጉ ነው።

300 መቀመጫዎች ባሉት ፓርላማ ውስጥ፣ ጥያቄው ሁለት ሶስተኛ ድምጽ ማግኘት ያለበት ሲሆን፣ ቢያንስ ስምንት የዩን ፓርቲ አባላት ድጋፋቸውን መስጠት ይጠበቅባቸዋል።

የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ሊ ጄ ሚዩንግ አርብ ዕለት የፕሬዚዳንት ዩን አስተያየት በጣም እንዳሳዘናቸው እና የሕዝቡን የቁጣ እና የክህደት ስሜት እንደሚጨምሩ ተናግረዋል።

ሊ አክለውም ፕሬዚዳንቱን ከስልጣን ለማውረድ የተቻላቸውን ሁሉ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።

"በአሁኑ ወቅት ደቡብ ኮሪያን የገጠማት ትልቁ ስጋት የፕሬዚዳንቱ በስልጣን ላይ መኖር ነው።"

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

በዩኦን ድርጊት የተበሳጩት ፖለቲከኞች ብቻ አይደሉም።

የ50 ዓመቷ ያንግ ሶንሲል በደቡብ ኮሪያ ዋና ከተማ ሴኡል በሚገኘው የናምዳሚን ገበያ የምግብ ቤት ባለቤት ነች።

አገሪቱን በወታደራዊ ዕዝ ስር የሚያስቀምጠው ሕግ ሲታወጅ ፍርሃትና አለማመን እንደተሰማት ለቢቢሲ ተናግራለች።

"በእሱ [ዮን] እንደ ፕሬዝዳንት ሙሉ እምነት አጥቼበታለሁ፣ እሱ ከእንግዲህ የእኔ ፕሬዝደንት ነው ብዬ አላስብም" ስትል ተናግራለች።

"እስከ መጨረሻው ድረስ መታገል አለብን፤ የፕሬዚዳንትነቱን ቦታ እንዲይዝ መፍቀድ አንችልም።"

በዚያው ገበያ ላይ የተገኘው ሸማቹ ሃን ጁንግሞ ደግሞ፣ ፕሬዝዳንት ዮን ይቅርታ መጠየቁ በቂ አይደለም ብሏል።

ፕሬዚዳንቱ ከሕዝቡ ጋር ያላቸውን አመኔታ በማፍረሳቸው "ወይ በገዛ ፈቃዳቸው ስልጣናቸውን መልቀቅ አልያም በሕግ እንዲወርዱ ሊደረግ ይገባል" ብሏል።

"በፕሬዝዳንትነቱ ለመቀጠል ፍላጎት ካሳየ በጣም ተስፋ ቢስ ሁኔታ ይሆናል፤ ምክንያቱም ይህ ፕሬዝዳንት የፈጸመው በደል የወታደራዊ ሕጉ ብቻ አይደለም።"

ደቡብ ኮሪያ ማክሰኞ ምሽት ላይ ዩን አስደንጋጩን ወታደራዊ ሕግ ማወጃቸውን ተከትሎ በፖለቲካዊ ቀውስ እና ትርምስ ውስጥ ገብታለች።

ፕሬዚዳንቱ ከሰሜን ኮሪያ ኮሚኒስት ኃይሎች አገራቸውን ለመጠበቅ ወታደራዊ ሕጉ አስፈላጊ ነው ሲሉ ተናገረው ነበር።

ነገር ግን ወታደራዊ ሕጉ በታወጀ ሁለት ሰዓት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ የፓርላማ አባላቱ ፕሬዚዳንቱን ተቃውመው በምክር ቤት ከተሰበሰቡ በኋላ አስቸኳይ ድምጽ በመስጠት ውሳኔውን አግደዋል።

ፕሬዚዳንቱ ይህንን ሕግ እንዲያውጁ ምክንያት የሆናቸው እሳቸው እንዳሉት የውጭ ኃይሎች ስጋት ሳይሆን ውስጣዊ የፖለቲካ ችግሮች እንደሆኑ ግልጽ የሆነው ብዙም ሳይቆይ ነበር።

አንዳንድ የሕግ አውጭዎች ፓርላማ ውስጥ ለመሰብሰብ እና የዮንን ድንጋጌ ለመሻር ለማድረግ የጸጥታ ኃይሎችን ለማለፍ አጥር ሲዘሉ፣ የተቀመጡ መከላከያዎችን ሲሾልኩ ታይተዋል።

የፓርላማ አባላት የዮን ድንጋጌ ከሻሩ በኋላ፣ ሌላ አዋጅ ያወጣሉ ተብሎ ተሰግቶ ነበር።

አንዳንድ የሕግ አውጭዎች ሌላ ሕግ ቢወጣ በፍጥነት ለመሻር በብሔራዊ ምክር ቤት አቅራቢያ ቆይተው ነበር ተብሏል።

ወታደራዊ ሕግ (ማርሻል ሎው) የሲቪል ባለሥልጣናት ሥራቸውን በአግባቡ ማከናወን እንደማይችሉ በሚቆጠርበት ጊዜ ወታደራዊ ባለሥልጣናት እንዲመሩ የሚደረግበት ጊዜያዊ አገዛዝ ነው።

አንዲት አገር በወታደራዊ ሕግ ስር በምትሆንበት ወቅት የሲቪል መብቶች መታደግ እንዲሁም ወታደራዊ ሕጉ ሊራዘም የሚችልበት ሁኔታ ይፈጠራል።

በደቡብ ኮሪያ ለመጨረሻ ጊዜ ወታደራዊ ሕግ የታወጀው በአውሮፓውያኑ 1979 ሲሆን፣ ወቅቱም አገሪቱን ለበርካታ ዘመናት የገዙት አምባገነኑ ፖርከ ቹንግ ሂ በመፈንቅለ መንግሥት መገደላቸውን ተከትሎ ነው።