'ሀሰተኛዋ' ጀርመናዊት ሀኪም ታሰረች

ሀሰተኛዋ ሀኪም በቁጥጥር ሥር ውላለች

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

ጀርመን ውስጥ ለአራት ህመምተኞች ሞት ተጠያቂ ናት የተባለችው ሀሰተኛ የህክምና ባለሙያ በቁጥጥር ሥር ዋለች።

እንደ ጎርጎሮሳውያኑ አቆጣጠር ከ 2015 እስከ 2017 በማዕከላዊ ጀርመን ውስጥ በሚገኝ ሆስፒታል ውስጥ ትሠራ የነበረው በሀሰተኛ ማስረጃ እንደሆነም ተገልጿል።

የ48 ዓመቷ ሴት፤ የሰው ሕይወት በማጥፋት፣ ሰነድ በማጭበርበርና የኃላፊነት ቦታን ያላግባብ በመጠቀም ምርመራ እየተደረገባት እንደሆነ ታውቋል።

ትሠራበት በነበረው ሆስፒታል ውስጥ ከማደንዘዣ ጋር በተያያዘ ስሀትት ሳቢያ፤ አራት ሰዎች ሲሞቱ ስምንት ሰዎች ደግሞ የጤና እክል ገጥሟቸዋል።

ማደንዘዣ እንዴት መጠቀም እንዳለባት ተገቢውን ትምህርት ሳትወስድ በሥራው በመሰማራቷ ጉዳቶቹ እንደደረሱም ተመልክቷል። በሆስፒታሉ ውስጥ ለነበሩ ታካሚዎች የተሳሳተ መድሀኒት በመስጠትም ተጠርጥራለች።

ከወራት በፊት የጀርመን መገናኛ ብዙህን በዘገባቸው እንደገለጹት፤ አቃቤ ሕግ ሆስፒታሉ ውስጥ ሰዎች ስለመጎዳታቸው ማስረጃ የለም ብሎ ነበር።

የኋላ ኋላ ግን ፖሊሶች ሆስፒታሉን ፈትሸው ሰነዶች ሰብስበዋል። ሆስፒታሉም ለምርመራው ሙሉ ትብብር እንደሚያደርግ አሳውቋል።