ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
የሰው ልጅ ዝግመተ ለውጥን እንደ አዲስ የሚጽፍ ነው የተባለው ሚሊዮን ዓመት ዕድሜ ያስቆጠረው የራስ ቅል
በቻይና የተገኘ አንድ ሚሊዮን ዓመት ዕድሜ ያለው የሰው ልጅ የራስ ቅል ሆሞ ሳፒየንስ የሚባለው የሰው ልጅ ዝርያ ከምንገምተው ከግማሽ ሚሊዮን ዓመት በፊት መኖር መጀመሩን ያሳያል ሲሉ ተመራማሪዎች በአዲስ ጥናታቸው አረጋግጠዋል።
ኒያንደርታልን ጨምሮ ከሌሎች ተመሳሳይ ዝርያዎች ጋር ከገመትነው ጊዜ በላይ እንደኖርን ያሳያል ብለዋል።
ሳይንቲስቶቹ ትንታኔያቸው ስለ ሰው ልጅ ዝግመተ ለውጥ ያለንን ግንዛቤ "ሙሉ በሙሉ ይለውጣል" ትክክል ከሆነ በታሪካችን ውስጥ ቁልፍ የሆነውን የመጀመሪያ ምዕራፍ እንደገና ይጽፋል ይላሉ።
ሌሎች ባለሙያዎች በበኩላቸው አዲሱ የጥናት መደምደሚያ አሳማኝ ቢሆንም ከእርግጠኝነት ግን በጣም የራቀ ነው ብለዋል።
'ሳይንስ' በተሰኘው ታዋቂ የሳይንስ መጽሔት ላይ የታተመው ግኝቱ፤ ከቻይና ዩኒቨርሲቲ እና ከእንግሊዝ የተፈጥሮ ታሪክ ሙዚየም ሳይንቲስቶች የተካተቱበትን የምርምር ቡድን አስደንግጦታል።
"ውጤቱን ስናገኝ ጀምሮ የማይታመን መስሎን ነበር። ይህ እንዴት ወደ ኋላ ሊወስድ ይችላል?" ብለዋል ጥናቱን የመሩት የፉዳን ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ዢጁን ኒ።
"ነገር ግን ሁሉንም ሞዴሎች ለመፈተሽ ሁሉንም ዘዴዎች ተጠቅመን ደጋግመን ሞከርን። እናም አሁን ስለ ውጤቱ እርግጠኞች ነን። በእውነቱ በጣም ደስተኞች ነን።"
ሳይንቲስቶች ዩንሺያን 2 የተሰየመውን የራስ ቅል ሲያገኙት የሆሞ ኢሬክተስ ሰው ነው ብለው አስበው ነበር። ይህ የሆነው ብዙ ሰው ዝርያዎች ብቅ ካሉበት ጊዜ በፊት ወደ አንድ ሚሊዮን ዓመታት ገደማ የጀመረ በመሆኑ ነው።
ሆሞ ኢሬክተስ በኋላም ከ600 ሺህ ዓመታት በፊት በዝግመተ ለውጥ ወደ ኒያንደርታሎች እና ሆሞ ሳፒየንስ መከፋፈል ጀመረ።
ነገር ግን በገለልተኛ የጥናት ቡድን የተገመገመው ዩንሺያን 2 ሆሞ ኢሬክተስ እንዳልሆነ ይጠቁማል።
ከኒያንደርታልስ እና ሆሞ ሳፒየንስ ጋር ተመሳሳይ በሆነ የእድገት ደረጃ ላይ የምትገኘው የሆሞ ሎንግይ ቀደምት እህት ዝርያ እንደሆነ ይታሰባል።
የጄኔቲክ ማስረጃዎች ከጎናቸው እንደነበሩ ይጠቁማሉ። ስለዚህ ዩንሺያን 2 ከመቶ ዓመት በፊት በምድር ላይ በእግሩ ከተጓዘ፤ ሳይንቲስቶች እንደሚሉት የኒያንደርታል እና የመጀመሪያዎቹ የራሳችን ዝርያዎችም ተመሳሳዩን አድርገዋል።
የጥናቱ ተባባሪ መሪ የሆኑት የተፈጥሮ ታሪክ ሙዚየም ፕሮፌሰር ክሪስ ስትሪንገር ይህ አስገራሚ ትንታኔ ትልቅ አእምሮ ያላቸው የሰው ልጆች የዝግመተ ለውጥ ጊዜን ቢያንስ በግማሽ ሚሊዮን ዓመታት ውስጥ በአስደናቂ ሁኔታ ቀይሮታል ብለዋል።
በፕላኔታችን ላይ እስካሁን ያልተገኙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ዓመታት ያላቸው የሆሞ ሳፒየንስ ቅሪተ አካል ሊኖሩ እንደሚችሉ ተናግረዋል።
የጥንት ሰውን ዝርያ ለመለየት እና በምድር ላይ ስለመራመዱ የራስ ቅሉን ቅርፅ እና የዘረመል መረጃን በመተንተን ይታወቃል። ሁለቱም ዘዴዎች ለዩንሺያን 2 ጥቅም ላይ የዋሉ ሲሆን አንድ መደምደሚያ ላይ ደርሰዋል።
በካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ የዝግመተ ለውጥ ጄኔቲክስ ተመራማሪ የሆኑት ዶ/ር አይልዊን ስካል ግን በሁለቱም ዘዴዎች ብዙ እርግጠኛ ያልሆኑ ነገሮች እንዳሉ ይናገራሉ።
"አንድ ሰው በተለይ ስለጊዜ ጉዳይ ግምታዊ መሆን አለበት። ምክንያቱም እንደዚያ ለማድረግ በጣም አስቸጋሪ ናቸው" ብለዋል።
"ምንም እንኳን ከፍተኛ መጠን ያለው የዘረመል መረጃ ቢኖርም እነዚህ ዝርያዎች በ100 ሺህ ዓመታት ውስጥ ወይም ከዚያ በላይ ሊኖሩ የሚችሉበትን ጊዜ ማስቀመጥ በጣም አስቸጋሪ ነው።"
አክለውም የፕሮፌሰሮች ኒ እና ስትሪንገር መደምደሚያዎች አሳማኝ ቢሆኑም ከእርግጠኝነት በጣም የራቁ በመሆናቸው እና የበለጠ ለማረጋገጥ ተጨማሪ ማስረጃ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።
"ይህ ሥዕል አሁንም ለእኛ ግልፅ አይደለም። ስለሆነም የዚህ ጥናት መደምደሚያ በሌሎች ትንታኔዎች፤ በተለይም በአንዳንድ የዘረመል መረጃዎች የሚደገፉ ከሆነ የበለጠ መተማመን የምንጀምር ይመስለኛል" ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።
ቀደምት የታወቁ ሆሞ ሳፒየንስ ማስረጃዎች የተገኙት በአፍሪካ ሲሆን ከ300 ሺህ ዓመታት በፊትእንደነበሩ ያሳያል። ስለዚህ የእኛ ዝርያ በመጀመሪያ በእስያ ውስጥ ሊፈጠር ይችላል ብሎ መደምደም ፈታኝ ነው።
በዚህ ደረጃ እርግጠኛ ለመሆን በቂ ማስረጃ የለም የሚሉት ፕሮፌሰር ስትሪንገር፤ በአፍሪካ እና አውሮፓ ውስጥም አንድ ሚሊዮን ዓመት ያስቆጠረ የሰው ልጅ ቅሪተ አካል በመኖሩ በትንተናው ውስጥ መካተት አለበት።
"የእኛ ዝርያዎች እንደገና ሊጣመሩ እንደሚችሉ የሚጠቁሙ አንዳንድ የዘረመል ማስረጃዎች አሉ። ይህ ግን እስካሁን አልተረጋገጠም" ሲሉ ለቢቢሲ ተናግሯል።
ጊዜው መርዘሙ ሦስቱ የሰው ልጅ ዝርያዎች በፕላኔታችን ላይ ለ800 ሺህ ዓመታት ያህል አብረው ኖረዋል፤ ይህም ቀደም ሲል ከታሰበው በላይ ረዘም ያለ ጊዜ ነው። ምናልባትም እርስ በርስ ተግባብተውና ተዳቀለው ኖረዋል።
ቀደም ብሎ ብቅ ማለቱ ከ800 ሺህ እና ከ100 ሺህ ዓመታት በፊት የሳይንስ ሊቃውንት በሰው ልጅ ቤተሰብ ውስጥ ለመለየት አስቸጋሪ ሆነው ያገኟቸው በደርዘን የሚቆጠሩ ቅሪተ አካላትን ለመረዳት ይረዳል።
የሆሞ ሳፒየንስ፣ ሆሞ ሎንጊ እና ኒያንደርታልስ ቀደም ብቅ ማለት ችግሩን በዘዴ ይፈታል። ይህም ማለት አሁን ለመመደብ አስቸጋሪ የሆኑትን ቅሪተ አካላት "ከትልልቅ ሦስት" ወይም ቀደምት ቅድመ አያቶቻቸው ኤዥያ ሆሞ ኢሬክተስ እና ሃይደልበርገንሲስ ንዑስ ቡድን መመደብ ተችሏል ይላሉ ፕሮፌሰር ኒ።
"የሰው ልጅ ዝግመተ ለውጥ እንደ ዛፍ ነው። ይህ ዛፍ በርካታ ቅርንጫፎችን ያካተተ ነው። የቅርብ ዝምድና ያላቸው ሦስት ዋና ዋና ቅርንጫፎች ነበሩ። እናም እርስ በርሳቸው የተዳቀሉ እና ለአንድ ሚሊዮን ዓመታት ያህል አብረው ኖረዋል። ስለዚህ ይህ የማይታመን ውጤት ነው።"
የራስ ቅሉ ከሁቤይ ግዛት በቁፋሮ ተገኝቷል። ሁለት የራስ ቅሎች አብረው ቢገኙም ሁለቱ የተጎዱ እና የተጨፈቁ ናቸው። ይህም ዩንሺያን 2 ኢሬክተስ ተብሎ ከተፈረጀባቸው ምክንያቶች አንዱ ነው።
ወደ ቀድሞ ቅርጻቸው ለመመለስ የፕሮፌሰር ኒ ቡድን የራስ ቅሎችን ስካን በማድረግ እና የኮምፒዩተር ሞዴሊንግ ቴክኒኮችን በመጠቀም የሦስት ማዕዘን (3 ዲ) ቅጂዎችን ለማተም ችለዋል።
ሳይንቲስቶቹ ይህንን በማየት የበለጠ የላቀ የሰው ዝርያ አድርገው እንዲመድቧቸው አግዟቸዋል።