ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ኢላን መስክ በጠቅላይ ፍርድ ቤት ምርጫ ለሚሳተፉ የ1 ሚሊዮን ዶላር ስጦታ እየሰጠ ነው
ቢሊየነሩ ኢላን መስክ ዊስኮንሲን በተባለችው ግዛት ለሚገኙ መራጮች የአንድ ሚሊዮን ዶላር ቼክ እየሰጡ መሆኑ ተሰምቷል።
መስክ ካለፈው ሳምንት ጀምሮ ነው የአንድ ሚሊዮን ዶላር ሽልማት መስጠት መጀመሩን ያስታወቀው። በዊስኮንሲን እጅግ የሚጠበቀው የጠቅላይ ፍርድ ቤት ምርጫ ማክሰኞ ይካሄዳል።
ዲሞክራቱ የዊስኮንሲን ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ጆሽ ካውል ሽልማቱ ድምፅ ለማግኘት ሲባል ስጦታ መስጠት ክልክል ነው የሚለውን ሕግ የሚጥስ ነው በማለት ክስ አቅርበዋል።
በምርጫው ምክንያት የግዛቷ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ወደ ሪፐብሊካን ሊያዘነብል ይችላል። ይህ ደግሞ ለትራምፕ እና አስተዳደራቸው መልካም ዜና ነው።
እሑድ በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ንግግር ሲያሰማ የነበረው ኢላን መስክ "እኛ የምንፈልገው ዳኞች የዳኝነት ሥራ እንዲሰሩ ብቻ ነው" ብሎ ለሁለት ሰዎች ለእያንዳንዳቸው የአንድ ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ሰጥቷል።
ሽልማቱ የሚደርሳቸው ሰዎች "አክቲቪስት" የሆኑ ዳኞችን ለማስቆም የሕዝብ ድምፅ ላይ ፊርማቸውን ያሳረፉ ሰዎች ናቸው።
ካውል የኢላን መስክ ድርጊት ድምፅ ለመግዛት የሚደረግ ሕጋዊ ያልሆነ ተግባር ነው ሲሉ ከሰዋል። የመስክ ጠበቃዎች ደግሞ ካውል "የመስክን ፖለቲካዊ ንግግር ለማገድ ሙከራ እያደረጉ ነው። ይህ ደግሞ የሕገ-መንግሥቱን የመጀመሪያውን አንቀፅ የሚጥስ ነው" ሲሉ ተከራክረዋል።
የመስክ ጠበቃዎች አክለው ስጦታው "አክቲቪስት የሆኑ ዳኞችን ለማስቆም የሚደረግ እንቅስቃሴ ነው እንጂ ለዚህ ምረጡ አሊያም አትምረጡ የሚል አይደለም" ብለዋል።
ካውል ሁለት ዝቅተኛ ደረጃ ላይ ያሉ ፍርድ ቤቶች ለኢላን መስክ ማድላታቸውን ካወቁ በኋላ የግዛቷ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ክሳቸውን እንዲሰማ ቢጠይቁም ጥያቄያቸው ተቀባይነት አላገኘው።
መስክ እና ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ወግ አጥባቂው ዳኛ ብራድ ሻይምል በዕጩነት አቅርበዋል። ተቀናቃኛቸው ደግሞ ሊበራሏ ዳኛ ሲዛን ክራውፎርድ ናቸው።
የአንድ ግዛት የጠቅላይ ፍርድ ቤት ምርጫ እንዲህ መነጋገሪያ የሆነው ዶናልድ ትራምፕ ለሶስተኛ ጊዜ ለመመረጥ ራሳቸውን እያመቻቹ ስለሆነ ነው የሚሉ አስተያየቶች ይሰማሉ።
መስክ ዕጣ ለደረሳቸው ሰዎች በነብስ ወከፍ አንድ ሚሊዮን ዶላር ከመስጠቱ በላይ ለወግ አጥባቂው ዳኛ የምርጫ ቅስቀሳ ቡድን 14 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ አድርጓል።
ኢላን መስክ ለድምፅ ሰጪዎች የገንዘብ ሽልማት ሲያደርግ ይህ የመጀመሪያው አይደለም።
ባለፈው ዓመት በጣም ወሳኝ በሚባሉ ግዛቶች ለሚገኙ መራጮች የሕገ-መንግሥቱን የመጀመሪያውን አንቀፅ እንደሚደግፉ በፈርማ በማረጋገጣቸው በነብስ ወከፍ አንድ ሚሊዮን ዶላር መስጠቱ አይዘነጋም።